ከእንቁላል ፋብሪካ ወደ ሩፋኤል ቤተክርስቲያን የሚያስኬደውን ቀጭን አስፋልት ይዘን እየወጣን ነው፤ ትንሽ እንደተጓዝንም የምንፈልገውን ቦታ ወይም ቤት ያገኘን መሰለንና መኪናችንን አቆምን። በእርግጥ የምንፈልገውን ቤት አግኝተናል። ይህ ቤት ምናልባትም በተለያየ ምክንያት የህይወት መንገዳቸውን ስተው በደባል ሱስ ውስጥ ገብተው ብዙ ነገራቸው የተበላሸ፤ ከመኖር ወዳለመኖር ሊሸጋገሩ የነበሩ የህብረተሰብ ክፍሎች እያገገሙበት ያለ ቤት ነው። ቤቱ ለሰዎቹ ተስፋ ሆኗቸው ከገቡበት ሱስ ሊያላቅቃቸው ግብ ግብ ላይ ያለም ነው።
ቤቱ የውጭ በሩ ግጥም ብሎ ተዘግቷል። ለመዘጋቱ ደግሞ ምክንያት አለው። በውስጡ ያሉት ሰዎች ጥበቃና እንክብካቤ የሚሹ ምስጢራቸው ከዛ ግቢ መውጣት የሌለበት ስለሆኑም ጭምር ነው።
እኛ ደግሞ እዚህ ቤት የተገኘነው ቀድመን ፈቃድ አግኝተን ነውና በሩን ለማንኳኳት አልፈራንም። አዲስ ህይወት የአልኮል መጠጥና የአደንዛዥ እፅ የቅድመ መከላከልና የተጠቂዎች የማገገሚያ ማዕከል ስሙ ነው። በርካቶች እያገገሙበት፣ ከተሳሳተው መንገዳቸው ተመልሰው ቀናውን መንገድ እያዩበት፣ ያለፉትን ህይወት እየኮነኑ የነጋቸውን ብሩህነት አሻግረው እያዩበት ነው።
የተዘጋውን በር አንኳኩተን ተከፈተልን፤ ለከፈቱልን ጎልማሳ ሰውም የመጣንበነትን ምክንያት ብሎም ቀጠሮ የተያዘልን መሆኑን ነግረን እንድንገባ ፈቅዱልን። አመስግነን ወደውስጥ ዘለቅን። በድንጋይ የታነጸው ቤት ከውጭ ሲታይ ያምራል፤ ወደውስጥ እንድንዘልቅ ጥበቃው ፊት ፊታችን ይመሩናል፤ እኛም ወደመሩን እየሄድን ዙሪያ ገባውን እንቃኛለን፤ ቤቱ የጋራ የሚባል ሳሎን አለው፤ ሳሎኑ የትኛውም ቤት ሊኖር በሚችል እቃ ተሟልቶለታል። ከዛ ቀጥሎ የነርሶች ክፍል የዋና ዳይሬክተርና የፋይናንስ ቢሮዎችም አሉ።
በሱስ የተጠቁ አሁን በማገገም ላይ ያሉ ሰዎችም ግማሾቹ የመኝታ ክፍሎቻቸውን ያጸዳሉ፤ ሌሎቹ ደግሞ የጠዋቷን ጸሀይ እየሞቁ እርስ በእርሳቸው ይጨዋወታሉ። እኛም ጠጋ ብለን ሰላምታ ከሰጠናቸአው በኋላ ከየት እንደመጣን በመግለጽ ትውውቅ አደረግን። ከመካከላቸውም ያለፉበትን የሱስ መንገድ አንስተው ከእኛ ሌሎች እህት ወንድሞቻችን ይማሩ ማንም በሱስ ውስጥ መግባት የለበትም የሚለውን መልዕክት ሊያስተላልፉልን ዝግጁ መሆናቸውን ጠየቅን። ወጣት አሉላ በላይ ሙሉ ፈቃደኛ መሆኑን ገልጾልን ተያይዘን ለመጨዋወት በሚያመቸን ቦታ ላይ ቁጭ አልን።
አሉላ በላይ የ36 ዓመት ወጣት ነው። ተወልዶ ያደገው አዳማ ከተማ ነው። ቤተሰቦቹ እሱን ጨምሮ ስድስት ልጆችን ወልደዋል። እርሱ ደግሞ የመጨረሻ ልጅ ነው። አሉላ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን እዛው አዳማ ከተማ በሆተ ጥበብና በአዳማ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተከታትሏል። በትምህትርት ሰነፍም ጎበዝም ሳይሆን በመካከለኛ ደረጃ ትምህርቱን ተምሯል።
“……በወቅቱ የትምህርት ጥቅም ባይገባኝም ለቤተሰቦቼ ስል መማር እንዳለብኝ አስብ ነበር። ከዚህ የተነሳም አነባለሁ የቤት ስራ ሰርቼ እሄዳለሁ በጠቅላላው የተጣለብኝን የተማሪነት ኃላፊነት በአግባቡ ለመወጣት የምችለውን ሁሉ በማደረግ በትምህርቴም ጥሩ የምባል ነበርኩ” ይላል።
ነገር ግን በ1996 ዓ.ም የ10ኛ ክፍል ማጠናቀቂያ ፈተና ወስዶ ወደ መሰናዶ ትምህርት የሚያስገባ ውጤት ባለማግኘቱ የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ቤት ይገባል። በዚህ ሁኔታ እምብዛም ደስተኛ ባይሆንም የነበረው አማራጭ ግን መማር ብቻ ሆነ።
አሉላ አባቱን በ1994 ዓ.ም ነው በሞት ያጣው። ከዛን በኋላ ያለውን ጊዜ ልጆችን የማሳደግ የማስተማር ኃላፊነቱ የወደቀውም በእናቱ ላይ ነበር፤ ይህም ቢሆን ግን እናቱ በጣም ታታሪና በጣም ጎበዝ ስለነበሩ የባለቤታቸውን ሀዘን ችለው ልጆቻቸው ከትምህርት እንዳይቀሩ እንዳይጎልባቸው የቻሉትን ሁሉ ያደርጉም ነበር። አሉላ እናቱ ልጆቻቸውን ለማሳደግ የሄዱበትን መንገድና ያሳለፉትን ነገር ሲያስብ እጅግ ይገረማል የእኔ እናት የጀግኖች ጀግና ናትም ይላል።
“…..እናቴ ለእኔ ጀግናዬ ናት። እንደውም እሷን መግለጫ ቃላት ያጥረኛል፤ አባታችን ከሞተ በኋላ እኛን ለማኖር የሄደችበት መንገድ እጅግ የሚገርም ምናልባትም በጣም ጥበብና የፈጣሪ እርዳታ የታከለበት ሆኖ ይሰማኛል “ ይላል።
አሉላ የቴክኒክና ሙያ ትምህርቱን ቢያጠናቅቅም በ1998 ዓ.ም በግሉ ፈተናውን የ10ኛ ክፍል ማጠናቀቂያ ፈተናን ዳግም ተፈትኖ ወደመሰናዶ ትምህርት የሚያስገባውን ውጤት አመጣ።
እዚህ ላይ ግን አሉላን ከመንገድ የሚያወጣ ምናልባትም አሁን ላለበት ደረጃ ያበቃውና ከፍ ያለ ስነ ልቦናዊ ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም ማህበራዊ ቀውሶችን ይዞበት ወደመጣው ሱስ ገባ። አሉላ ለጥናት ብሎ የጀመረው ጫት እንደቀልድ ጣፈጠው፤ ከመጣፈጥም አልፎ በቁጥጥሩ ስር አዋለው። ይህ የጫት ሱስ ደግሞ ሌሎች ደባል ነገሮችንም ጎተተበት፤ ቀኑን በመቃም ምሽቱን ደግሞ እሱን ለመስበር በሚል በመጠጣት ማሳለፍ የቀን ተቀን የኑሮው ሂደቱ ሆነ። በጣም የሚገርመው ግን በዚህ ሁሉ ሱሶች ውስጥ ሆኖ አንድም ቀን ትምህርቱን ስለማቋረጥ አስቦ አለማወቁ ነው። የመሰናዶ ትምህርቱን በአግባቡ ይማራል፤ ክፍል ይገባል፤ ከትምህርት ጓደኞቹም በእውቀት አይተናነስም። ነገር ግን ከትምህርት ቤት ሲወጣ እነሱ ወደ ቤታቸው እሱ ደግሞ ሱሶቹን ሊያስተናግድባቸው ወደሚችሉት ቦታዎች መሄዱ ልዩነት ፈጠረ።
“…….በወቅቱ ገንዘብ እንኳን ባይገኝ በቀላሉ ጫት ይገኝ ነበር። አንዱ ጓደኛም ገንዘብ ካለው ለሁሉም ይተርፋል፤ በጠቅላላው ለሱስ ሲሆን ምንም አይጠፋም” በማለት ይገልጸዋል።
“ውሃ ሲወስድ አሳስቆ” እንደሚባለው አሉላም እንደ ቀልድ ለጥናት ብሎ የገባበት የጫት ሱስ በቀላሉ የሚተወው አልሆነም። እንደውም ከቀን ቀን ፍጆታው እየጨመረ ከጫትና ከጫት ቃሚዎች ጋር አብሮ የሚያሳልፈው ሰዓት እየረዘመ መጣ። አሁን የመሰናዶ ትምህርቱን አጠናቆ የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተናንም ወስዶ አልፏል። ምድቡም ሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ መሆኑ ታውቋል። ሊማር የተመደበበት የትምህርት ዘርፍ ደግሞ ሲቪል ኤንድ አርባን ኢንጂነሪንግ ነው። በውጤቱም በተመደበበት የትምህርት ዘርፍም ደስተኛ ነበር።
“ …..በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የጀመርኩትን የጫትና የሌሎችም ነገሮች ሱስ ዩኒቨርሲቲ ስገባ አጠናከርኩት። እረ እንደውም በራሴ መንገድ ህጋዊ ሁሉ አደረኩት። ማንንም ሳልፈራ በልበ ሙሉነት መቃም መጠጣት ስራዬ ነበር። ገንዘብ እንደሆነ ለሱስ አይጠፋም፤ከእኔ ቀድመው ዩኒቨርሲቲ ገብተው የወጡ ጓደኞቼ ይሰጡኛል። እናቴም እህት ወንድሞቼም በሚችሉት አቅም ይልኩልኛል። በተለይ አንዷ እህቴ ዱባይ ስለነበረች በተወሰኑ ጊዜያት ልዩነት ገንዘብ ትልክልኝ ነበር፤ በወቅቱም በትንሽ ገንዘብ በአራት ብር ብዙ ጫት መግዛት ይቻላል፤ ብቻ ገንዘብ አይጠፋም፤ ከጠፋም ደግሞ ሌላ መንገድ ይፈጠራል። በቃ ለሱስ እና ለቀብር ገንዘብ አይጠፋም” በማለት ያለፈበትን መንገድ ይገልጻል።
ወጣት አሉላ ይህንን መሰል ህይወት ውስጥ ይኑር እንጂ በዩኒቨርሲቲ ቆይታው ለትምህርቱ ላቅ ያለ ትኩረትን ነበር የሚሰጠው። ጓደኞቹ ከተመረቁበት ጊዜም አንዲት ሴሚስተር እንኳን ሳይጨምር 2 ነጥብ 9 ውጤት ይዞ ስለመውጣቱ ይናገራል።
“በትምህርትማ ቀልድ አላውቅም። ጠዋት ክፍል እገባለገሁ እማራለሁ፤ ከሰዓት በኋላ ምሳዬን እንደበላሁ የማጠናውን ወረቀት ይዤ ጫት ቤት እሄዳለሁ፤ እዛ እያጠናሁ እቅማለሁ። ግን ከወጣሁ በኋላ ያ ሁሉ ጥንካሬዬ ጠፍቶ ከባድ የሱስ ወጥመድ ውስጥ ወደኩ፤ እሱም ለአሁኑ ለተበላሸው ህይወቴ አበቃኝ” ይላል።
ከሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በሲቪል ኤንድ አርባን ኢንጂነሪንግ እንደተመረቀ በቀጥታ ከሰም ስኳር ፋብሪካ ነበር ስራ የጀመረው። በወቅቱም ይከፈለው የነበረው ደመወዝ በጣም ትልቅ ስለነበር ይዞት የገባውን ሱስ አጠናክሮ ለመቀጠሉ መደላድሉን ፈጠረለት።
“ …..አሁን እያነበብኩት ያለሁት መጽሀፍ አለ በእውነት ከእኔ ህይወት ጋር የሚመሳሰል ነው። የመጽሀፉ ርዕስ “ሪች ዳድ ፖር ዳድ” ነው የሚለው፤ይህ መጽሀፍ ሰዎች በውል የማያውቁት “ዲዛየር” የሚባል በሽታ እንዳለ ይገልጻል፤ ይህ በሽታ ደግሞ ገንዘብ ችግርን የሚፈታ እንዲመስለን የሚያደርግ ነው። ነገር ግን ገንዘብ ሲመጣ ችግሮቹም ቀዳዳዎቹም ይበዛሉ፤ አንድ ሰው ቮልስ ቫገን ይነዳ ከነበረ ልክ ገንዘቡን ሲያገኝ የተሻለ መኪና ያምረዋል እንደማለት ነው፤ እኔም በፊት በማገኘው ገንዘብ እጠቀማቸው የነበሩ አደንዛዥ ነገሮች አቅሜን ያገናዘቡና መጠናቸው ትንሽ ነበር፤ ነገር ግን ገንዘብ ከተገኘ በኋላ ጥፋቱም የዛኑ ያህል ጨመረ” ይላል።
ወጣት አሉላ እንደ ቀልድ ብዙ ብዙ ጊዜዎቹ ባከኑበት “…. በጣም የሚገርመው ደግሞ ሱስ ውስጥ ያለን ሰዎች የሚያዘናጋን የራሳችን ጭንቅላት ነው። ሰውዬው በቃሲል ጭንቅላቱ ደግሞ እረ ዛሬ አይደለም ጊዜው አንተ እኮ በማንኛውም ሰዓት ከወሰንክ ማቆም ተችላለህ፤ ዛሬ ግን አታድርገው የሚል የተሳሳተ መረጃን ያቀብላል። በእንደዚህ አይነት ሁኔታ መሄዱ ደግሞ መመለስ ወደማይቻልበት መንገድ ያስገባል”።
ዛሬ ላይ አሉላ ያለፉትን ጊዜያት ሲያስባቸው ይገረማል በመባከናቸው ቢያዝንም ዛሬን ያሳየውን ከሱስ ወጥቶ ጥሩ ጭንቅላት ላይ ቆሞ እያመዛዘነ፤ ነገን እያቀደ፤ እያወጣ፤ እያወረደ መሆኑን ሲያስብ ደግሞ ተመስገን ይላል።
“…..ሱስ እንደዋዛ እያሳሳቀ ረጅም ርቀት ይዞ ይጓዛል፤ እኔም በዚህ ሁኔታ ረጅም ርቀት ከሄድኩ በኋላ ነቃ ብዬ ዞር ስል የመጣሁበት ርቀት በጣም ረጅም ነው። ረጅም ብቻም ሳይሆን በጣም አስፈሪ ከዛ ሁሉ በላይ ደግሞ በዚህ በተሳሳተ መንገድ ስጓዝ ተው ጥሩ መንገድ ላይ አይደለህም ሲሉኝ በመንገዴ ውሃ ሲያቀብሉኝ የነበሩ ሁሉ ተሰላችተው ደክሟቸው ትተውኛል። በቃ ልመለስ ስል እነዛ ሰዎች ከጎኔ የሉም። ይህ ደግሞ የሰሃራ በረሃ ላይ ብቻ እንደመጣል አይነት ስሜት እንዲሰማ ያደርጋል። በዚህ አጋጣሚ ደግሞ ሱሱ በግላጭ አግኝቶ ይጫወትብናል” በማለት ስለ አስፈሪው ጊዜው ይናገራል።
አሉላ በተለይም በዚህ ሱስ ውስጥ ሆኖ መውጣት ሲያቅተው ታላቅ ወንድሙ ቴዎድሮስ በላይ ያደረገለትን ብሎም የለፋውን ልፋት መርሳት ይከብደዋል። ነገር ግን ብዙ ቢታገልም እሱ ዝግጁ ስላልነበር ውጤታማ ሳይሆን ቀረ።
አሉላ በከፋ የሱስ መንገድ ራሱን ጥሎ ከቤተሰቡ ተነጥሎ ቆይቷል። ሰው ቢታመም፣ ቢወልድ፣ አይጠይቀም። ቢሞት ለቅሶ አይደርስም።ሰርግ፣ ምርቃት፣ ክርስትና የመሳሰሉት ነገሮች እሱ ጋር ቦታ የላቸውም። የእሱ ቤተሰብ የቅርብ ጓደኛ ብቻ ከጎኑ ሆኖ በርታ ግፋበት የሚለው ሱሱ ነበር። አሉላም እጅ ሰጥቶ ስለነበር ከሱስ ለመውጣት ቢያስብ እንኳን መንገዱን ስለማያውቀው ከመኖር ወዳለመኖር የሚሸጋገርበት መንገድ ላይ ደርሶም ማቆም አልቻለም ነበር። እሱ እንደሚለው የፈጣሪ እጅ ገብቶበት አትሙት ጠፍተህ አትቅር ሲለው ግን አንድ አጋጣሚ ወደህይወቱ መጣ። አሉላ አጋጣሚውን ዛሬ ላይ ቆሞ ሲያስበው እውነት ሁሉ አይመስለውም።ህልም ከህልምም የማይጨበጠው ቅዠት ይመስለዋል። ግን ሁሉም ነገር እውነት ነበር።
የልጅነት ጓደኛ ውለታ
አለም ፈርሳ ድጋሚ ብትሰራ ሁሉ ለእኔ እንደ ልጅነት ጓደኛዬ አብሮ አደጌ ክብሮም ሃጎስ የሚያስገርመኝ ይፈጠራል ብዬ አላስብም። ክብሮም የልጅነት ጓደኛዬ ነው። እሱ ያደረገልኝን በአንደበቴ መግለጽ ይከብደኛል።በቀላሉ ከሞት ወደህይወት መልሶኛል። እኔ ክብሮምን ቀሪ ዘመኔን እንኳን የእሱ አገልጋይ ሆኜ ብቀር ውለታውን የምከፍለው አይመስለኝም።
ክብሮም ሀጎስን ሁለት ዓመት እበልጠዋለሁ ታላቁ ነኝ፤ ግን ደግሞ ሁሉም ሰው ስለእኔ ሰልችቶት በምክርም በድጋፍም ፊቱን ባዞረብኝ ወቅት የደረሰልኝ ነው። ሳይታክት ፈልጎ አግኝቶኝ ያለሁበትን ሁኔታ አይቶ ሳይጠየፍ እንደውም ሁለመናዬን ቀይሮ አንደኛ ሚዜው አድርጎኝ ሰው ፊት አቀረበኝ።
በወቅቱ እኔ የነበርኩበት ሁኔታ እንኳን ሰው የተሰበሰበበት ቦታ ሚዜ ሆኜ ልቆም ቦታ ጠፍቶሽ አቅጣጫ ለመጠየቅ የምትመርጪኝ ሰው አልነበርኩም። እሱ ግን ይህንን ሳያይ የልጅነት ጓደኛዬ ሚዜዬ ሆኖ ካላጀበኝ ማን ሊያጅበኝ ብሎ መርጦኝ ሚዜ አደረገኝ። እሱ አይደለም የሚገርመው፤ አንድ ወር ከአንድ ሳምንት ቤቱ አስቀምጦኝ እራሴን እንድመለከት ከነበርኩበት ሁኔታ እንዳገግም ሰውነቴ እንዲመለስ ብዙ አደረገልኝ።
ክብሮም ኑሮው ከአገር ውጪ በመሆኑ ሊሄድ ሲል አንተን ሱስ ላይ ጥዬ ወይም ገንዘብ ሰጥቼ ሙት ብዬህ አልሄድም፤ ከዛ ይልቅ በደንብ የምትለወጥበት ቦታ አስገብቼህ ወደራስህ እንድትመለስ ሰርተህ መብላት የምትችልበት ቁመና ላይ እንድትደርስ አደርጋለሁ፤ብሎ መጀመሪያ ጳውሎስ ሆስፒታል ወሰደኝ፤ ከዛ ግን ወደ አዲስ ህይወት የሱስ ማገገሚያ ማዕከል ይዞኝ መጣ በማለት ጓደኛው ለእሱ የሆነውን ይናገራል።
አንዳንድ ጊዜ ሱሱ ሙሉ በሙሉ ወስዶሽ መተው በማትችይበት ወቅት ሰዎች ብዙ ጥረት ያደርጋሉ፤ነገር ግን ስኬታማ አይሆኑም።እኔ ደግሞ የነበርኩበት ሁኔታ ሰዎች ጥረት አድርገው ሰልችቷቸው የተውኝ ሰዓት ላይ ነበር በተቃራኒው ግን እኔ ደግሞ ከሱስ ጋር መኖሬ እጅግ ያንገፈገፈኝና የመረረኝ፤ማነው ከዚህ መከራ የሚያወጣኝ ብዬ ያልኩበት ወቅት ነበር ጓደኛዬ ወደእኔ የመጣው።
“…..ማንም ሰው በተለያዩ ሁኔታዎችና አጋጣሚዎች ሱስ ውስጥ ሊገባ ይችላል፤ በዛ ሂደትም የነበረውን ነገር ሁሉ ቀስ በቀስ እያጣ ይሄዳል። ከሁሉም በላይ ግን አጥቶ አጥቶ ከነበረው ነገር ቀንሶ መሬት ላይ ሲደርስ ቆም ብሎ ማሰብ ይገባዋል። እኔ መሬት ደርሼ ነበር ስራዬንም ትቼ እነሱ እንኳን ጊዜ ሰጥተው ና ሲሉኝ እበሳጭ ነበር። ብቻ ለመጥፊያ አይጠፋምና ባልሰራም መጥፊያዬ በዝቶ ጠፍቼም ነበር” ይላል።
አሉላ በዛ ሁኔታ ውስጥ ሆኖ አብረውት አፈር ፈጭተው ያደጉትን ልጆች ሲያይ የተሰማውን ስሜት መግለጽ ይከብደዋል። አብዛኞቹ በጣም ጥሩ ስራና የገቢ አቅም ላይ ናቸው፤ቤተሰብ መስርተዋል፤ ኑሯቸውን በሰላም ይኖራሉ፤ ከሱስ ነጻ ናቸው፤ መልካቸው፣ አለባበሳቸው በጣም ያምራል፤ እሱ ግን ከነሱ በተቃራኒው ነው፤ ስጋ ርቆት በአጥንቱ እየሄደ ነው፤ገንዘብ የለውም፤ እናቱን እህት ወንድሞቹን አስቀይሟል፤ ትዳር አልመሰረተም በጠቅላላው የእኔ የሚለው ነገር የለውም። ይህንን ሁሉ ዞር ብሎ እንዲያይ ያደረገው ደግሞ የክብሮም ሰርግ ነው።
ብዙ ሰው በገንዘብ አቅም ጓደኛ ሲበልጠው እኔስ ሊል ይችላል አሉላ ግን የእነሱ ገንዘብ አይደለም ያማረው ወይም እኔስ እንዲል ያደረገው ገንዘብን ጤናማ ሆኖም ጤናማ ሳይሆንም አገኝቶት ጤናማ አካባቢ ባለመዋሉ ያጣው ነገር ነው። አሉላ በዚህ አልተበሳጨም፤ ከዛ ሁሉ በላይ እኔስ እንዲል ያደረገው ጓደኞቹ በሙሉ ሰው ፊት ሊቀርብ የሚችል ቁመና ባለቤት መሆናቸው ነው። ይህ ሁኔታ ደግሞ በውሳኔው እንዲጸና ዳግም ወደሱስ እንዳይመለስ ከራሱ ጋር ቃል እንዲገባ አደረገው።
“…..እኔ እድለኛ ነኝ ዛሬን ለማየት በቅቻለሁ። የነበርኩበትን ዞር ብዬ ሳስበው ከሞቱት በላይ ካሉት በታች ነበርኩ፤ በሱስ ምክንያት ራሴን ያልሆነ ነገር ውስጥ አስገብቼ ነበር፤ አሁን ሳስበው ሱስ ምንም ጥሩ ነገር የሌለው ገዳይ ከሰው በታች የሚያደርግ አዋራጅ መንገድ መሆኑ ይሰማኛል” በማለት ይገልጸዋል።
ሱስ ውስጥ ላሉ
ማንኛውም ሰው መኖር ነው የሚፈልገው፤ መኖር የሚፈልግ ሰው ደግሞ በፍጹም ሱስ ውስጥ አይገባም። እኔ በወቅቱ ሱስ ገዳይ ነው ከሰው ያሳንሳል ተብዬ ብዙ ተለምኛለሁ፤ ተመክሬያለሁ፤ ነገር ግን አልሰማሁም። እኔ አሁን ለሌሎች የምናገረው ሱስ ሊያጠፋ ሲል ምልክት ያሳያል፤ ከማህበራዊ ህይወት ይነጥላል፤ ለቅሶ አያስደርስም ፣ ለሰው ግድ ማጣት ይፈጥራል፣ ራስን ያስጥላል ፣ ንጽህናን ለመጠበቅ ጊዜ አይሰጥም፤ እነዚህ ነገሮች ሲመጡ በሱስ ውስጥ ያለ ሁሉ ቆም ብሎ ሊያስቡ ይገባል።
“…ሌላው ጥያቄ መኖር ትፈልጋለህ፤ አትፈልግም የሚል ነው” መኖር የፈለገ ሰው ዛሬ ነገ ሳይል ከገባበት ሱስ ሊወጣ ይገባል። ምክንያቱም ሱስን እያስተናገዱ መኖር ስለማይቻል። አንዳንድ ሰዎች መከርን ይሉና አጉለው ይናገራሉ “ጫት ብቻ እኮ ችግር የለውም፣ መጠጥም ሳይበዛ ጥሩ ነው” ይላሉ ግን ልክ አይደለም፤ ምናልባት በደንብ እስኪይዝና ጉልበት እስኪያሳጣ ድረስ ማዘዝ ይቻል ይሆናል። ቀስ ብሎ ወደመሃል ካስገባ በኋላ ግን ማንኛውም ሱስ አዛዥ ይሆናል።
እኔ በከንቱ አስራ ምናምን አመቶቼ ጠፍተውብኛል። መሆን በሌለበት መንገድ ስራዬን ቤተሰቤን በጠቅላላው ማህበራዊ ግንኙነቴን አጥቻለሁ። ሌሎችም እኔን አይታችሁ ተማሩ ሱስ እያስተናገዱ መኖርን መምረጥ ስህተት ነው።
ቤተሰብ ሊረዳው የሚገባው ነገር
ማንም ወላጅ ልጁን አሳደኩ ሊል የሚችለው ከ14 ዓመት እድሜው በኋላ ነው። ከ14 ዓመት በታች ያሉ ህጻናት በቁጥጥር ስር ስለሆኑ ማንም አያሳድጋቸውም ፈጣሪም ይጠብቃቸዋል። 14 ዓመት ሲሆን ግን የወላጅ የአስተዳደግ ጥበብ መገለጥ ይጀምራል። ከዛ በኋላ በወላጅ ፍላጎት መዝናናት ቀርቶ በልጁ ፍላጎት መሄድን ያስፈልጋል። ከልጆች ጋር መግባባት እንጂ ተቆጪ መሆን ዋጋ ያስከፍላል። ሌላው ወላጆች ልጆቻቸው ምንም ነገር ውስጥ ቢገቡ መውጣት እንደሚችሉ ከወዲሁ መንገር ማስተማር መቻል አለባቸው።
ከቤትሽ ጀርባ አንድ ትልቅ ተራራ አለ። ተራራውን መውጣት እየፈራሽ አልወጣሽም፤ ነገር ግን አንድ ቀን በሰዎች አደፋፋሪነት ወጣሽና ስታይው ውብ የመዝናኛ ቦታ ያለው ስፍራ ሆኖ አገኘሽው፤ከዛ በኋላ ማንም ሳትጠብቂ መመላስ ጀመርሽ፤ ሱስም እንደዚሁ ነው። ወላጆች ለልጆቻቸው ጫትንም ሆነ ሲጋራን አግዝፈው ይነግሯቸዋል፤ ተጠቃሚውንም ሰው እንደሌላ ፍጡር ይስሉላቸዋል። በሆነ አጋጣሚ ልጆቹ ሲያዩት ግን ጭንቅላታቸው ውስጥ ትልቅ ቦታ ይሰጡታል፤ ከዛ መመለሱ ከባድ ይሆናል።
በመሆኑም ማንም ወላጅ ለልጁ መናገር ያለበት ሲወለድ ሲጋራ ጫት ወይም የአረቄ መለኪያ ይዞ የተወለደ አለመኖሩን ነው፤ ነገር ግን እድሜው ሲደርስ በአቻ ግፊትም ይሁን በሌላ ምክንያት ሊገባበት ይችላል፤ እንደ ወላጅ ቀደም ብለን ልንል የሚገባን ነገር “ልጄ ከእለታት አንድ ቀን ተሰናክለሽ ብትደፈሪ ተመልሰሽ ትቆሚያለሽ፤ ወንዱንም አንድ ቀን ተሳስተህ ሱስ ውስጥ ብትገኝ ነገ ትመለሳለህ” ማለት መቻል ያስፈልጋል። በመሆኑም ወላጆች ለልጆቻቸው ሊናገሩ የሚገባው ነገር ምንም ነገር ከቁጥጥራቸው ውጪ እንዳልሆነ የተበላሸ ነገር መስተካከል እንደሚችል ነው።
ስለ አዲስ ህይወት የእጽና አልኮል ሱሰኞች ማገገሚያ ማዕከል
ብዙ ሰዎች ይህንን ተቋም አያውቁትም፤ እዚህ ማዕከል ውስጥ ለመምጣት ፍቃደኛ የሆነ ሱስ ውስጥ ያለ ሰው ሁሉ መዳን፤ ማገገም፤ ወደቀድሞ ስብዕናው መመለስ የሚያስችል ህክምናን ያገኛል። ስህተትን ማረሚያ መንገዶች አሉ። በሀይልና በጉልበት ከሱስ ለማስወጣት ከመሞከርም ወደዚህ ያሉ ተቋማት ማምጣት ጥሩ ነው። ከእኔ ተሞክሮ ልናገር በሱስ ውስጥ ካሉ ሰዎች መካከል 20 በመቶው በሚያደርጉት ነገር ደስተኞች አይደሉም። ምናልባት መርሳት የሚፈልጉት ነገር ይኖራል፤ አልያም መውጣት እንደማይቻል ሆኖ አእምሯቸው ውስጥ ቀርቷል። በመሆኑም ምንም ነገር ሳታከብዱ እኔ አለሁልህ ልጄ በማለት ከባለሙያ በመማከር ወደደዚህ አይነት ተቋም ማምጣት ያስፈልጋል።
በሌላ በኩል ሰዎች ወደዚህ አይነት ተቋም ሲመጡ ከ 90 በመቶ በላይ ስራው የራሳቸው በመሆኑ አእምሮን ማሳመን ወደቀደመው መንገድ መመለስ የሚያመጣውን ነገር ማወቅና መረዳት ወደኋላ ላለመመለስ መወሰን፤ እነዛን አስቀያሚ ጊዜያትን ማሰብ፤ ወደፊት ለመራመድ ደግሞ ራዕይ ማስቀመጥ ያስፈልጋል። መልካም ነገሮችን የሚያስቡና በስብዕናቸው ምሉዕ ከሆኑ ሰዎች ጋር መዋልና እነሱን ሞዴል ማድረግ ያስፈልጋል።
ማዕክሉም የማንበብ፤ ራስን የማዳመጫ ጊዜ ይሰጣል የስነ ልቦና አማካሪዎች አሉ፤ ስምንት ሰዓቱን የስራ ሰዓት ለማስለመድ ጥረት ይደረጋል። በጠቅላላው ማዕከሉ ከዚህ በበለጠ ቢጠናከር ብዙ ሰዎችን ማገልገል እና መመለስ ይችላል።
መልዕክት
አገርን መለወጥ አቅም ያላቸው ሰዎች ሱስ ውስጥ አሉ፤ አገርንም እያጠፉ ያሉት ሰዎች በተመሳሳይ በሱስ ውስጥ ናቸው። ትልልቅ ፋርማሲስቶች ታማሚው እየተሰቃየ እነሱ በጎን መድሃኒት አውጥተው የሚሸጡት ለሱሳቸው ነው። የባንክ ማናጀሩ ለሚገባው ትቶ ለማይገባው ሰው ብድር የሚፈቅደው ለራሱ ሱስ ማስተናገጃ ስለሚያገኝበት ነው። ይህንን የምናገረው ዝም ብዬ አይደለም ከልምዴ ከአዋዋሌ ተነስቼ ነው።
በመሆኑም ይህ የሱስ ነገር ሁሉንም የሚነካ እንደ አገርም ብዙ ዋጋ እያስከፈለ ያለ ወደፊትም የሚያስከፍለን ነው። ይህም ቢሆን ግን እንደ አዲስ ህይወት አይነት ማዕከላት ብዙ የሉም። ጳውሎስ ሆስፒታል አገልግሎት ለመስጠት ቢሞክርም የሚመጡትን ታካሚዎች ባህርይ ያገናዘበ መስተንግዶ የለም። በሱስ የተጠቁ ሰዎች አሰልቺ ጊዜያትን ለማሳለፍ ይገደዳሉ፤ ይህ ደግሞ በሱስ ውስጥ ላለ ሰው ከባድ ነው። በመሆኑም ይህንን ሴክተር ማጠናከር ተነሳሽነቱን ወስደው የሚሰሩ ግለሰቦችን ማበረታታትና እነሱን መደገፍ ነገ አገር ተረካቢ ትውልድ እንዳናጣ ያደርጋል።
ሰው ወደሱስ እንዳይገባ ሰፈሩ ቁጭ ብሎ ድንጋይ እንዳያሞቅ ማድረግ ያስፈልጋል። በትምህርት ቤቶች ዙሪያ ያሉ ጫት ቤቶች መላ ሊመታላቸው ይገባል። ዛሬ አገር እየገነባን መንግስትም ብዙ ስራ እየሰራ ነው። ነገር ግን ስራው ውጤት የሚያመጣው ጤናማ ትውልድ መቀጠል ሲችል ብቻ ነው።
የወደፊት እቅድ
ከዚህ በፊት በነበረኝ ህይወት ምንም አላፍርም፤ ብዙ ጥፋቶችንም አጥፍቻለሁ፤ ትናንት ከሞት ያልተናነሰ ህይወት ኖሬያለሁ፤ ማህበረሰቡም ላብድ ስል ቆሞ እያየኝ ነበር፤አሁን በአዲስ ህይወት የሚኖረኝን ቆይታ አጠናቅቄ ስወጣ ግን የራሴን ስራ መጀመር፤ በምችለው አቅም በሱስ ውስጥ ያሉ ጓደኞቼን መንገድ ማሳየት እቅዴ ነው።
እፀገነት አክሊሉ
አዲስ ዘመን ታህሳስ 1 ቀን 2015 ዓ.ም