የአባታቸው ደቀመዝሙር ናቸው ።የ11ኛ ክፍል ተማሪ እያሉ ነበር በአጋጣሚ ከባሕረ ሐሳብ ጋር የተዋወቁት ።መማር የጀመሩት ።በዚህ ቀን ትፈተናላችሁ ሲባል ዕለቱን ለማወቅና ለመዘጋጀት አስበው ከቤት ውስጥ የነበረውን ተንጠልጣይ ካሌንደር ሲፈልጉ በቀላሉ ማግኘት አልቻሉም ።ስለዚህም በመፈለግ ጊዜያቸውን እንዳይፈጁ የፈለጉት ሐሳበ አቡሻህርን ጨምሮ የተለያዩ ሐሳቦችን የያዘው የባሕረ ሐሳብ መምህሩ አባታቸው ሊቀ ሊቃውንት ያሬድ ፈንታ ከወንበራቸው ሥር ወረቀትና ብዕር ይዘው እንዲቀመጡ አደረጓቸው ።
ማወቅ ያለባቸውን ዋና ዋና ነጥቦችን ጨምሮ የማንኛውም ቀን ዕለቱ የሚታወቅበት የስሌት መንገድንም በምሳሌ፡- እያደረጉ አስተማሯቸው ።ጋዜጠኛው መምህር ሔኖክ ያሬድ ፈንታም ትምህርቱን ለመጀመሪያ ችግር መፍቻቸው ብቻ ሳይሆን ለወደፊቱም የመፍትሔ ቁልፋቸው ሊያደርጉት ፈለጉ ።ከአባታቸው የቀሰሙትን እውቀት በቅርባቸው ላሉ ተማሪዎች ማሳወቁንና ክህሎታቸውን ማዳበሩን ተያዙት ።ተማሩና እስከ ሁለተኛ ዲግሪ ድረስም ጥናታዊ ሥራዎችን ከወኑበት፤ አስተማሩበትም ።
አሁንም የተለያዩ ጥናታዊ ጽሑፎችን ዩኒቨርሲቲዎችን ጨምሮ በተለያዩ መድረኮች ላይ አቅርበውበታል ።ስለ ኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር ምንነትና ፎክሎራዊ ገጽታ ለቱሪስት አስጎብኚዎች፣ ለባህልና ቱሪዝም ባለሙያዎች በተለያዩ ቦታዎችም እየተጋበዙ ሥልጠና ሰጥተውበታል ።እያስተማሩም ነው ።ይህ የዘመን አቆጣጠር በአገራችንና በዓለም ደረጃ እንዴት ይታያልና መሰል ጥያቄዎችን በማንሳት ከሕይወት ልምዳቸው ጋር በማድረግ ልናነጋግራቸው ወደናልና ተጋበዙልን ።
አዲስ ዘመን፡- የእርስዎን የሕይወት ተሞክሮ ስናነሳ አባትዎን ሳይጠቅሱ ማለፍ በፍጹም አይቻልም ።የዛሬውን መምህር የሠሩት እርሳቸው ናቸው ይባላል ።
መምህር ሔኖክ፡- የሥጋም የቀለምም አባቴ ከአካዳሚያው ትምህርት አስቀድሞ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ልዩ ልዩ የአብነት ትምህርቶችን ተምረዋል፣ ቀጽለዋል ።በርካታ መጻሕፍትን አዘጋጅተዋል ።ከነዚህም መካከል የግእዝ ቋንቋ መማሪያ (ፍኖተ ግእዝ ዘመናዊ)፣ የእንግሊዝኛና የአማርኛ ሰዋስውን የሚያስተምረው የንግግር ሥርዓቶችና አገባቦች፣ የዘርዐ ያዕቆብና የወልደ ሕይወት ሐተታዎች ትርጉምና ባሕረ ሐሳብ የቀመርና የሥነ ፈለክ ምሥጢር ይገኙበታል ።
ባሕረ ሐሳብን በጥልቀት ያጠኑ፣ ኢትዮጵያ ስምንት ዓመት ጨምራ የምትቆጥርበትና ወደኋላ የሚቀር ዘመን እንደሌላት ለመጀመሪያ ጊዜ ይፋ ያደረጉት እሳቸው ናቸው።አሁንም ከእሳቸው ወንበር እየቀጸልሁ ነው።የረቀቀውን የዘመን መቁጠሪያ ጥበብ በመማሬም ብዙዎችን አስተምሬያለሁ።ከዲፕሎማ እስከ ሁለተኛ ዲግሪ ድረስ ስማር የተለያዩ የትምህርት መስኮችን ቃኝቻለሁ።ሁሉንም ግን ከባሕረ ሐሳብ ጋር እንዳገናኛቸውና የበለጠ እውቀት እንድጨብጥባቸው አድርጎኛል ።
በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ከተማሪነቴ ጀምሮ እንድጽፍና የጽሑፍ ጥበብን እንድረዳም ከአባቴ የተሰጠኝ ትምህርት በብዙ መልኩ አግዞኛል ።ተነባቢ በነበረው የየካቲት መጽሔት የውጭ ጸሐፊ ሆኜ እስከ መሥራት ደርሻለሁ ።ቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲን ጨምሮ በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ከማስተማር ባለፈ ባሕረ ሐሳቡን አስመልክቶ ጥናታዊ ጽሑፎችን ለማቅረብ ችያለሁ ።እየሠራሁበት ባለው ሪፖርተር ጋዜጣ ላይ በተለይ ትውፊትና ዘመንን በተመለከተ ጥናት ተኮር መጣጥፎችን ለማዘጋጀት ባሕረ ሐሳቡ ትልቅ አቅም ፈጥሮልኛል ።
አዲስ ዘመን፡- የዘመን አቆጣጠር እንዴት ይገለጻል፣ የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር ከሌሎች የተለየ የሆነበት ምክንያት ምንድነው?
መምህር ሔኖክ ፡- የዘመን አቆጣጠርን ሐሳበ ዘመን እንለዋለን ።በቁሙ ሲፈታ የዘመን ቁጥር፣ ዕድሜ ማለት ነው ።በሌላ አገላለጽ ‹‹ባሕረ ሐሳብ›› ይባላል። እርሱም ቁጥር ያለው ዘመን ተብሎ ይፈታል ።ሐሳበ ዘመን ‹‹ካሌንደር›› ተብሎም ይጠራል ።በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥንታዊ ሥርዓተ ትምህርት ውስጥም ይገኛል ።አገራችንን ልዩ ከሚያደርጓት መገለጫዎች አንዱ የዘመን አቆጣጠር ስልቷ ነው። የዓመት ቁጥር ልኬት መባቻውን መስከረም 1 ቀን በማድረግ በፀሐይ 365 ከሩብ ቀን ይዘልቃል ።
አመዳደቡም 12ቱ ወር እያንዳንዱ ወር 30 ቀን፣ እንዲሁም ጳጉሜን ተብለው የሚታወቁ ሦስቱን ዓመት 5 በአራተኛ ዓመት 6 ቀኖችን የያዘ ነው ።ይህ የ13 ወራት አቆጣጠር በኛ ብቻ ሳይሆን በግብፅ ኮፕቲክም እየተሠራበት ይገኛል። ከሌሎቹ አቆጣጠሮች መካከል በዓለም አገልግሎት እየሰጠ ያለው በዘልማድ ‹‹የአውሮፓውያን አቆጣጠር›› የሚባለው ጎርጎርዮሳዊው ቀመር፣ ከርሱ በፊት የነበረው የጁሊየስ ቀመርን ጨምሮ ዓመቱን በ12 ወሮች ሲመድቡ የእያንዳንዱ ወር የቀን ብዛት 28፣ 30 እና 31 በማድረግ ይዘምታሉ ።የዓመቱ መጀመሪያቸው ጃንዋሪ (ታኅሣሥ/ጥር) ላይ ነው ።
እዚህ ላይ የሚነሣው ነጥብ አንዳንዶች በጽሑፍ ጭምር ሲገልጹ የኛን አቆጣጠር ‹‹የጁሊያን ካሌንደር›› ይላሉ ።ይህ ስሕተት ነው ።የጁሊያን አቆጣጠር መባቻው ጃንዋሪ መካተቻው ዲሴምበር ነው ።በየአራት ዓመቱ አንድ ቀን የሚጨምሩት በሁለተኛው ወራቸው 28 የነበረችው ፌብሪዋሪን 29 በማድረግ ነው ።በወር አደረጃጀት፣ በቀን መደብ፣ ባመት መባቻ አንገናኝም። የመሬት ዑደት 365.25 ቀን ነው ማለትን ብቻ እንጋራለን። አቆጣጠራችን ከግብፅ/ኮፕት ጋር ነው የሚመሳሰለው ።
አዲስ ዘመን፡- ስለ ሐሳበ ዘመን ዓይነቶች ቢያብራሩልን?
መምህር ሔኖክ፡- የዘመን አቆጣጠር መለኪያዎች ቀን፣ ወርና ዓመት ናቸው ። ይህም በመሬት፣ በፀሐይና በጨረቃ እንቅስቃሴዎች አማካይነት የሚገኝ ነው። ቀን የሚለካው መሬት በራስዋ ዛቢያ (መስመር) ላይ በምታደርገው ዑደት (ዙረት) ነው ።የጨረቃ ወር ሲባል ጨረቃዋ በ29 ወይም በ30 ቀኖች ውስጥ እያፈራረቀች ዙረትዋን የምትፈጽምበት ጊዜ ነው። ዓመት የሚለካው መሬት በፀሐይ ዙሪያ ዞራ ወደ ነበረችበት ለመመለስ በሚፈጅባት ጊዜ ነው ።በዚህም ጉዞዋ አማካይነት አራቱ ወቅቶች ማለትም ክረምት (ከሰኔ 26 እስከ መስከረም 25)፣ መፀው (ከመስከረም 26 እስከ ታኅሣሥ 25)፣ በጋ (ከታኅሣሥ 26 እስከ መጋቢት 25)፣ ፀደይ/በልግ (ከመጋቢት 26 ሰኔ 25) የተባሉት ይፈራረቃሉ ።
ሌሎች ዓውዶች የሚባሉ የዘመን መስፈሪያዎችም አሉ ። ዞረው የሚመጡት ዓውዶች ማለትም ዓውደ ዕለት ከእሑድ እስከ ቅዳሜ ያሉት 7 ቀኖች፣ ዓውደ ወርኅ በጨረቃ 29/30 ቀን፣ በፀሐይ ዘወትር 30 ቀን፣ ዓውደ ዓመት በጨረቃ 354 ቀን፣ በፀሐይ 365 ቀን፣ ዓውደ ጳጉሜን 4 ዓመት፣ ዓውደ አበቅቴ 19 ዓመት፣ ዓውደ ፀሐይ 28 ዓመት፣ ዓውደ ማኅተም 76 ዓመት፣ ዓውደ ቀመር 532 ዓመት ናቸው ።ከጠቀስናቸው የብርሃናት መለኪያ አንፃር የሐሳበ ዘመን ዓይነቶች ሦስት ናቸው ። እነርሱም የፀሐይ፣ የጨረቃ የፀሐይና የጨረቃ ጥምር አቆጣጠሮች ተብለው ይጠራሉ ።
ፀሐያዊው አቆጣጠር (ባለ 365/6 ቀን) በመደበኛነት እያገለገለ የሚገኝ ሲሆን የኢትዮጵያ አቆጣጠር፣ የአውሮፓውያን አቆጣጠር ወዘተ ያሉትን ይመለከታል ።የጨረቃው አቆጣጠር (ባለ 354 ቀን) በተለይ በእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ በዓመተ ሒጅራ ይታወቃል ።የፀሐይና የጨረቃ ጥምር አቆጣጠር ከአይሁድ ጋር ይያያዛል ።አይሁድ ወራቸውን በጨረቃ፣ ዓመታቸውን በፀሐይ ይቆጥራሉና ።የቤተ ክርስቲያን የዘመን አቆጣጠርም ይጋራዋል ።
ሁለቱን የብርሃን መንገዶች አቆጣጠርን ይከተላል። የልደት በዓልን የሚመስሉ በቋሚ ቀን የሚውሉት ፀሐይን ብቻ ሲከተሉ፤ ትንሣኤ (ፋሲካ) እና ከርሱ ጋር ተያያዥ የሚሆኑት በየዓመቱ የሚውሉበት ቀን የሚለዋወጠው ደግሞ የሁለቱን ፀሐይና ጨረቃ አቆጣጠር ይጠቀማሉ ።የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በተለይ መስከረም 1ን ርዕሰ ዓውደ ዓመት ቅዱስ ዮሐንስ ትለዋለች ።በዘመን መለወጫ ቀን በተለያዩ ታሪካዊ የዓመት መነሻዎች በሦስቱ መንገዶች በማስላት የዘመኑን ተዘዋዋሪ አጽዋማትና በዓላትን ታውጅበታለች ።
ከመደበኛው የዓመተ ምሕረት አቆጣጠሯ (ዓመተ ሥጋዌም ይባላል) በተጨማሪ በተለያዩ ታሪካዊ መነሻዎችም ዘመኑን ታሰላለች ።አንደኛው ዓመተ ዓለም ነው ።ዓለም ከተፈጠረበት ከክርስቶስ ልደት 5500 ዓመት በፊት አንስቶ ነው የሚቆጠረው ።በዚህም መሠረት ዛሬ በጀመርነው በ2015 ዓ.ም ዘመኑ 7515 ዓመተ ዓለም ይሆናል ።ይህም ዘመኑ ስምንተኛው ሺህ ውስጥ እንዳለን ያሳየናል ።
ሌላኛው ጥምር አቆጣጠር ሲሆን፤ በዚህ አቆጣጠር በዛሬው መስከረም 1 ቀን በፀሐይና ጨረቃ ጥምር አቆጣጠር የኢትዮጵያ 2023ን ጀምረናል ።ይህ ጥምር አቆጣጠር ትንሣኤን ይዘው በሚንቀሳቀሱና ልደትን ይዘው በማይንቀሳቀሱ በዓላትና አጽዋማት መካከል ያለውን ልዩነት ለማወቅ ይረዳል። በፀሐይ መስከረም 1 ቀን በጨረቃ ‹‹መስከረም 15›› መሆኑን፣ በሒጅራ ሠፈር 15ቀን 1444፣ በአይሁድ ኢሉል 15 ቀን 5782 መሆኑን ዕለታቱ በሦስቱም ሃይማኖቶች በጨረቃ አቆጣጠር ተመሳሳይነት ያረጋገጥነው በ2023 አቆጣጠራችን ነው ።እዚህ ላይ የዕለት የ«24 ሰዓት» መነሻ ሁለት ዓይነቶች መኖራቸውን ማስታወስ ይገባል ።
አንደኛው ከኛ አንፃር መደበኛው ፀሐያዊ ዕለት «ሲቪል ዴይ» የሚባለውና ጠዋት 12 ሰዓት የሚጀመረው ሲሆን፣ ከሥርዓተ አምልኮ ጋር የሚያያዘው ማታ 12 ሰዓት የሚጀመረው «ዕለተ ሊጡርጊያ» (ሊተርጂካል ዴይ) ሌላው ነው ።በሌላ በኩል እያንዳንዱ ዓመት በአራቱ ወንጌላውያን እንደ ቅደም ተከተላቸው ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስ (ባመቱ መጨረሻ ጳጉሜን 6 የምትሆንበት) እና ዮሐንስ ተብለው ተሰይመዋል። ለምሳሌ የያዝነው 2015 ዘመነ ሉቃስ የሚያበቃው በ366ኛው ቀን ላይ ጳጉሜን 6 ነው ።
አዲስ ዘመን፡- ስለ አዲስ ዓመት ከማውራታችን በፊት እስቲ ልዩ ስለሆነችዋ ጳጉሜን ይንገሩን?
መምህር ሔኖክ፡- ጳጉሜን ከነሐሴ ወር መጨረሻ አዲስ ዓመት ከሚጀመርበት መስከረም አስቀድመው የሚገኙ ዕለታትን ያቀፈች ናት ።ጳጉሜን ተጨማሪ ተብሎ ይተረጐማል። የ12ቱ ወራት 360 ቀኖች ብቻ ዓመቱን ሙሉ አያደርጉትም ።የሚሞላው የመጨረሻዎቹ የጳጉሜን ቀናት 5 ቀኖች (በአራት ዓመት 6) ሲመጡ ነው ። ንዑስ ወሩ ተጨማሪ የሚል ትርጉም ያገኘው በ12 ወራት ላይ የሚጨመር ስለሆነ ሲሆን፣ በሌላ በኩልም ከወሮች ዑደት ተርፎ ስለተገኘም ትርፍ ይባላል ።
ጳጉሜን ከዓመት ማጠቃለያ ባለፈ፣ እንደ ዘመን መነሻም የሚታሰብበት ልዩ መንገድ ሊቃውንቱ አላቸው። ‹‹ጳጉሜን የመጨረሻ አትምሰልህ የመጀመሪያ እንጂ›› ይሉታል ።ጳጉሜን እንደ አሮጌ ዓመት መዝጊያና የአዲስ ዓመት መጀመሪያ አድርጎ በማሰብም ሰዎች ራሳቸውን የሚገመግሙበትና ለመጪው አዲስ ዓመት ደግሞ እግዚአብሔር ምሕረቱን ረድኤቱን እንዲያበዛላቸው እየለመኑ ለበለጠ ሥራ ራሳቸውን የሚያዘጋጁበት ጊዜ ነው ።
አዲስ ዘመን፡- መስከረም ለምን የአዲስ ዓመት መነሻ እንዲሆን ተመረጠ ይላሉ?
መምህር ሔኖክ፡- በመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታችን ስለ አማርኛ ግጥም ስንማር ከማስታውሳቸው አንዱ ስለ የዓመቱ ወራት የቀረበውን ነው ።
‹‹ጨለማው ሲጠፋ ዝናቡ ሲያቆም
ያ የለውጥ ወራት መጣ መስከረም
ሰዎች ይነሣሉ ሊሠሩ ታጥቀው
መስከረም ነውና ብርሃን ሰጪው›› እያለ ዓመቱን ይዘልቃል ።ስለሆነም መስከረም ከባዱ ክረምት ቀዝቀዝ የሚልበት ደመራ ከተለኮሰ በኋላ መሰስ ብሎ የሚወጣበት፣ ምድሪቱ በአደይ አበባ የምታሸበርቅበት ነው ።‹‹መስከረም መስከረም የወራቱ ጌታ አበቦች ተመኙ ካንቺ ጋር ጨዋታ›› መባሉም ለዚህ ነው ። ሰ እና ዘ ተወራራሽ ናቸውና መስከረም ‹‹መዝከረም››ም ይባላል ።መዘክረ ዓም (የዓመት መታወሻ) ተብሎ ዘመን ይሰላበታል፤ በዓላትና አጽዋማት ይታወጅበታል ።በእርግጥ መስከረምን እንደኛ የአዲስ ዓመት መግቢያ የምታደርገው የግብፅዋ ኮፕቲክ ናት ።ከመስከረም ጋር በሚገናኘው ሴብቴምበር ዓመታቸውን የሚጀምሩት ቢዛንታይኖች እነ ግሪክ ኦርቶዶክስ ናቸው ።በኛ ነሐሴ 26 ላይ በዋለው ሴብቴምበር 1 ቀን አክብረዋል ።
እስራኤሎች ‹‹ሮሽ ሃሻናህ›› የዓመት መጀመሪያ/ ርዕሰ ዓመት የሚሉት የጨረቃ ጥቅምት 1 ቀን በአብዛኛው በመስከረም ወር ውስጥ ይውላል ። ዓለም በዚህ ወር ተፈጥሮበታል ብለው ያምኑበታል ። ሌላው መስከረም ወር እንደ መጋቢት ቀንና ሌሊቱ በ25ኛው ቀን ላይ እኩል 12፣ 12 ሰዓት የሚሆንበት ነው ።በ13 ወራት መደብ በ366 ቀናት የሚከበሩ የቅዱሳንና የነገሥታት እንዲሁም የዓለሙን ታሪክ በያዘው በጥንታዊው መጽሐፍ ስንክሳር፣ የዓመቱ መጀመሪያ መስከረምን ስለሆነ ይተነትነዋል።
‹‹የተባረከ የመስከረም ወር የግብፅ፣ የኢትዮጵያና የኑቢያ ዓመታት ወሮች ራስ ነው። የቀኑ ሰዓትም ከሌሊቱ ሰዓት የተስተካከለ አሥራ ሁለት ነው። ከዚህ በኋላ እያነሰ ይሄዳል ።›› ይህም የቀን እኩል ወይም ዕሪና ከክረምት ቀጥሎ በሚመጣው የአበባና የነፋስ ወቅት በመፀው፣ ‹‹የመፀው ዕሪና›› ተብሏል። ይህ ቀን ከዘመነ አክሱም ጀምሮ ክረምቱ ማለፉን አበቦች መፍካታቸውን ለማመልከት ‹‹ተቀፀል ጽጌ›› (አበባን ተቀዳጅ) እየተባለ በየዓመቱ እስከ 15ኛው ምዕት ዓመት ሲከበር ቆይቷል። ከዚያ ወዲህ ግማደ መስቀሉ ከመጣበት ጊዜ አንሥቶ ግን በመስከረም 10 ቀን እየተከበረ ይገኛል ።
አዲስ ዘመን፡- በአንድ በኩል ኢዮሃ አበባዬ ተያይዞም ዕንቁጣጣሽ ይባላል፤ ምንድን ይገልጻል?
መምህር ሔኖክ፡- ‹‹ኢዮሃ አበባዬ-መስከረም ጠባዬ›› ዘመን በተለወጠ ቁጥር የሚያስተጋባ ነው። በመጻሕፍት እንደተጠቀሰው፣ ኢዮሃ አበባዬ የደስታ ቃል ነው ።ወንዶች የደመራ ዕለት እየዘፈኑ ድምሩን የሚዞሩበት የአበባ ዘፈን ነው ።ሰኔ ግም ብሎ፣ ያምሌን ጨለማ አልፎ፣ የነሐሴን ጎርፍ ሙላትን በእኝኝ ተሻግሮና ተንተርሶ በጠንካራው ዝናብ (ውኃ) ምክንያት ብቅ የምትለዋ ያደይ አበባ ናትና፤ ውኃ ያደረገውን ታምር፣ ያስበቀለውን አበባ አደያዊን ተመልከት ለማለት ‹‹ኢዮሃ አበባዬ መስከረም ጠባዬ›› ይባላል ።
ወደ ዕንቁጣጣሽ ስንመጣ ከትውፊት የሚቀዱ አገላለጾች አሉ ። ከአዲስ ዓመት ዋዜማ ጀምሮ በተለይም በወርኃ መስከረም መሬቷ በአደይ አበባ አሸብርቃ ስለምትታይና በተለይም ዕንቁ የመሰለ አበባ ስለምታወጣ መሬቷን ዕንቁጣጣሽ፣ ‹‹ዕንቁ የመሰለ አበባ አስገኘሽ›› ለማለት ዕንቁጣጣሽ ተብላለች ።አያይዘው አቧራ፣ ቡላ የነበረው መሬት በዝናቡ ኃይል ለምልሞ ተመልከቱኝ፣ ተመልከቱኝ የምትል ያሸበረቀች፣ አበባ የተንቆጠቆጠች ሆነች የሚል ለዕንቁጣጣሽ ስያሜ መነሻ ሊሆን እንደሚችል ይጠቁማሉ ።
በሌላ ተረክም ዕንቁጣጣሽን ንግሥተ ሳባ ኢየሩሳሌም ሄዳ ጉብኝቷን ፈጽማ ስትመለስ ንጉሥ ሰሎሞን ብዙ ዕንቁ ለጣጣሽ ‹‹ለችግርሽ›› ይሁን ብሎ መታሰቢያ ከሰጣት ጋር ተያይዞም ይነገራል ።ከልዩ ልዩ ተረኮች መካከል እነ አፈ ሊቅ አክሊሉ ገብረኪሮስ፣ አለቃ ነቢየ ልዑል በተውልን ማስታወሻ ላይ እንደተገለጸው፣ ማክዳ የምትባለው ንግሥተ ሳባ አንድ ዓመት ያህል ቆይታ ከመናገሻ ከተማዋ በገባች ጊዜ ወንዱ በሆታ ሴቱ በዕልልታ ሲቀበላት፣ ሕፃናቱ ደግሞ አበባ፣ ለምለም ቅጠል ይዘው ነበር የተቀበሏት ።
‹‹ሰሎሞን ዕንቁ ለጣጣሽ ሰጠሸ፣ በዓመትሽ እንኳን ደህና መጣሽ፤›› እያሉ ስለተቀበሏት ልምድ ሆኖ ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተላለፈ መጥቷል ።ከጊዜ ብዛት ዕንቁ ለጣጣሽ የሚለውን ‹ለ›ን በመግደፍ ዕንቁጣጣሽ ሆነ ይላሉ ። በዕለቱ ልጆች በየቤቱ እየሄዱ ‹‹ዕንቁጣጣሽ በያመቱ ያምጣሽ›› እያሉ አበባ ያበረክታሉ፣ ሥዕል ይሰጣሉ ።እዚች ላይ በዕንቁጣጣሽ ዋዜማ አዲሱ ዓመት መድረሱን ስለሚያበስረው እንግጫ ማንሣት ይገባል ።እንግጫ የሳር ዓይነት ነው ።በአዲስ ዓመት ዋዜማ ልጃገረዶች መስክ ወርደው የሚነቅሉት ነው። የዕንቁጣጣሽ ብሥራት ነጋሪ ነው ።በአንድ የማይዳሰሱ ቅርሶች ድርሳን ላይ እንዳነበብሁት፣ በዘመን መለወጫ ዋዜማ እንግጫ ሳር በልጆች እየተነቀለ እንደቋጨራ እየተጎነጎነ ጣራ ላይ ተወርውሮ ያድርና ጠዋት ላይ ለዘመን መለወጫ መስከረም 1 ቀን እየተጎነጎነ ራስ ላይ፣ ቡሃቃ አንገት ላይና ሌማት ክዳን ላይ ይታሰራል ።
ቡሃቃ እና ሌማት ላይ የመታሰሩ ምልክትነት ለረድኤትና ለበረከት ሲባል የሚደረግ ነው ።ራስ ላይ የታሰረው ደግሞ ለመስቀል በዓል ተቀምጦ ይቆይና ደመራው ላይ ይታሰርና እንዲቃጠል ይደረጋል ።ለራስ ምታትና ለጤንነት ሲባል በማኅበረሰቡ የሚከወን ነው ። እንግጫ ከአዲስ ዓመት ማብሰሪያ በተጨማሪ የመተጫጫ በዓልም ጭምር ነው ።
አዲስ ዘመን – በዓለም ላይ ኢትዮጵያን ጨምሮ የራሳቸው ዘመን አቆጣጠር ያላቸው አገራት ምን ያህል ናቸው?
መምህር ሔኖክ፡- በርካታ አገሮችና ሃይማኖቶች ቀኖችን፣ ወሮችን እና ዓመቶችን የሚቆጥሩበት የየራሳቸው የዘመን አቆጣጠር ወይም ካሌንደር አላቸው ።በአገራችንም እንደዚሁ። አቆጣጠሮቹም በሦስት ዓበይት የካሌንደር ዓይነቶች ይገለጻሉ። እነርሱም የጨረቃ፣ የፀሐይ እና የጨረቃና ፀሐይ ጥምር አቆጣጠሮች ናቸው ።ባንድ የዳሰሳ መረጃ ላይ እንደተጠቀሰው በዓለም ዙሪያ ከ40 በላይ ካሌንደሮች በአገልግሎት ላይ ይገኛሉ ።በዓለም ካርታ አስደግፎ የቀረበው መረጃ ከአፍሪካ ኢትዮጵያና ግብፅን፤ ከአውሮፓና እስያ ሮም (ጣሊያን)፣ ግሪክ፣ ባቢሎን ፋርስ (ፐርሺያ)፣ ቻይና፤ ከማዕከላዊ አሜሪካ ማያን እና አዝቴክ ተጠቅሰዋል ።
አዲስ ዘመን፡- አንዲት አገር የራሷ የዘመን አቆጣጠር አላት ማለት የሚያስገኘው ጥቅም ምንድን ነው፤ ከሥልጣኔ አንፃርስ እንዴት ይታያል?
መምህር ሔኖክ ፡- በርካታ ጥቅም አለው።የመጀመሪያው በሕይወት ለመኖር የሚያስችሉ መሠረታዊ ነገሮችን ለማሟላት አራቱ ወቅቶችን (ክረምትና መፀው፣ በጋና ፀደይ) የሚገቡበትን ማወቅ አንዱ ግዴታ ነው ። ዝናቡ መቼ እንደሚመጣ፣ መቼ እንደሚተከልና መቼ እንደሚሰበሰብ ለማወቅ በጣም አስፈላጊ ነው ። ብርሃናት የተፈጠሩት ለምልክቶች፣ ለዘመኖች፣ ለዕለታትና ለዓመታት ነው ።ሁሉም የቀን መቁጠሪያዎች በጊዜ ሒደት ለመቁጠር በሚረዱን በሦስት ዑደቶች ወይም ተደጋጋሚ ክስተቶች ላይ የተመሠረቱ መሆናቸውን አስቀድመን አንሥተናል ። እነዚህም ቀኑ – ከፀሐይ መውጫ እስከ ፀሐይ መውጫ ወይም ፀሐይ ከጠለቀች እስከ ፀሐይ መግቢያ፣ ወር-ከሙሉ ጨረቃ እስከ ቀጣዩ ሙሉ ጨረቃ (ወይም ከአዲስ ጨረቃ እስከ ቀጣዩ አዲስ ጨረቃ) እና ዓመት – ከአንዱ በጋ ወደ ቀጣዩ ወይም ከአንዱ ክረምት ወደ ቀጣዩ፣ ወይም ከመፀው እስከ መፀው አሊያም ከፀደይ እስከ ፀደይ ናቸው።
ቀኑ ረዥም ሌሊቱ አጭር፣ እንዲሁም ሌሊቱ ረዥም ቀኑ አጭር የሚሆንበት ገጽታውን ከሥነ ፈለክ አንፃር በመመርመር የተገኘ ነው ። የራስ የዘመን አቆጣጠር መኖር ከአየር ንብረት ጋር ጭምር ራስን አዋሕዶ ለመጓዝ፣ በጀትን ለመመደብ፣ የትምህርት ወቅትን ለማወቅ፣ እቅድ ለመያዝ፣ ለቀዳሽም፣ ለአራሽም ወዘተ እጅግ ጠቃሚ ነው ።ቅዱስ ያሬድ ለዜማው ድርሰቱን ያዘጋጀው በአራቱ ወቅቶች መነሻነት ነው ።መስከረም 1 በክረምት ውስጥ የምትገኝ ያመት መነሻ ናት ።ሰኔ 26 ቀን የገባው ክረምት የሚወጣው መስከረም 25 ቀን ላይ ነው። የስድስተኛው ምዕት ዓመት የነገረ መለኮት ሊቁ፣ ማሕሌታይ ቅዱስ ያሬድ በመጽሐፈ ድጓው ‹‹ኀለፈ ክረምቱ ጸገዩ ጽጌያት ቆመ በረከት!›› – ክረምቱ አለፈ አበቦችም ፈኩ፣ በረከትም ቆመ ይለናል ። እንደ ቅዱስ ያሬድ የዓመት አመዳደብ፣ በውስጡ ልዩ ልዩ ንኡሳን ክፍሎች አሉት ።ከነሱም መካከል የነሐሴ መጨረሻና የጳጉሜን ሳምንት ‹‹ጎሕ፣ ጽባሕ››- ወጋገን፣ ንጋት ይለዋል ።ይህም የአዲስ ዘመን መስከረም የሚጠባበት ጊዜ መድረሱን አመላካች ነው ።
ሌላው ንኡስ ክፍል ከዓመት አውራ መነሻ (ርእሰ ዐውደ ዓመት) መስከረም 1 ቀን እስከ መስከረም 7 (8) ቀን ያለው ‹‹ዮሐንስ›› ሲባል፣ ከመስከረም 9 እስከ 15 ዘመነ ፍሬ ይባላል።‹‹ዮሐንስ›› የሚለው ቃል የተወሰደው በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ከሚገኘውና እግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስን ካጠመቀው ዮሐንስ ነው ።መስከረም 1 ቀን ቅዱስ ዮሐንስ፣ ዕለተ ዮሐንስ መባሉ በተምሳሌታዊ ፍች የመጣ ነው ።
ከአሮጌው ብሉይ ኪዳን ወደ ሐዲስ ኪዳን፣ ወደ ዓመተ ምሕረት መሸጋገሪያ ላይ የመጣው መንገድ ጠራጊው ዮሐንስ ስለሆነ፤ ባህሉ/ ትውፊቱ ከአሮጌው ዓመት ወደአዲሱ መሸጋገሪያዋን ዕለት፣ መስከረም 1 ቀንን በዘይቤ ዕለተ ዮሐንስ እያለ ይጠራዋል ።ከጥንት እስከ ዛሬ በአገልግሎት ላይ ይገኛል። በባሕረ ሐሳባችን መሠረት አዲሱ ዘመን የሚለወጥበት ንጋት 12 ሰዓት ላይ እንጂ እንደ ምዕራባውያን እኩለ ሌሊት (6 ሰዓት) አይደለም ።
አዲስ ዘመን፡- ብዙ ጊዜ መስከረምና ጥቅምትን ‹‹ፀደይ›› ሲባል እንሰማለን ነውን?
መምህር ሔኖክ፡- ስሕተት ነው ። ፀደይ በልግ ሲሆን፣ ከመጋቢት እስከ ሰኔ ይቆያል ።የአደይ አበባና የነፋሱ ወቅት መፀው ሲሆን፤ ፍቺው አበባ ነው። በአውሮፓ በጋ ሲሆን፣ በኛ ክረምት ነው ። ለእነሱ ፀደይ ሲሆን ደግሞ ለኛ መፀው ይሆናል ። ሰው ያለ አጥቢያው ወቅቱን ማዘዋወሩ ነው ያስቸገረን ። በተለይ በአብዛኛው የጥበብ ሰዎች ።ስለዚህ በዚህ ተስተካክሎ መታየት አለበት ።
አዲስ ዘመን፡- መስከረም ለኢትዮጵያውያን ምን ትርጉም አለው፤ የተለያዩ እምነቶች ቢኖሩም ሁሉም በደስታ የሚያከብሩትና ተስፋ የሚጥሉበት ወር ነው። ለመሆኑ አንድ ያደረጋቸው ምንድነው ይላሉ?
መምህር ሔኖክ፡- በፀሐይ ላይ የተመሠረተው የዓመት አቆጣጠር አራቱን ወቅቶች የሚያስገኝልን ነው። ለኛ መስከረም የወራቱ ጌታ የአበቦቹ እመቤት ናት። መምህራኑ እንደሚገልጹት ክረምት የሚያልፍበት፣ ዝናብ የሚቆምበት ፀሐይ የምትጎላበት ወንዞች ንጹሕና የጠራ ውኃ የሚጎርፉበት፣ ምንጮች የሚፈልቁበት የተዘሩት ማሸት የሚጀምሩበት፣ ሜዳዎችና ተራራዎች ሸለቆዎችም በአበባ የሚያሸበርቁበት ነው። ‹‹የመስቀል ወፍ›› የምትባለው የመስከረሟ ወፍ ነባር ቀለሟን ለውጣ የምትታይበትም ነው ።‹‹የመስቀል ወፍና አደይ አበባ ቀጠሮ እንዳላቸው ማን ያውቋል?›› አይደል ያሉት ታላቁ ባለቅኔ መንግሥቱ ለማ ።
መስከረምን የአዲስ ዘመን መባቻ እንዲሆን የተተለመበት ዓቢዩ ምክንያት ከቀድሞው ዘመን አንፃር ሲታይ ታቹ ውኃ፣ ላዩም ውኃ ሆኖ ወገን ከወገኑ ዘመድ ከዘመዱ አለያይቶ የነበረው የክረምቱ ሦስት ወራት አልፎ፣ የተለያዩት የሚገናኙበት የራቁት የሚቀርቡበት በመሆኑ ነው ።ትምህርት ቤት ሰኔ 30 ተዘግቶ በመስቀል ደመራ ማግስት መስከረም 18 ቀን ይከፈት የነበረው ለዚህ ነው ።ስለዚህም እነዚህ ጉዳዮች ሁሉንም ኢትዮጵያውያን ያገናኟቸዋል ።
አዲስ ዘመን- አዲስ ዘመን ሲመጣ ሰዎች ያቅዳሉ ።ይሁን እንጂ እቅዶቹ ወደ ውጤት አይደርሱም ምክንያቱ ምንድን ነው?
መምህር ሔኖክ፡- ማቀድ መልካም ነው ።ነገር ግን መተግበር ሊታከልበት ይገባል ።በእርግጥ ብዙዎቹ ያቀዱትን ሲተገብሩ አይታይም ።ምክንያቱ የተለያየ ሊሆን ይችላል ።ከራስ ድክመት እስከ ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ ችግሮች ያቀድነውን እንዳንተገብረው የሚያደርጉን ምክንያቶች ናቸው ።የአገር ሰላም መደፍረስም እንዲሁ ሌላው መሰረታዊ ችግር ነው ።
አዲስ ዘመን፡- የመጪውን ዘመን ምኞትዎን ቢገልጹልን?
መምህር ሔኖክ ፡- ሁሉም ብሩህ እንደሚሆን ተስፋ አደርጋለሁ። ባሕረ ሐሳብን ጨምሮ አገር በቀል ዕውቀቶች ተገቢው ትኩረት አግኝተው ማየትን እመኛለሁ ።‹‹ታውቅ ዘንድ የዘመን ምሥጢር የምትመረምር አንተ ብልህ ሰው ይህን ዕወቅ፤›› የሚል ጥንታዊ ኃይለ ቃል በድርሳናት ውስጥ ይገኛልና የባሕረ ሐሳብን ልዩ ልዩ አቆጣጠሮችን እንመርምር ።ከክረምት ቀጥሎ የሚመጣው መፀው እንጂ ፀደይ አንበል ።እሱ የመጋቢት ነውና ።‹‹ቀንንና ወርን ዘመንንም ዓመትንም በጥንቃቄ ትጠብቃላችሁ›› የሚለውን መጽሐፋዊ ማስገንዘቢያንም አንዘንጋ ።
አዲስ ዘመን፡- ስለሰጡን ማብራሪያ እጅግ አድርገን እናመሰግናለን።
መምህር ሔኖክ ፡- ክብረት ይስጥልኝ። የከርሞ ሰው ይበለን ።
ጽጌረዳ ጫንያለው
አዲስ ዘመን መስከረም 1 ቀን 2015 ዓ.ም