የተወለደው በ1953 ዓ.ም ነው። የትውልድ ስፍራው ደግሞ በሰሜን ሸዋ ጅሩ ወረዳ እነዋሪ ከተማ ነው። ተፈጥሮ ከነሙሉ ክብሯ በምትገለጥበት ስፍራ የተወለደው የዛሬው እንግዳችን እጆቹ በሸራ ላይ ተአምር የሚሰሩ ናቸው። አንዳንዶች እንደሚሉት እንዲያውም የመዝገቡ ስእሎች ፎቶን የሚያስንቁ እና ልቅም ያሉ ናቸው። መዝገቡ ግን ለስእል ካለው ቀናኢነት የተነሳ እንዲህ አይነት አድናቆትን አይቀበልም። በአንድ ወቅት ከቢቢሲ ጋር በነበረው ቆይታ “በሥልጣኔ ታሪክ ፎቶግራፍ የመጣው ከሥዕል በኋላ ነው፤ ሥዕልን ፎቶግራፍ ይመስላል ማለት ማሳነስ ነው” ሲል የሥነ ሥዕልን ታላቅነት ይሞግታል። የዛሬው ርእሰ ጉዳያችን በዚህ ዘመን ካሉ ድንቅ ሰአሊያን አንዱ በሆነው ሰአሊ መዝገቡ ተሰማ ላይ ነው።
በዘመናችን ካሉ ሰአሊያን ከምርጦቹ ተርታ የሚሰለፈው መዝገቡ ያደገበት መንገድ ቀለማዊ እይታዎችን እንዲስተውል አግዞታል። ተራራው፤ ወንዙ፤ መስኩ፤ እንስሳቱ፤ ወዛም እና ፈርጣማ ሰዎች እና መሰል እይታዎች በመዝገቡ የልጅነት አእምሮ ውስጥ እየታተሙ መጡ። ያን የመሰለ መልክአ ምድር እያየሁ ማደጌ ለኔ እድል ነበር። እስከዛሬም ድረስ የስራዎቹ አነሳሽ ምክንያት እሱ ነው ይላል።
ገና በልጅነቱ የተጠናወተው የስእል ውቃቢ በደብተሩ ላይ ይገለጥ ነበር። ደብተሩ ሁሌም በስእል ያጌጠ ነበር። በተለይም እግር ኳስ ተጫዋች እና ደብተር የያዘ ተማሪ መሳል ደስታው ነበር። ለዚህም ኩርኩም ቀምሷል። ነገር ግን ይህም ሳያርመው ቀርቶ ጭራሽ በመማሪያ ዴስኩ ላይ ስእል ጨመረበት። ይህ ሌላ ቅጣት አስከተለበት። እንዲያም ሆኖ ግን እጆቹ ስእል ከመሳል አላረፉም። ስለዚህም ተማሪዎች ስእል መሳል በከበዳቸው ጊዜ ሁሉ ለእርዳታ የሚጠራው መዝገቡ ነው። ይህን ተሰጥኦውን ለተማረበት ትምህርት ቤት አገልግሎት አውሎት ብዙ የጂኦግራፊ እና ሌሎች የትምህርት አይነት ስእሎችን ስሏል።
የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ሲጨርስ መጥቶ የተቀላቀለው አለ የስነ ጥበብ ትምህርት ቤትን ነው። እዚያ ሲገባ ደግሞ አላማው እንደ ሮል ሜዴል የሚያየው ታደሰ መስፍንን መሆን ነበር። ለከፍተኛ ትምህርት ደርሶ እንደ ዘመኑ አስተሳስብ የሚያበላ ስራ ይመርጣል ሲባል እሱ ግን የስነ ጥበብ ትምህርት ቤት ገባ። ቤተሰቦቹ አልተቃወሙትም። ያልተቃወሙኝ በየዋህነት እሱ የሚያስደስተውን ስራ ይስራ ብለው ስላሰቡ ነው ይላል። በእርግጥም የቤተሰቦቹ ዝምታ ጠቀመው። ተማረ።
የመጀመሪያ ስራው ቤተሰብ የተሰኘ ነው። በአንድ ወቅት ከቢቢሲ ጋር በነበረው ቆይታ ስለዚህ ስእሉ ሲናገር እንዲህ ብሏል። “ገጠር ውስጥ ቤተሰብ የሚለው ሐሳብ በራሱ ሰፊ ነው፤ የቤት እንስሳት ሁሉ እንደ ቤተሰብ አባል ይቆጠራሉ፤ የእገሌ ልጅ እንደሚባለው፤ የእገሌ ፍየል፣ የእገሌ በሬ ይባላል” የሚለው ሠዓሊው ይህንን ለማጉላት ሥዕሉን እንደሠራው ያስረዳል።
መዝገቡ ከአለ የስነ ጥበብ ትምህርት ቤት ከተመረቀ በኋላ እዚያው ለአንድ አመት አስተማረ። ከዚያም የውጭ የትምህርት እድል አጋጠመውና ወደ ሩሲያ ተጓዘ። ኢሊያ ኢፊሞቪች ሬፒን ሌኒነግራድ የስነ ጥበብ ትምህርት ቤትም ተማሪ ሆነ። በስነ ጥበብም ሁለተኛ(ማስተርስ) ዲግሪውን ያዘ። ሲመለስ የስእል እና ቅብ መምህር ሆነ። ከዚያም ለ7 አመታት የስእል ዲፓርትመንት ዲን ሆኖ ከቆየ በኋላ በድጋሚ ወደ መምህርነቱ ተመለሰ።
መዝገቡ እውናዊ (Naturalistic/ Realistic/ Expressionist) የሥዕል አሳሳል ዘዴን ከሚከተሉት ሰዓሊያን በጉልህ ይጠቀሳል። በኢትዮጵያ የሥዕል ታሪክ የትኛው የአሳሳል ዘዴ ተቆናጦ እንደቆየ ለመናገር ቢያስቸግርም ለምሳሌ በደርግ ዘመን የእውናዊ የአሳሳል ዘዴን እንደ አንድ የፕሮፖጋንዳ ጥበብ ለዐሥራ ሰባት ዓመታት ይጠቀሙበት ነበር።
በሠዓሊና ሃያሲ ስዩም ወልዴ ግለ ታሪክ መጽሐፍ (ኩርፊያ የሸፈነው ፈገግታ) በደርግ ጊዜ የሌሎች አገራት መሪዎችን ለመቀበል የመሪዎቹን ምሥል በትልቅ ሸራ ላይ ይሥሉ እንደነበር ተጠቅሷል። ይህንንም ለንግግሩ ዋቢ ማድረግ ይቻላል። እርሱ ግን ገበያውንና ጊዜውን አይቶ ሳይሆን የልጅነት ህልሙ እንደሚመራው ይናገራል።
ተወልዶ ባደገበት አካባቢ ያለው የመንገዱ ጠመዝማዛነት፣ የምንጮቹ፣ የዳገቱ፣ የመስኩ፣ የዕጽዋቱ፣ የከብቶቹ…በልጅነት አዕምሮው መዝገብ ሰፍረዋል፤ ይህም አሁን ለሚከተለው እውናዊ የሥዕል አሳሳል ዘዴ መነሻ እንደሆነው ይገልጻል። በወቅቱ አካባቢውን እንዲያይ፣ እንዲያደንቅ፣ እንዲመረምር፣ የፈለገበት ቦታ እንዲሄድም ቤተሰቦቹ ይፈቅዱለት ነበር። ይህም ከመልክዓ ምድሩ ጋር ያለውን ትስስር አጠናክሮለታል።
ከዚህም ባሻገር የሥነ ጥበብ ትምህርት ቤቱ እውናዊ ሥራዎች እንዲሠሩ የሚጠይቅ ነበር፤ እርሱን አሟልቶ ያልሠራ ተማሪ መቀጠል አይችልም ነበር፤ ስለሆነም የትምህርት ሥርዓቱ ብርታት ሆኖታል። የሥዕል ሥራዎቹ ረቂቅ ስሜቶችና ሥነ ልቦና ይንጸባረቁበታል። “ይህ ግን በአንድ ጊዜ ተሳክቶ የሚመጣ አይደለም” የሚለው መዝገቡ ሁልጊዜ በዝርዝር የሚገለፁ ነገሮችን ከመሣል በፊት “ጥናትና ሙከራ አደርጋለሁ፤ የሰው ባህሪ ከነመልኩ መዋሃዱን በተደጋጋሚ አጤናለሁ፤ ውጤታማ እስከሚሆን መሥራትንም እመርጣለሁ” ብሏል።
የመዝገቡ ስእሎች በጣም ለዝርዝር ጉዳዮች ትኩረት የሚሰጡ በመሆን ይታወቃሉ። ይህ ሁኔታ ደግሞ የበለጠ የሚገለጠው በአንድ ስእሉ ነው። ይህ ስእል መዝገቡ ታዋቂ የሆነበት ሲሆን የስእሉ መጠሪያም ንግስ ይባላል። በ10 ስኩዌር ሜትር ላይ ያረፈውን ይህን ስእል ለመሳል ከ3 አመት በላይ ፈጅቶበታል። ይህ የሆነውም በስእሉ ውስጥ ያሉ እያንዳንዱ ነገሮች ልቅም ተደርገው መሳል ስላለባቸው ነው።
መዝገቡ ስእሎችን ለመሳል የሚወስደው ጥንቃቄ አስገራሚ ነው። እንዲያውም በአንድ ወቅት አድባር የተሰኘ ስእሉን በሚስልበት ወቅት በስእሉ ላይ አንዲት ስንጥር ልትወድቅ ስትል ያን ለማዳን ያደረገው ጥረት የወገብ ጉዳት እንዲያጋጥመው አድርጎት ነበር። በዚህም የተነሳ ሀኪሙ እረፍት እንዲያደርግ አዝዞት የነበረ ቢሆንም እረፍት አልባው መዝገቡ ግን ከሀኪሙ ምክር በተቃራኒ በከዘራ እየተደገፈ ስእሉን ይስል ነበር።
የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች ደራሲዎች፣ ሠዓሊዎች፣ ሙዚቀኞች፤ ሥራዎቻቸውን የሚሠሩበትና ፍላጎት የሚፈጥሩ መልካም አውድ ‘ሙድ’ ይፈልጋሉ። ገጣሚ፣ ደራሲና የመብት ተሟጋች ማያ አንጀሎ ምንም እንኳን ቤት ቢኖራት ለመጻፍ የሆቴል ክፍል ትከራይ ነበር። ጆርጅ ኦርዌል አልጋ ላይ ወይም ሶፋ ላይ በጀርባው ጋደም ማለትን ሲመርጥ በተቃራኒው ቻርለስ ዲከንስ ቆሞ መጻፍ ይመቸዋል። ቪክቶር ሁጎ ልብሱን አወላልቆ እርቃኑን ካልሆነ የሥነ ጽሑፍ አድባር አትጠራውም። ፈረንሳዊው የልቦለድ ጸሐፊ ባልዛክ በቀን 50 ስኒ ቡና ካልጠጣ የጥበብ አውሊያዎች ዝር አይሉለትም ነበር።
መዝገቡስ? “የራሴ ስንፍና፣ የመሥራት ፍላጎት፣ ጥንካሬና ጉድለት ካልሆነ በስተቀር ምንም የሚረብሸኝ ነገር የለም” ይላል። ለመዝገቡ ሥዕሎቹን ለመሥራት የትም መሄድ፣ ምንም ማድረግ አይጠበቅበትም። ከቤተሰቦቹ ጋር ተመካክሮ ፈቃድ በማግኘቱ የሥዕል ስቱዲዮውን የመኖሪያ ቤቱ ሳሎን ውስጥ አድርጓል። ልጆች ቢቦርቁ፣ ዘመድ አዝማድ ቢያወራ፣ ቡና አጣጭ ቢያሽካካ ከጀመረው ሥራ አንዳችም የሚያናጥበው ምድራዊ ኃይል የለም።
የመዝገቡ ስእሎች ውድ ናቸው ይባላል። እንዲያውም ንግስ ለተሰኘ ስእሉ 3 ሚሊየን ብር ተሰጥቶት እምቢ አለ ተብሎ ነበር። እሱ ስለዚህ ተጠይቆ ነገሩ ሀሰት ነው ይላል። እንዲያም ቢሆን ስእሎቹ በትልልቅ ቦታዎች ይገኛሉ። ለዚህም ማሳያ በሸራተን አዲስ እና በሀይሌ ሪዞርት ያሉት ስእሎቹ ናቸው። በሌላ መልኩ ስእሎቹ ከዚህ ቀደም ኤግዚቢሽን ላይ የቀረቡ ሲሆን ተደርጎ በማያውቅ ሁኔታ ንግስ የተሰኘው የስእል ኤግዚቢሽኑ በህዝብ ጥያቄ እንዲደገም ሆኗል። በወቅቱ ኤግዚቢሽኑን ካዩ በኋላ ብዙዎች በመደመም አስተያየት የሰጡ ሲሆን ከተሰጡት አስተያየቶች መሀከል አንድ ሁለቱን እንመልከት።
የመጀመሪያው አስተያየት ሰጪ አንዋር ሙሰማ የተባለ ሰው ሲሆን እሱ እንዲህ ብሏል “መዝገቡ ተሰማ የስዕል ትምህርቱን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የስዕል ትምህርት ቤት ቀጥሎም ባሕር ተሻግሮ አገራት አቆራርጦ በሩሲያ አገር የተከታተለ ሲሆን ወደ አገሩ በመመለስም አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ የስዕል ትምህርት ቤት የስዕል ጥበብን በማስተማር ሙያ ተሰማርቷል። በመኖሪያ ቤቱ ረጅም ጊዜ ወስዶ በትጋት የሚሰራቸው የምርምርና የሐሳብ ንድፎቹ ሰፊውን ጊዜ ተሰጥቷቸዋል። እነዋሪ ተወልዶ ያደገው ሰዓሊው የልጅነት ዕድገቱ ለዛሬው ባላገርና የባላገር ማንነትን ሸጣው፣ የመልከዐ ምድር ንድፎቹ መነሻ የባላገር ሕይወት ላይ የማተኮር ተመስጦው የዛ የትናንቱ ውጤት ሆኖ ተከትቧል።
መልከዐ ምድርን ያሰፈረባቸው ስዕሎቹ ብዙ ጎብኚዎችን ፎቶግራፍ ነው ወይስ እውነት ሸራ ላይ በቀለም የተሰራ ስዕል በማለት ደጋግመው ይጠይቁ ዘንድ አስገድዷቸው አስተውያለሁ። ከወጣት ሸምገል እስካሉት፤ ለጥበብና ስዕል ቅርብ ከሆኑት በሌላ የሙያና የትምህርት ዳራ ለሚገኙት የጉብኝትና የመወያያ አጀንዳ ሆኖም አስተውያለሁ፤ ከአገር ውስጥ እስከ ባሕር ማዶ ሰዎች ጥበቡን ሲኮመኩሙም ነበር።
በትክክል መመስከር የሚቻለው አንድ ነገር ሁሉም ሰው በመደመም እጁን በአፉ መጫኑን ነው። የገራልታ ምት / ገራልታስ ሪዝም/፣ ግለት፣ እጥፋት፣ የተዘረጋ፣ ላል፣ ህልመኛው፣ ኩሬ፣ የአለት ገጽታ፣ የጎንደር አበባ እና ሌሎችም በርካቶች የጠቢቡ የሸራና ቡርሽ ምትሃት የተገለጠባቸው ስራዎች ናቸው።”ብሏል።
ሌላኛው አስተያየት ሰጪ ሸንቁጥ አየለ የሚባል ሲሆን የመዝገቡን ኤግዚቢሽን ከተመለከተ በኋላ እንዲህ ብሏል “የስዕል ኤግዚቢሽኑን ገብቼ ስመለከተው ስሜትን ጭምድደው የሚይዙ፣ ሀሳብን የሚሰርቁ የሚያመራምሩ እና እጅግ መሳጭ የሆኑ ስዕሎችን ተመለከትሁ:: መቼም የዚህ አርቲስት ችሎታ ነብሴን ሰርቆብኛልና ለሁለተኛ ጊዜ በርካታ ጓደኞቼን ሰብስቤ ተመለከትኩት:: በየስዕሉም ላይ የሀሳብ ልውውጥ አደረግንበት::
መቼም ግሩም ድንቅ ነው ከማለት የዘለለ ቃላት ብፈልግም አጣሁ:: አንዱ ስዕል ለተለያዩ ሰዎች የሚያስተላልፈው ትርጉም እጅግ አስገራሚና አስደማሚ ነበር:: በስዕል ኤግዚብሽኑ ላይ የተሳተፉ ሰዎችን አስተያየት አደምጥም ነበር:: ተመልካቹ ሁሉ እጅግ ተመስጦ ነበር:: ደግሞም እንደገባው ሁሉም በተጸሞና ባግራሞት ይመራመር ነበር:: አንዳንዱም ይከራከር ነበር:: ሁሉም ሰው ግን በጣም ተመስጦና አድናቆት ውጦት ነበር::”
በስነ ጥበብ ትምህርት ቤት ካገኛት ባለቤቱ ወ/ሮ ሄዋን ገ/እግዚአብሄር ጋር ትዳር የመሰረተው መዝገቡ የሶስት ልጆች አባት ሲሆን ትዳር የሰውን ልጅ ሙሉ ያደርጋል ይላል።
አቤል ገብረኪዳን
አዲስ ዘመን ግንቦት 28/2014