ባለሙያዎች ወርቃማ ድምጽ ይሉታል ድምጹን። አስገምጋሚ ድምጽ አለው። ሰውነቱን ላየ ሰው ድምጹ ከሱ የሚወጣ አይመስለውም። በዚህም የተነሳ ብዙዎች በትወና የሚያውቁትን ያህል በዚህ ጆሮ ገብ ድምጹ ለይተው ያስታውሱታል። የዛሬው እንግዳችን አንጋፋው ተዋናይ ዮናስ ጌታቸው ነው።
የበረሀዋ ንግስት በምትባለው ድሬዳዋ ከተማ ተወለደ። ወቅቱም ጥቅምት 23 ቀን 1962 ዓ.ም ነው። አባቱ አቶ ጌታቸው ውብሸት እና እናቱ ዘውድነሽ ተፈራ ከወለዷቸው ስድስት ልጆች የመጀመሪያው ዮናስ ሆነ። ከሱ በታች ሌሎች ሁለት ወንዶች እና ሶስት ሴት ልጆች አሉ።
አባት እና እናቱ ነጋዴ ነበሩ፤ ነገር ግን በጊዜ ሂደት የንግዱ ሁኔታ አላዋጣ ሲል ወደ ተቀጣሪነት ዞሩ። አባት ድሬዳዋ ምድር ባቡርን እናት ድሬዳዋ ጨርቃ ጨርቅን ተቀላቀሉ። የመጀመሪያ ልጃቸው ዮናስ ደግሞ የንግድ ሥራውን መሞካከር ቀጠለ። በተለይም 1982 ላይ ብሔራዊ ፈተናን ከወሰደ በኋላ ሥራው ይህ ነበር።
የአራተኛ እና አምስተኛ ክፍል ተማሪ በነበረበት ወቅት በክፍል ውስጥ እንደማንኛውም ታዳጊ ይሳተፍበት ከነበረው ሙዚቃና ውዝዋዜ በቀር ለጥበብ ዝንባሌ ኖሮት የማያውቀው ዮናስ፣ ከሁለተኛ ደረጃ መልቀቂያ /ማትሪክ / ፈተናው በኋላ ግን ያልጠበቀው የጥበብ በር ተከፈተ።
በሚኖርባት ድሬዳዋ ከተማ አጎናፍር ወዳጆ የሚባል የጥበብ ሰው ተውኔት እያዘጋጀ ነበር። ነገር ግን ተውኔቱ ላይ ዋነኛ ተዋናይ የነበረው ልጅ ቴአትሩ ለሕዝብ ሊቀርብ ቀናት በቀሩበት ወቅት ቤተሰቦቼን ልጠይቅ ብሎ ከድሬዳዋ ወደ ትውልድ ስፍራው ይሄዳል።
ይሄኔ የቴአትሩ ደራሲ የሚያደርገው ሰው ግራ ገባው። ስለዚህም ወደ ዮናስ መጣ። ተውንልኝ አለው። ዮናስ ከዚህ ቀደም ስለ ቴአትርም ሆነ ስለ ሌላ የጥበብ ጉዳይ እውቀት ባይኖረውም እሺ አለ። ደራሲው ዮናስን ወስዶ አሸዋ ላይ የመድረኩን ገጽታ ስሎ “ይሄ ሳሎን ነው ፤ ይሄ መኝታ ቤት ነው” ብሎ መግቢያ እና መውጫውን አሳየው። ቃለ ተውኔቱንም በቀናት ውስጥ ከነስሜቱ አጥንቶ ተወነ። ዮናስና ጥበብ ፤ ዮናስ እና ቴአትር ፤ ዮናስና መድረክ ተዋወቁ ፤ ተዋደዱም። ከዚያ በኋላ ትወናው ላይ በረታ። ሌሎች ተውኔቶችንም ሠራ።
ዮናስ እና ቴአትር ድሬዳዋ ላይ የጀመሩት ፍቅር እየጦፈ ሲሄድ ይሳተፍበት የነበረው ወጋየሁ ንጋቱ የተሰኘ የቴአትር ክበብ እንቅስቃሴ መቀዛቀዝ ያዘ። ስለዚህም ዮናስ እና ጓደኛው ድሬዳዋን ትተው የቴአትርም ሆነ የሌሎች ነገሮች መናኸሪያ ወደነበረችው አዲስ አበባ መጡ።
አንድ ቀንም ወደ ባህል ማዕከል ጎራ አሉ። ሲደርሱ ተዋንያን በሙሉ ልምምድ ላይ ናቸው። ቁጭ ብለው ልምምዱን መከታተል ያዙ። ይሄኔ ደራሲው እና ዋና አዘጋጁ ጌታቸው ታረቀኝ ወደ እነሱ መጣ። ምን እየሠራችሁ ነው ብሎ ጠየቀ። ዮናስ እና ጓደኛውም ከድሬዳዋ እንደመጡ ፤ ቴአትርን እንደሚወዱ እና ቴአትር ማየት ስለናፈቃቸው ወደ እዚህ እንደመጡ ይነግሩታል።
እሱም ጥቂት ጥያቄዎችን ካቀረበላቸው በኋላ የየኔ ቢጤ ገጸ ባህሪ ተውነው እንዲያሳዩ ጠየቃቸው። ተውነው አሳዩት። በማግስቱ ለገጸ ባሕሪው የሚሆን ልብስ ለብሰው እንዲመጡ አዘዛቸው። ለብሰው መጡ። የተውኔቱ አካል ሆነውም ተሳተፉ። ከዚያ በኋላ ሌላ ድርሰት እንዲያጠኑ ሰጣቸው። በ15 ቀን ውስጥ አጥንተው ጨረሱ። 1984 ላይ ያ የተለማመዱት ቴአትር ሃገር ፍቅር መድረክ ላይ ቀረበ። ነገሮች በዚህ ቀጠሉና ዮናስ በተውኔት 50 ብር በወር 200 ብር እየተከፈለው ቀጠለ።
ከዚያም በ1987 አ.ም በአዲስ አበባ ቴአትር እና ባህል አዳራሽ ተቀጠረ።በዚያ እየሠራ እያለ ሃገር ፍቅር ቴአትር የደረጃ እድገት ወጣ። በቴአትር እና ባህል አዳራሽ 370 ብር ይከፈለው የነበረው ዮናስም ሃገር ፍቅር በ50 ብር ጭማሪ 420 ብር ተከፋይ ሆኖ ገባ። የትወና ሕይወቱም ከፍተኛው ደረጃ ላይ ደረሰ።
1989 ላይ ግን ዮናስ ከሚሠራበት ቴአትር ቤት ተሰናበተ። ወደ ትውልድ ቦታው ድሬዳዋም ተመለሰ። ድሬዳዋ ሲመለስ ዝም ብሎ አልተቀመጠም። ሕጻናትን እና ወጣቶችን ሰብስቦ ቴአትር ማስተማር ጀመረ። ቴአትሮች እንዲቀርቡም አደረገ። አንድነት የተሰኘ የቴአትር ክበብም አቋቋመ። ላሳደገችው ድሬዳዋ በሙያው ውለታዋን ለመመለስ ሞከረ።
ከሥራው ከተሰናበተ ከ8 ወር በኋላ ከአዲስ አበባ ተደወለለት። ና ቅጥር ወጥቷል ተባለ። መጥቶ በድጋሚ ተቀጠረ። ከዚያም በኋላ በመሐል ለ5 ዓመታት በሕጻናት እና ወጣቶች ቴአትር ቤት ከነበረው ቆይታ ውጭ ጠቅላላ የሙያ ሕይወቱ በሃገር ፍቅር ቴአትር ቤት ውስጥ ነው።
ዮናስ ተዋናይነቱ ላይ እንከን አይወጣለትም። ከዚህም በላይ ቴአትርን በመጠገን እና በማሳደግ ረገድም ጎበዝ ነው። ይህ ዘርፍ በባለሙያዎቹ አንደበት ሀኪመ ተውኔት (ፕለይ ዶክተር) ይባላል። ተውኔቱ ላይ ያለውን ክፍተት ማስተዋል እና ያንን ጠግኖ የማሻሻል ሥራ ማለት ነው።
በዚህ ዘርፍ በርከት ያሉ ሥራዎችንም ሠርቷል። የዚህ መነሻው አንድ ቀን አለቃው ጌታቸው ታረቀኝ የዩኒቨርሲቲ ምሩቃን የሆኑ ተዋንያን ድርሰት ጽፈው እንዲያመጡ አዘዘ። ጽፈው አመጡ። ከዚያም አስተያየት እንዲሰጥበት ሲቀርብ ሁሉም አንጋፋ ተዋንያን ቴአትሩ ጥሩ ነው አሉ። ዮናስ ግን ቃለ ተውኔቱ ያለበትን ክፍተት ዘርዝሮ 11 ገጽ ሂስ ጽፎ መጣ። ይሄኔ ሁሉም በዮናስ ሀሳብ ስለተስማሙ ለምን እሱ እንደ አዲስ አይጽፈውም አሉ፤ ተሰጠው። በድጋሚ አስተካክሎ ጽፎ አመጣ። የመጀመሪያ የቴአትር ሕክምናውንም በዚህ መልኩ አከናወነ።
ቆየና ሌላ ዳና በተሰኘ ተውኔት ላይም ይህን ጥበቡን ተጠቀመ። እንዲህ እንዲህ እያለ በተውኔት ሐኪምነቱ በረታበት። ሌሎችንም ሠራ። ዮናስ እንደሚለው ከሆነ ብዙውን ጊዜ ደራሲዎች ተውኔትን ሲያዘጋጁ ሁሉንም በራሳቸው ልክ ይቃኟቸዋል። በዚህም የተነሳ ገጸባህሪው እና የሚናገረው ንግግር ያለመጣጣም ችግር ያጋጥማቸዋል። ስለዚህም እሱ እንዲህ አይነት ግድፈቶችን ሲያይ በተውኔት ሐኪምነቱ ደራሲውን ከገጸ ባሕሪው የማውጣት እና ገጸ ባሕሪው ራሱን ችሎ እንዲቆም የማድረግ ሥራ ይሠራል። ከዚህም በተጨማሪ ታሪኩ በሚፈለገው ልክ ሴራ ሲጎድለው ፤ ጡዘት ላይ መድረስ ሳይችል ሲቀር ወይም መሰል ቴክኒካዊ ግድፈት ሲኖረው የተሰጠኝን ብቻ ልሥራ ከማለት ይልቅ ተቀብሎ ማስተካከል የሚችለውን ያህል ይሠራል።
የቼዝ ዓለም ፤ የስልጣን ማደጎ ፤ ፎርፌ እና በርካታ ቴአትሮችን በተዋናይነት የሠራው፤ ብዙ ተውኔቶችን ያከመው እና በሬዲዮም ሳቤላ እና ሌሎች ድርሰቶችን በወርቃማ ድምጹ የተወነው ዮናስ በቴሌቪዥንም ብዙዎች ያውቁታል። ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ይበልጥ የተዋወቀበትም እምአእላፍ በሚል ገጸ ባሕሪ የተወነበት የማለፊያ ጉዞ የተሰኘ የቴሌቪዥን ድራማ ነው።
ከዚያም በኋላ ማን ገደላት ፤ በዚህ መንገድ አለ እና ሌሎች በርካታ ሥራዎችን ሠርቷል። በሕዝብ ዘንድ ከፍተኛ ተወዳጅነት በነበራቸው የመስኮት አጫጭር የቴሌቪዥን ድራማዎች እንዲሁም በጥላሁን ዘውገ እና አለልኝ መኳንንት ይዘጋጁ የነበሩት ስንቅ ተከታታይ አጫጭር የቴሌቪዥን ድራማዎች ላይ በደራሲነት እና በተዋናይነት ተሳትፏል።
ዮናስ ብዙም ያልገፋበት የትወና ዘርፍ የፊልም ትወና ዘርፍ ነው። ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ እሱ በስክሪፕት ላይ የሚሰጠው ሂስ ነው። ፊልም እንዲሠራላቸው የሚፈልጉት ሰዎች የሚሰጡት እሱ እንዲተውንላቸው የሚፈልጉትን የፊልሙን ክፍል ብቻ ሲሆን እሱ ግን ለመሥራት ከመስማማቱ በፊት ሙሉውን ስክሪፕት እንዲሰጡት ነው የሚፈልገው። በዚህ ከብዙዎች ጋር መስማማት ስለማይችልም ብዙ ፊልሞች ላይ አልተሳተፈም።
ዮናስ እስካሁን ላጤ ነው። ለዚህም እንደ ምክንያት የሚያነሳው የኑሮውን አለመመቻቸት ነው። ከ1992 ጀምሮ ቤት እንዲሰጠው ለቀበሌ ጥያቄ እንዳቀረበ ነገር ግን ያመለከተበት ቀበሌ ሁሌም ያስገባው ማመልከቻ ጠፋ እንደሚባል ይናገራል። በአሁኑ ወቅት በሚሠራበት ሀገር ፍቅር ከታክስ በኋላ የሚደርሰው ገንዘብ 4100 ብር እንደሆነ የሚናገረው ዮናስ ለቤት ኪራይ 4ሺ ብር እንደሚከፍል ይናገራል። በዚህም የተነሳ አሁን ልጅ በመውለጃ ጊዜዬ አላገባሁም ይላል። ለከርሞው ግን እቅዱ ማግባት እንደሆነ ይናገራል።
ዮናስን የእረፍት ቀንህን በምንድን ነው የምታሳልፈው አልነው። ”እኔ ከእሁድ እስከ እሁድ እዚህ ነኝ። ብዙም ማኅበራዊ ሕይወት የለኝም። እዚሁ ተውኔቶችን ስጽፍ ነው የምውለው። ”ይላል። እቅዱም ሁለት የሙሉ ጊዜ ተውኔቶችን መጻፍ እና ትዳር መያዝ እንደሆነ ይናገራል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ዮናስ በቅርቡ የቴአትር ሕይወቱን አደጋ የሚከት ክስተት አጋጥሞት ሰሞኑን የመገናኛ ብዙኃንን ትኩረት ስቦ ነበር። ነገሩ የተከሰተው ታኅሳስ 28 ቀን 2012 ቀን ነው። እንደተለመደው ሃገር ፍቅር ቴአትር አምሽቶ ወደ ቤቱ ሲሄድ ገዳም ሰፈር በሚገኘው መኖሪያ ቤቱ በር ላይ በወሮበሎች አንገቱ ላይ ጉዳት ደርሶበት ገንዘቡን እና ስልኩን ይቀማል።
በወቅቱ ከተፈጠረው ክስተት በኋላ መለስተኛ ሕክምና ቢያደርግም፣ በጊዜ ሂደት ያ ገጠመኝ የጉሮሮው አንደኛ ክፍል እንዳይሠራ በማድረጉ በሚፈልገው እና ለመድረክ በሚመጥን መልኩ ድምጽ ማውጣት እንዳይችል በማድረጉ ከሚተውንበት ተውኔትም እንዲወጣ አድርጎታል። በአሁኑ ወቅት በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሕክምናውን እየተከታተለ ሲሆን፣ ሐኪሞችም ወርቃማውን ድምጹን ለማቆየት ጥረት እያደረጉ ናቸው። ሕክምናውን በአግባቡ ለመከታተል ግን የሕዝብን ድጋፍ ይሻል።
(አቤል ገ/ኪዳን)
አዲስ ዘመን ግንቦት 7 ቀን 2014 ዓ.ም