በፋሽን ኢንዱስትሪው ቀድመው ብዙ የተራመዱ አገራት ከዘርፉ ማግኘት የሚገባቸውን ትሩፋት ከሁሉ ቀድመው ተቋድሰዋል። አገራት ለኢኮኖሚያቸው ትልቅ አስተዋፅዖ ማበርከት የሚችለውን የፋሽን ኢንዱስትሪ ለማሳደግ ቢሠሩ ተጠቃሚነታቸው አያጠያይቅም። በዘርፉ አገራዊ ገቢያቸውን ያሳደጉ የአውሮፓና ሰሜን አሜሪካ አገራት ለፋሽን ኢንዱስትሪው ከፍተኛ ትኩረት ሰጥተው በመሥራታቸው እንደሆነ ይነገራል።
እንደኛ ባሉ አገራት ደግሞ ፋሽን ገና በትውውቅ ደረጃ ላይ ይገኛል። እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ሰፊ የሕዝብ ቁጥር ባላቸው፣ የበርካታ ባህል ባለቤት በሆኑና በወጣት ዕድሜ ላይ ያሉ ቁጥሩ ከፍተኛ የሆነ አምራች ዜጋ በሚገኝባቸው አገራት ፋሽንን እንደ መልካም አጋጣሚ ተቆጥሮ ቢሠራበት የሚያስገኘው ውጤት ከፍተኛ ነው።
በአገር ደረጃ አሁን ላይ ከሚታዩ ተናጥሏዊ ጥረቶች ባሻገር ለዚህ ዘርፍ የሚገባውን ትኩረት የተሰጠው አይመስልም። ለዚህም ማሳያው የፋሽን ዘርፉ የእድገት ሁናቴ ነው። በእርግጥ በአገር ደረጃ ሲለካ ዘርፉን የማዘመንና የማሳደግ ተግባር ላይ የጎላ እንቅስቃሴ ባይታይም በግልጥ ጥረት ወደ ፋሽን ዘርፍ ገብተው ታላቅ ውጤት የተቀዳጁ ኢትዮጵያውያን በመበራከት ላይ ይገኛሉ። በዛሬ የፋሽን ገፃችን ወጣት የፋሽን ዲዛይን ባለሙያዎች በፋሽን ዘርፍ እያደረጉት ያለውን እንቅስቃሴ ለማየት ወደናል።
እራሳቸውን ብሎም አገራቸውን በዘርፉ ወደፊት ለማራመድ ቆርጠው የተነሱ ወጣት ዲዛይነሮች ናቸው። ያለሙትን ለማሳካት ሁሌም ግብ አስቀምጠው ለዚያ የሚያዳርሳቸው መንገድ ጀምረዋል። ሁሌም እራሳቸውን በማብቃት ላይ የሚገኙ፣ ለህልማቸው መሳካት ያልተቋረጠ ጥረት የሚያደርጉት ወጣቶቹ ዲዛይነሮች በፀሎት ዘውገና ዳናዊት አለማ ይባላሉ። ወደፊት በፋሽን ኢንዱስትሪው መስክ ርቀው ለመሄድ ያለሙ የራሳቸውን ብራንድ በዓለም ገበያው ለማስተዋወቅና የኢትዮጵያን ባህል የሚያንፀባርቁ ዘመናዊና ተመራጭ አልባሳት ሠርቶ በማቅረብ ላይም ይገኛሉ።
የፋሽን ኢንዱስትሪውን ተቀላቅለው በግል ጥረታቸው ፋሽንን ለማሳደግ የሚታትሩ ዲዛይነሮቹ የራሳቸውን አዳዲስ ፈጠራ በመጠቀም ተጨባጭ የሆነ ለውጥ በማስመዝገብ ላይ ይገኛሉ። ሜክሲኮ አካባቢ በሚገኘው ክሬቲቭ ሃብ ለሙያቸው የሚያገለግላቸውን ስልጠና ሲወስዱ አግኝተን አዋራናቸው። ከዲዛይነሮቹ ጋር በነበረን ስለ ፋሽን ኢንዱስትሪው እንቅስቃሴ፣ ስለ የፋሽን ዲዛይን ሥራዎቻቸውና ሙያውን በተመለከተ አጠቃላይ ያላቸውን አስተያየት አጋርተውናል።
ዳናዊት አለማ የ `ዳን ክሎዚንግ` መስራችና ዲዛይነር ስትሆን የራሷ ፈጠራ የታከለባቸው አዳዲስ ፋሽን ዲዛይን አልባሳት ሠርታ በማቅረብ ላይ ትገኛለች። ከሁለት ዓመት በፊት በመሠረተችው ዳን ክሎዚንግ የተለያዩ መድረኮች ላይ ሥራዎቿን አቅርባ፤ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሳየች ባለችው ለውጥ ተቀባይነትን አግኝታለች። ማህበረሰቡ አገራዊ ምርቶችን እንዲጠቀም ኢትዮጵያዊ ባህልን የሚያንፀባርቁ አልባሳት ትኩረቷን እንደሚስብዋትና እሷም መሰል አልባሳት በመስራት ለገበያ ታቀርባለች።
ማህበረሰባችን ፋሽን ላይ ያለው ምልከታ ብዙ ይቀረዋል የምትለው ዳናዊት ግንዛቤ የመፍጠሩን ሥራ ለመሥራትም እቅድ እንዳላት ከውጭ የሚገቡ አልባሳት በማስቀረት በሰዎች ተመርጠውና ተወደው የሚለበሱ አልባሳት በመሥራት ለገበያ ለማቅረብ እየሠራች ትገኛለች። ፋሽን ዲዛይን እጅግ በጣም ጠቀሜታ ያለው ዘርፍ እንደመሆኑ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል የምትለው ዳናዊት በመንግሥትና በግል ተቋማት ዘርፉን ለማንቃት ጥረቶች ሊደረጉ እንደሚገባም አስተያየቷን ታጋራለች።
በተለይ ሙያተኛው የፋሽን ዲዛይን በኢትዮጵያ ውስጥ ለማሳደግ በጋራ ጥረት ማድረግ እንዳለበት የሚትገልፀው ዲዛይነሯ ሙያዊ የልምድ ልውውጥ በማድረግና በመተጋገዝ ዘርፉን መለወጥና ወደተሻለ ደረጃ ማድረስ እንደሚቻል ትገልፃለች።
ሙያዋን ለማሳደግ የተለያዩ ስልጠናዎች በመውሰድ ላይ መሆኗን የምትገልፀው ዳናዊት ፋሽን ሁሌም አዳዲስ ነገር የሚንፀባረቅበት በመሆኑ እራሷን ለማብቃት ጥረት ታደርጋለች። ገና ለእድገት ድክ ድክ በሚለው የፋሽን ኢንዱስትሪ ውስጥ የራሳቸውን አሻራ ለማሳረፍና በእድገቱ ውስጥ የበኩላቸውን ሚና ለመወጣት ጥረት ከሚያደርጉ ዲዛይነሮች መካከል አንዷ የሆነችው ዳናዊት አለማ በፋሽን ኢንዱስትሪው የራሷን አሻራ ለማሳረፍ ጥረቶቿን ቀጥላለች።
ዲዛይነር በፀሎት ዘውገ ገና ልጅ ሆና ነበር ሳታውቀው ሙያውን መውደድና ወደዚያ የሚያቃርባት ሙከራ ስታደርግ ያደገችው። ልጅ ሆና አሻንጉሊት ላይ የተለያዩ ልብሶችን በመስፋትና ወረቀት ላይ ዲዛይኖችንና ምስሎችን መሥራት ታዘወትር ነበር። ዛሬ ላይ እራሷን ብቁ አድርጋ የተለያዩ ፋሽን አልባሳትን በማዘጋጀት ለደንበኞቿ የምታቀርበው ዲዛይነር በፀሎት በሥራዎቿ ውስጥ አገራዊ ባህልን የሚገልፁ ኢትዮጵያዊነትን የሚያንፀባርቁ ዲዛይኖችን በስፋት ይስተዋላል።
የራሷ «ዘመናይ ክሎዚንግ» የተሰኘ የፋሽን ዲዛይን ብራንድ መስርታ በመሥራት ላይ ስትሆን በዚህም የተለያዩ መድረኮች ላይ የመሳተፍና ሥራዎቿን የማቅረብ ዕድል ገጥሟታል። ሥራዎቿን በተለያዩ መድረኮች ላይ በማቅረብ በፋሽን ወዳጆች የተወደዱላት ዲዛይነር በፀሎት ሥራዎቿን የተመለከቱ ደንበኞቿ የሰጧት አስተያየት ይበልጥ ጠንክራ እንድትሠራ ብርታት ሆኗታል።
የዘመናይ ክሎዚንግ መስራች የሆነችው ዲዛይነር በፀሎት ወደፊት አገራዊ ምርቶችን በማሳደግና ጥራታቸው በመጨመር ለውጭ ገበያ የማቅረብና ተወዳዳሪ የማድረግ እቅድ ይዛ እየሠራችም ትገኛለች። በተለይም አዳዲስ ፈጠራዎችንና በሰዎች ዘንድ ተወዳጅ የሆኑ ጥራታቸውን የጠበቁ ኢትዮጵያዊ ቀለም ያላቸው አልባሳት በሥራዎቿ ታዘወትራለች።
በሙያው ላይ ከሚታዩ ችግሮች ውስጥ የግብዓት እጥረትና ገበያው ላይ የሚፈልጉት መስሪያ ቁሳቁሶች እጥረት ዋንኞቹ መሆናቸውን የምትገልፀው በፀሎት ይህንን መፍታት ቢቻል የተሻሉ ሥራዎች መስራትና ፋሽንን ማሳደግ ይቻላል። ለ6 ዓመታት ያህል በፋሽን ዲዛይን ሙያና ለዚሁ ሙያ የሚጠቅሟትን በትምህርትና ስልጠና ስትወስድ የቆየችው በፀሎት፤ ሙያው እንዲያድግ ከተፈለገ ሙያተኛው የሙያውን ስነምግባር በጠበቀ መልኩ ሥራቸውን ሊሠሩ እንደሚገባ ትገልፃለች። የአገራችን ዲዛይነሮች ለአገራቸው ባህል ትኩረት በሥራቸው እንዲያንፀባርቁትና ሙያውን በማክበር ለሙያው እድገት በጋራ እንዲሠሩ መክራለች።
ኢትዮጵያን በዘርፉ የተሻለ ደረጃ ላይ ለማድረስ ብርቱ ጥረት ላይ መሆኗን የምትገልፀው በፀሎት ማኅበረሰቡ ለአገራዊ ምርቶች ዋጋ በመስጠት በአገራችን በዲዛይነሮች የሚሠሩ አልባሳት እንዲጠቀም፤ በዚህም አገርንና ሙያውን ለማሳደግ እንደሚረዳ መልዕክቷን አስተላልፋለች።
ለአገራዊ ገቢ ከፍተኛ ጠቀሜታ ያለው የፋሽን ኢንዱስትሪ እድገት ይፋጠን ዘንድ እየተደረገ ካለው ጥረት ባሻገር እንደ በፀሎትና ዳናዊት ያሉ ዲዛይነሮች በግል ተነሳሽነት የሚያደርጉት ያልተቋረጠ ጥረት የሚደነቅ ነው። እነዚህ ወጣት ዲዛይነሮች ነገ የተሻለ ቦታ ላይ ለመድረስ የሚያደርጉት ዘርፈ ብዙ ጥረት በመደገፍ ለአላማቸው መሳካት የሚመለከተው አካል እገዛውን እንዲያደርግ መልዕክታችንን እናደርሳለን። ለወጣቶቹ ዲዛይነሮች ተግባራችሁ የሚደነቅ ነውና በርቱ ማለት ወደድን፤ አበቃሁ ቸር ይግጠመን።
ተገኝ ብሩ
አዲስ ዘመን መጋቢት 26/2014