ልጅነታቸው ካልተሰረቀ ሰዎች መካከል አንዱ ነኝ” ይላል ስለ ልጅነቱ ሲናገር። የተወለደው የዛሬ 64 ዓመት በያኔው ቃሉ አውራጃ ኮምቦልቻ ከተማ ውስጥ ነው። አባቱ አቶ ማሞ እና እናቱ ወ/ሮ ጣይቱ አሊ አማኑ ከወለዷቸው አምስት ልጆች መካከል የመጀመሪያው ነው። መጋቢት 23 ቀን 1949 ዓ.ም ቀን ነው የተወለደው።
”ነጻ እና አቃፊ ከሆነ ማህበረሰብ ነው የተወ ለድኩት” የሚለው ተስፋዬ ይህም ልጅነቱ ውብ እንዲሆን እንዳገዘው ይናገራል። እርግጥም ተስፋዬን ያሳደገው ማህበረሰብ ለየት ያለ ነው። በዝና የሚነገረው የወሎ ማህበረሰብ መገለጫ ሁሉ በእነ ተስፋዬ ቤተሰብ ውስጥ ይታያል።
ኩታበር እና ተሁለደሬ ውስጥ የሚኖሩት የእናቱ ዘመዶች በአብዛኛው ሙስሊሞች ናቸው። የነተስፋዬ ቤተሰብ ደግሞ ክርስቲያን ነው። ተስፋዬ ራሱም ድቁና ላይ ባይደርስም ዳዊትን በአግባቡ የደገመ ልጅ ነበር።
የተስፋዬ እናት ወለዬ ሲሆኑ አባቱ ደግሞ የሸዋ ኦሮሞ ናቸው። ትውልዳቸውም አዋሽ መልካሳ ነው። የአውራ ጎዳና ሰራተኛ የሆኑት ጋሽ ማሞ ወ/ሮ ጣይቱን ወደድው ወሎ ገቡ። አልተመለሱም። ተስፋዬን እና ሌሎች አራት ልጆቻቸውን ወልደው ከወ/ሮ ጣይቱ ጋር በፍቅር ወሎ ውስጥ ኖሩ። ተስፋዬና ወንድምና እህቶቹም ቦርቸሌ በሚባል የኮምቦልቻ ሰፈር ውስጥ የቦርከና ወንዝ ውስጥ እየዋኙ አደጉ።
ተስፋዬ እንዲህ ባለ ባለብዙ ቀለም ቤተሰብ እና ማህበረሰብ ውስጥ ተወልዶ ማደጉም ነው ልጅነቱ እንዳይባክን ያደረገው።
ትምህርትና የሥራ ዓለም
ደህና ተማሪ ነበር።የመጀመሪያ ደረጃውን ትምህርት እዚያው ኮምቦልቻ ከተማረ በኋላ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ ደሴ ወ/ሮ ስህን ትምህርት ቤት አጠናቀቀ። ከዚያም ወደ ጎንደር ተሻግሮ ጤና ጥበቃ ኮሌጅ ገብቶ መለስተኛ የጤና ትምህርቱን ተማረ።
ከዚያም ወደ ኤርትራ አሰብ ለሥራ ተሻገረ።ከአሰብ ወደ አስመራ ፤ ከአስመራም በአንቶኖቭ አውሮፕላን ተጭኖ ዘላቂ ማረፊያው ወደ ሆነችው አዲስ አበባ መጣ።ጳጉሜ 2 ቀን 1973 ቀን አዲስ አበባ ሲገባም ማረፊያው ኬንያ ኤምባሲ አቅራቢያ ሆነ።
በአቃቂ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ በህክምናውም በርእዮተ ዓለም ባለሙያ ሆኖም መስራት ቀጠለ። ከዚያም በኋላ ከ1977ቱ ድርቅ በኋላ ወደ መተከል ሰፈራ ጣቢያ ተልኮ ለጥቂት ጊዜ ሰራ።ከዚያም በጣና በለስ ፕሮጀክት ለ1 ዓመት ከ 4 ወር ገደማ ሰራ።ያ ግን የመጨረሻው የተቀጣሪነት ሥራው ሆነ።ተሰጥኦዬ ነው ወደሚለው ስነ ጽሁፍ ሥራ ሊገባ ወስኖ ሥራውን ለቅቆ ወጣ።
ስነጽሁፍ
ወደ ስነጽሁፍ ሲገባ ነገሩ ቀላል አልነበረም።እሱ እንደሚለው ከሆነ “ወደኋላ ላለመመለስ ድልድዩን መስበር” ነበረበት። ስለዚህም ድልድዩን ሰበረ።
የህክምናም ሆነ የፖለቲካ ባለሙያ አይደለሁም ፤ እኔ የስነጽሁፍ ባለሙያ ነኝ አለ።ለቀጣይ 11 ወራት የኖረበት መንገድ ከባድ ነበር።አንድም የኔ ነው የሚለው ሰው በሌለባት አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ያኔ 10 ሳንቲም ይሸጥ የነበረውን ዳቦ በቀን አንድ ጊዜ ብቻ በውሀ እየበላ መኖር ጀመረ።
ስነጽሁፉን ማጠናከርም ቀጠለ። አሰፋ የተባለ ሰውም ጽሁፉን ያይና ለታዋቂው የጥበብ ሰው ታደሰ ሙሉነህ ሰጠው። ከጥቂት ጊዜያት በኋላ ይህን ሥራውን አርቲስት ጥላሁን ጉግሳ በኢትዮጵያ ሬድዮ ሲተርከው ሰማ። ህዝብም ወደደው። ከዚያ በኋላ በርትቶ መጻፍ ቀጠለ። ጽሁፎቹ በመጽሐፍ እንዲታተም ሲፈለግም 6 ሌሊት በተከታታይ ጽፎ ለህትመት አደረሰው። 1982 ዓ.ም ላይም የመጀመሪያ መጽሐፉ እጸ በለስ ታተመች። በወራት ውስጥም ከ10ሺ በላይ ኮፒ ተሸጠ። በ1984 ዓ.ም ደግሞ የጨረቃ ጥሪ የተሰኘ መጽሐፍን ጻፈ።
ነገር ግን ተስፋዬ ስነጽሁፍን ቢወዳትም እንደሰው የፈለገውን በልቶ እና ለብሶ ለማደር እንደማይችል ተገነዘበ። ከዚህም በተጨማሪ በየቀኑ የሚጽፋቸውን ጽሁፎች ሳይሻግቱ ህዝብ ጋር እንዲደርሱ ማድረግ አስፈላጊ እንደሆነ ተረዳ። ስለዚህም ከመጽሀፍ ማሳተም ባለፈ ፊልም ለመስራት ተንቀሳቀሰ። የስኬት ጉዞውም ተቀላጠፈ። የቴሌቪዥን ድራማዎች ፤ የሬድዮ ድራማዎች ፤ ፊልሞች ፤ ማስታወቂያዎች በተከታታይ መስራት ያዘ።
በቴሌቪዥን ድራማ በተለይ ታዋቂ የሆነው ትንቅንቅ በተሰኘ ድራማው ነው። ከትንቅንቅ በፊት የሚቀርቡት ድራማዎች ሶስት እና አራት ክፍሎች ብቻ ያሉት ቢሆንም ትንቅንቅን ግን 12 ክፍሎች ያሉት የወቅቱ ረጅሙ ድራማ ነበር። ጀማነሽ ሰለሞን እና እናትፋንታ ውቤን የመሳሰሉ አንጋፋ ተዋንያን የተወኑበት ድራማ ነበር። ከዚያም በኋላ ብዙ ድራማዎችን በደራሲነት በአዘጋጅነት አበርክቷል።
በማስታወቂያው በኩል ከአንጋፋው ጉድሞርኒንግ ሻይቅጠል እና አንበሳ ሻይ አንስቶ በርካታ ማስታወቂያዎችን ሰርቷል። የሚድሮክ ማስታ ወቂያዎች የእሱ ሥራዎች ናቸው። በዶክመንተሪ ሥራም እንዲሁ በርካታ ሥራዎችን ሰርቷል። በፊልም በኩልም በኢትዮጵያ የፊልም ጅማሮ ታሪክ ውስጥ ፈርቀዳጅ ከሆኑት መሀከል አንዱ የሆነውን ፍቅር መጨረሻ የተሰኘ ፊልምን እና ሌሎች ፊልሞችን ሰርቷል።
የትዳር ሕይወት
የተስፋዬ የትዳር አጀማመር ለየት ያለ ነው።እስከ ሰላሳዎቹ መጨረሻ ድረስ ትዳር የሕይወት እቅዱ ውስጥ አልነበረም። አንድ ቀን ግን ቁጭ ብሎ ማሰብ ጀመረ። በእሱ አለመውለድ አባቱን ዘር አልባ ሊያደርግ እንደሆነ ተሰማው። ስለዚህም ለማግባት ቆረጠ። ነገር ግን ትዳር በእቅድ አይሆንምና ጊዜው እስኪደርስ መጠበቅ ነበረበት።
አንድ ቀን ከአንዲት ጓደኛው ጋር ቀጠሮ ኖሮት አዲሱ ገበያ ጽዮን ሆቴል ተቀምጦ እየጠበቀ ነበር። ከእሱ ወዲያ ማዶ ሌሎች የሚያውቃቸው ሴቶች ተሰብስበው እየተጨዋወቱ ነው። ተስፋዬ የሚጠብቃት ሴት አልመጣችም። በሌላኛው ጠረጴዛ ላይ ያሉት ሴቶች እንዲቀላቀላቸው ጋበዙት። ተቀላቀላቸው። የዛሬዋ ባለቤቱ እና የሶሰት ልጆቹ እናትም እዚያው ነበረች። በገጠመኝ የተገናኙት ተስፋዬ እና ባለቤቱ ረጅሙን ጉዞአቸውን ጀመሩ። የትዳር ሕይወታቸውም ወደ 23ኛ ዓመቱ እየተዳረሰ ነው።
የልጆች ሁኔታ
ተስፋዬ የሶስት ልጆች አባት ነው። እሱም እንደሚያምነው ልጅ መውለዱ መሰረታዊ ለውጥ በህይወቱ ውስጥ አስከትሎበታል። ”የመኖርን አላማ አግኝቼባቸዋለሁ” ይላል። በእነሱ ውስጥ ሀገርን እየገነባ እንደሆነም ያምናል።” ልጆቼ የሚኖሩባት መልካም ሀገር እንዲኖረኝ ስለምፈልግ ነው ለሀገሬ የምሰራው” በማለትም ልጆቹ እና ሀገሩ ያላቸውን ተዛምዶ ያስረዳል። ልጅ መውለዱ በተስፋዬ አኗኗር ላይ ለውጥ ለማምጣቱ ብዙ ማሳያዎች አሉ። ከእነዚህ ማሳያዎች መካከል ዋነኛው ግን ከአንድ ልጁ ጋር የነበረው ገጠመኝ ጥሩ ማሳያ ነው።
ተስፋዬ ከሶስት አሥርት ዓመታት በላይ ለሚልቅ ጊዜ ሲጋራ አጭሷል። ሲጋራ ማጨሱ ለእሱ ችግር ሆኖ ባይሰማውም ልጆቹ ግን ሁሌም ስጋት ነበረባቸው። በተለይም የመጀመሪያው ልጁ ናኦል እና ሁለተኛ ልጁ ዳግማዊ ይህ የሲጋራ ሱስ አንድ ቀን አባታቸውን እንደሚሳያጣቸው ይሰጉ ነበር።
ስለዚህም አንዳንዴ ሲጋራውን በመደበቅ ፤ አውጥቶ በመጣል እና ሌሎች መንገዶች ሞካክረዋል። ነገር ግን ሙከራቸው አልተሳካም። አንድ ቀን የመጀመሪያ ልጁ አባቱን በግል ሊያናግረው እንደሚፈልግ ይገልጽና ወደ ውጭ ይዞት ይወጣል። ”አንተ ሲጋራ ካላቆምክ ሲጋራ ጠቃሚ ነገር ቢሆን ነውና እኔም ሲጋራ ማጨስ ልጀምር ነው” ብሎ ለአባቱ ይነግረዋል።
”መሀል አናቴን የተፈነከትኩ ነው የመሰለኝ” ይላል ተስፋዬ ቅጸበቱን ሲያስታውስ። መልስ አልሰጠም። ወደ ቢሮው ሄደ። ከራሱ ጋር አተካሮ ገጠመ። ገና በአፍላነት ከጀመረው ገዳይ ወዳጁ ሲጋራ ጋር ያለውን ግንኙነት ማቆም ቀላል ውሳኔ አልነበረም፤ ፈራ። ሲጋራውን ሳቆም ምን ሊከሰት ይችላል የሚለው ሀሳብ ቀላል መልስ ያለው አልነበረም።
በሌላ መልኩ የልጁ ሲጋራ ማጨስ መጀመር ደግሞ ፍጹም ሊቀበለው ቀርቶ ሊያስበው እንኳን የማይችል አሰቃቂ ሀሳብ ሆነበት፤ በመጨረሻ ወሰነ። ለልጆቹ ፍቅር ሲል የሰላሳ ዓመት ወዳጁን ሲጋራን ሊሰናበት ቆረጠ፤ አቆመ። አልተመለሰም።
እነሆ ተስፋዬ ማሞ ከሲጋራ ጋር ከተለያየ 13ኛ ዓመቱ ላይ ደረሰ። ሶስተኛዋ እና የመጨረሻ ልጁ ፌኔት 13 ዓመቷ ላይ የደረሰች ሲሆን አባቷ ሲጋራ ሲያጨስ አይታውም አታውቅም። ትልልቆቹም ልጆቹ ሲጋራ አጫሹን አባታቸውን ረስተው ስፖርተኛውን ተስፋዬ ማሞን ነው የሚያውቁት። ነገሩን በአጭሩ ሲገልጸው “ፍቅር ያድናል” ይላል።
የእረፍት ውሎ
ተስፋዬ አሁን ላይ ብዙ ጊዜውን በቤት በሥራ እና በቤቱ መካከል የሚያሳልፍ ነው። ከልጆቹ ጋር ሁልጊዜ ቅዳሜ ላይ ቅዳሜን ከተስፋዬ ጋር የሚል ልዩ የቤተሰብ የልፊያ ፕሮግራም አለው። አላማውም ከልጆቹ ጋር ያለውን ቅርርብ ማጠናከር እንደሆነ ይናገራል። ይህን የተማርኩት ከአንበሳ ደቦል ነው ይላል።
አሁን ላይ የመጀመሪያ ልጁ ለትምህርት አሜሪካ የሚገኝ ሲሆን ሁለተኛ ልጁም ስለጎረመሰ ይህ ልፊያ ከአፍላዋ የመጨረሻ ልጁ ጋር ብቻ ሆኗል። ቅዳሜ ከሰዓትን የጥበብ የፈጠራ ሥራዎችን በመስራት የሚያሳልፈው ተስፋዬ እሁድ ግን የተለየ ነገር ካልገጠመው በቀር የቤተሰብ ጊዜ ነው ይላል።
ማህበራዊ ሕይወት
ተስፋዬ በማህበራዊ ኑሮ ላይ ንቁ ተሳታፊ ነው። ”በሬን አልዘጋም። ማንም ሰው ቢደውልልኝ አነሳለሁ። ሁሉንም ኢሜይል እመልሳለሁ። ሀሳብ አልፈራም። ቢሮዬ መጥተው የሚያናግሩኝን ሰዎች በሙሉ አናግራለሁ። በሰፈር አካባቢ በሁሉም ማህበራዊ ነገር ላይ እሳተፋለሁ። ትንሽ ችግር የሚሆነው ነገር በየቦታው ስጠራ ሁሉም ቦታ ላይ መሄድ አለመቻሌ ነው። ከዚያ ውጭ አገልጋይ ነኝ” ይላል። በተለይም ከልብ ማእከል ጋር የማእከሉን ዶክመንታሪ ከመስራት ጀምሮ በብዙ ነገር በንቃት ተሳታፊ እንደሚሆን ይናገራል። ከሌሎች ተቋማት ጋርም የአቅሙን ያህል እንደሚሰራ ይገልጻል።
መልእክት
በመጨረሻም መልእክት ካለው እንዲያስተላልፍ ጋበዝነው። ”ማንም ያለ አላማ የተፈጠረ ሰው የለም። ሁሉም ሰው ቦታ አለው። በምንኖርበት ዘመን ሁሉ ቦታችንን ሸፍነን ለመስራት እንሞከር። ይላል። አንዳችን ለአንዳችን እናስፈልጋለን። በሰውነት ደረጃ ብንኖር እና ስለሰው ብንቆረቆር ጥሩ ነው። የተፈጠርነው ሰው ብቻ ሆነን ነው። ስለዚህ ለሰው እንኑር። በቦታችን ሆነን ከሰራን ለዓለማችን ብዙ እንጠቅማለን። ”በማለት ሰብዓዊነት ላይ ትኩረት እንድናደርግ ጥሪ አቅርቧል።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን መጋቢት 4/2014