ኢንዱስትሪውን አስቀድመው ያወቁ ከብረውበታል። አስቀድመው የጀመሩት ብዙ ርቀት ሄደውበታል። ከፍ ያለ መዋለ ንዋይ በዘርፉ ይዘዋወራል። ዘመነኞች ዋንኛ መታያቸው መዋቢያና ማጌጫቸው ወቅታዊ የሆነ ግብዓት “ፋሽን” የተሰኘ ቁስ ነውና አነፍንፈው የራሳቸው ያደርጉታል። በዚህም ብዙዎች ከራሳቸው አልፈው ማኅበረሰቡን ብሎም አገራቸውን የገቢ ምንጭ እንድታገኝ ምክንያት ሆኖላቸዋል።
የፋሽን ገበያ በባህሪው ዓለማቀፋዊ ነውና ባጠረ ጊዜ ዓለም ላይ ተዘዋውሮ ያለ ገደብ እዚህም እዚያ ይገኛል። በምቾት በጥራትና በዲዛይን ማማሩ ዋነኛ መስፈርት ነው። የመልኩን ያህል ዋጋ፣ የዲዛይኑን ወይም ንድፉን ያህል ገንዘብ፣ የዘመኑን ያህል ተመን ወቶለት ይቸበቸባል። በዚህም አገራት ገቢያቸውን የማሳደጊያ ሰበብ፣ የበርካታ ዜጎቻቸው የሥራ ዕድል መፍጠሪያም አድርገውታል።
የፋሽን ኢንዱስትሪው ተዋንያን እንደ አገር የተሻለ ውጤት ለማምጣት ዘርፉ በተሻለ መንገድ መደገፍ የዘርፉ ተዋናዮችን ማጠናከርና ወቅቱንና ቴክኖሎጂውን ያማከለ ስልጠና፣ ትምህርትና ያልተቋረጠ ክትትልና ድጋፍ ማድረግ ይገባቸዋል። በእርግጥ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገራት ዘርፉ ገና ብቅ ብቅ ያለና አዲስ እንደመሆኑ መጠን ከሌሎቹ ጋር እኩል መራመድና በፋሽን ኢንዱስትሪው ውጤት ለማምጣት ብርቱ ስራ ይጠብቃል።
የፋሽን ኢንዱስትሪው መነቃቃት እንዲያሳይና ዘርፉ የላቀ አበርክቶ እንዲኖረው ከታሰበ ደግሞ ሙያውን የሚመጥኑ ባለሙያዎች ማፍራት ተገቢነቱ ይነሳል። በተለይም በንድፍ ሥራ ወይም በዲዛይነርነት በፋሽን ኢንዱስትሪው የሚሳተፉ ባለሙያዎች ብቃት ደረጃ ከፍ ማለትና ማነስ ዘርፉ ላይ ትልቅ ተፅዕኖ ይፈጥራል። በመሆኑም ባለሙያዎቹን ማፍራትና ማብቃት ላይ ትልቅ ሥራ መሥራት እንደሚገባ የዘርፉ ባለሙያዎች ይጠቅሳሉ።
ለመሆኑ በእኛ አገር በተለያየ መልኩ የፋሽን ዲዛይን ትምህርት ቤቶች የወቅቱን የፋሽን ኢንዱስትሪ መሠረታዊ ጉዳዮች አሟልተው ነው ትምህርት እያሰጡ የሚገኙት? የሚለውን ጥያቄ ከዚህ ቀደም በዚሁ ገፃችን ማንሳታችን ይታወሳል። ዛሬ ደግሞ ዲዛይነሮቻችን ወደ ዘርፉ የሚገቡበት መንገድና በፋሽን ዲዛይን ሙያ ራሳቸውን ለመለወጥ በሚያደርጉት ሂደት ውስጥ እያደረጉት ያለውን ጥረት እንመለከታለን።
አንድ ዲዛይነር ዲዛይነር ለመሰኘት መሠረታዊ የሙያውን እውቀት ከክህሎት ጋር የተላበሰ፣ የሙያውን ሥነ ምግባር ያከበረና አግባብ ካለው ተቋሙ በሙያው የተመረቀ ሆኖ ሊገኝ ይገባል። በእኛ አገር ልምድና ተሞክሮ ወደዘርፉ በአብዛኛው የሚገባበት መንገድ ከዚህ የተለየ ነው።
ዲዛይነር ሄለን አየለ ከ5ዓመት በላይ ሙያው ላይ ቆይታለች። በእርግጥ ጅማሮው ላይ የ3 ወር አጭር ስልጠና ወስዳ ወደ ዲዛይን ሙያው መግባቷን የምትናገረው ሄለን፣ የረጅም ጊዜ ቆይታዋ ግን በዲዛይን ሥራው የተሻለ ደረጃ ላይ እንድትገኝ አድርጓታል። በዘርፉ የሚታየው ችግር ዋንኛ መንስኤ ከመንግሥት የተሰጠው ትኩረት ዋንኛ መሆኑን የምትናገረው ዲዛይነር ሄለን፣ ሙያተኛውም በድፍረት ያለችሎታና እውቀት የሚገባበት መሆኑም ትልቅ አሉታዊ ተፅዕኖ ይፈጥራል ትላለች።
እንደባለሙያዋ አስተያየት አብዛኛው ወደሙያው የሚገቡ ግለሰቦች ሙያውን በትክክል አውቀውትና ለሙያው የሚያስፈልገውን ነገር ጨብጠው ሳይሆን፣ ውስጣቸው ባለ ፍላጎት ተነሳስተው መሆኑን ትናገራለች።
እርሷን ጨምሮ በዘርፉ ያሉ አብዛኛዎቹ ጓደኞቿ በሌላ ሙያ ተመርቀው ነገር ግን በአጋጣሚ ውስጣዊ ፍላጎታቸው ስለሆነ ወደ ፋሽን ገብተው እንደቀሩ ትናገራለች። አሁንም የተሻለ ቴክኖሎጂና የዘርፉን ሙያ የሚያሳድግ እውቀት ምን አልባትም ከማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ አይተው ካልቀሰሙ በስተቀር የሙያውን ደረጃ የሚመጥን ትምህርት በአገር ደረጃ እየተሰጠ አይደለም ብላ ታምናለች።
ህሊና ይታየው በዲዛይነርነት ሙያ ላይ ሁለት ዓመት ሠርታለች። ሙያው የሚጠይቀውን ስልጠና በፋሽን ዲዛይን መስክ ወስዳ ነው ወደ ሥራ የገባችው። በእራሷ ሙያዊ ብቃቷን እንዳሳደገች ትገልፃለች። በሙያው ውስጥ ከሚታዩ ችግሮች አንዱና ዋንኛው ሙያው በደንብ ሳይረዱትና ሳያውቁት ስሙን ብቻ ይዘው የሚሠሩ ግለሰቦች መሆናቸውን የምትገልፀው ሕሊና፣ ወደ ሥራው ሲገባ በአግባቡ ሰልጥኖና ሙያው የሚፈልገው ክህሎት ተይዞ መሆን ይገባዋል ነው የምትለው።
በተለያዩ ከተሞች የሚታዩት የፋሽን ትምህርት ቤቶችም ቢሆኑ መሠረታዊ እውቀት እንድትጨብጥ ከማድረግ ያለፈ ጉልህ ሚና እንደሌላቸውም ነው ዲዛይነር ሄለን የምትናገረው።
የፐርፕል ዲዛይን ባለቤት የሆነችው ዚነት ሙሐመድ ከሶስት ዓመት በላይ በሙያው ቆይታለች። ቀድማ በአካውንቲንግ ትምህርቷን ተከታትላ የጨረሰችው ዚነት፣ ወደ ፋሽን ዘርፍ የመጣችው ውስጧ የነበረውን ፍላጎትና ምኞት ለማሳካት በዘርፉም የራስዋን አስተዋፅኦ ለማበርከት ነው። በግልዋ የተወሰኑ የፋሽን ዲዛይን ትምህርት ኮርሶችን ወስዳ ነው ወደ ሙያው የገባችው። በአሁኑ ሰዓት ፐርፕል የተሰኘ የራስዋ የፋሽን ዲዛይንት/ቤት ከፍታ እየሠራች ትገኛለች።
ወደ ፋሽን ዲዛይን ትምህርት ቤት የሚገቡ ወጣቶች የመቀበያ መስፈርት እንደሌለና ማንበብና መፃፍ የሚችል ሁሉ መሰልጠን እንደሚችል ትናገራለች። ሁለት ማሰልጠኛዎች አሉዋት። በማሠልጠኛዋ ውስጥ የእርስዋ ድርሻ ማስተዳደር መሆኑን የምትገልፀው ዚነት፤ አሠልጣኞቹም በሌቭል (በደረጃ )4 ወይም በዲግሪ ደረጃ በፋሽንና ዲዛይን የተመረቁ መሆናቸውን ታስረዳለች። በፋሽን ዲዛይን ትምህርት ቤቷ ውስጥ አንድ የስዕል ዲዛይን አስተማሪ ሌሎቹ አራት ደግሞ ዲዛይንና ስፌት አስተማሪዎች እንዳሉና ሙያው ላይ ብቁ መሆናቸውን ትናገራለች።
በፋሽን ኢንዱስትሪው ውስጥ የላቀ ሚና ያላቸው በተለያየ መልኩ በፋሽን ሙያ ላይ የሚሳተፉ ግለሰቦች ወደሙያው የሚገቡት በተለያየ መንገድ ነው። በተለይ እንደ አገራችን ባሉ ለኢንዱስትሪው አዲስ የሆኑ አገራት ላይ ከሙያው ጋር በተያያዘ እንደአዲስነቱ የተለያዩ ጥያቄ ሊነሳ ይችላል። የሰልጣኞች መቀበያ መስፈርት እንደ አንድ ጥያቄ ሊነሳ ይችላል።
ስልጠናው ተግባራዊነት ላይ ስለሚያመዝን ሰልጣኞች በመስፈርት ባይገቡም የመፃፍና የማንበብ ችሎታ ካላቸው በቂ ነው የምትለው ዚነት፣ ለተሻለ ዕድገትና ሙያዊ ፈጠራ በትምህርት ደረጃም ይሁን በክህሎት ከፍ ያለ መስፈርት ቢወጣ የተሻለ ውጤት ማግኘት እንደሚቻል ግን ታስገነዝባለች።
የመቀበያ መስፈርቱ በእርግጥ በሁሉም ትምህርት ቤት አንድ እንዳልሆነና አንዳንድ ትምህርት ቤቶች ከ10ኛ ክፍል በላይ ያሉ ተማሪዎችን እንደሚቀበሉ፣ እነርሱ ግን ማንበብና መጻፍ የሚችል ከሆነ እንደሚያሰለጥኑ ትገልፃለች። ከዚህ ጋር ተያይዞ በባለሙያዎች የሚነሳ ሌላ ጥያቄም አለ። ዲዛይነር ማን ነው? ለሚለው ጥያቄ የሚሰጠው ምላሽ ከዚህ ሀሳብ ይመዘዛል።
ይህ ሙያ ታላቅና በብዙዎች የተወደደ የለውጥም መሠረት ሆኖ ሳለ እንዲሁ በፍላጎትና በሙያው ባላቸው ፍቅር ብቻ ዘለው ገብተው ሙያው ላይ የሚሳተፉ በሙያው የሚፈለገውን የብቃት ደረጃ ሳያሟሉ በራሳቸው ብቻ የተለያዩ አጋጣሚዎችን ፈጥረው የዲዛይነርነት ካባ የደረቡ “ዲዛይነር” የተሰኙ እንዳሉም ይነሳል።
ዲዛይነር ሄለንም ሆነ ዲዛይነር ዚነት በዚህ አይስማሙም። ሙያውን በትክክል ጠንቅቆ ያወቀ የሚፈልገውን ክህሎትና ዕውቀት የተላበሰና በስራው ጥሩ ስኬት ያስመዘገበ ካልሆነ በቀር የሙያው ፍላጎት ያለው ሁሉ ገብቶ ልሥራ ማለቱን አይቀበሉትም። የሚመለከተው አካል የቁጥጥር ሥርዓት ዘርግቶ በእዚህ እንዲሠራም ይጠይቃሉ።
ተገኝ ብሩ
አዲስ ዘመን ሰኞ የካቲት 28 ቀን 2014 ዓ.ም