“ዓድዋን ለኢትዮጵያውያን ኅብረት፣ለአፍሪካ የነጻነት ጮራ”
ዛሬ የዓድዋ ድል 126ኛ ዓመት በመላ ኢትዮጵያ በደማቅ ሥነ ሥርዓት እየተከበረ ነው። በዓሉ በተለይ በአዲስ አበባ በደማቅ ሥነ ሥርዓት የሚከበር ሲሆን ፣ በክልሎችም በተለያዩ ሥነሥርዓቶች እየተከበረ ነው። በበዓሉ የዓድዋ ድል፣ ድሉ እንዲመዘገብ የጎላ አስተዋጽኦ የነበራቸው ጀግኖች፣ የመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ የአንድነት ስሜት፣ ወዘተ በሚገባ ይዘከራሉ። ይህ በዓል ለዘመናት ሲከበር ይደረጉ ከነበሩትና አሁንም ድረስ ከዘለቁት መካከል ፉከራዎች ፣ ሽለላዎች፣ ቀረርቶዎች ይጠቀሳሉ።
ፉከራ፣ ሽለላና ቀረርቶዎቹ እንዲሁም ቅኔ በጦርነቱም ወቅት ሠራዊቱን ለማነቃቃት ለማጀገን ባላቸው ፋይዳ በሚገባ ጥቅም ላይ ውለዋል። ከድሉም በኋላ በየበዓላቱ ወቅት የበዓሉ ድምቀት ሆነው ዛሬም ድረስ ቀጥለዋል፤ እያንዳንዱ ትውልድም እነዚህን ፉከራ፣ ቀረርቶ፣ ሽለላና ቅኔዎች ከአባቶች እየተቀበለ በተለያዩ መድረኮች ዓድዋን ይዘክርባቸዋል።
በቅድሚያ ስለ ፉከራ፣ ሽለላ፣ ቀረርቶ ጥቂት እንበል። ደስታ ተክለወልድ በአማርኛ መዝገበ ቃላታቸው ቀረርቶን፤- ቀረረ፣ የጦር ግጥም ገጠመ ፣አጉራራ፣ ቀረርቶ፣ ሽለላ፣ የጦር ዘፈን በማለት ይገልጹታል። በዚህ ጽሑፋችን ማንሳት የፈለግነው በዓድዋ ዙሪያ ስለተገጠሙ ግጥሞች ነው። ግጥሞቹ በጦርነቱ ዋዜማና በወቅቱ በፍጻሜው የነበሩ ሲሆኑ፤ቅድመ እና ድኅረ ተብለው የሚከፈሉ ናቸው። በጦርነቱ ወቅትም የተገጠሙት ሳይረሱ ማለት ነው። ለምሳሌ እኔ የሎሬት ፀጋዬ ‹‹ዋ! አድዋ›› ግጥም እነ የእጅጋየሁ ሽባባው የዓድዋ ዘፈን የዓድዋ የልጅ ልጆች ሆነው ዝናውን ሰምተው የድህረ ዓድዋ ዘመን ተሻጋሪ ሥራዎች ናቸው።
ሽለላ የሚለውን ቃላት ሲፈቱት ቅርርት አለ።አለ ነገር አለ ፤ነገር ቁልቁለቱን ወርደን ወንዙን ስንሻገር ማለት መሆኑን አንድም ሽለላ ሽድሸዳ ውስወሳ በማለት ይገልጹታል።ምናልባት በዘመናችን ፕሮፓጋንዳ እንደሚባለው ይመስላል።
ፉከራንም እንዲሁ ፉከራ ፤ዘራፍ ማለት ድንፋታ ዠብዱ ቈጠራ ። መፈከር ፤መደንፋት ዝኆን፣ አንበሳ፣ ጠላት ገዳይ በሚል ይኸው መጽሐፍ ይፈታዋል።ፉከራ በብዛት ከሽለላና ቀረርቶ የሚለየው ግጥም አልባ ድንፋታ ያለው ጭምር ነው። ለአብነት የሚሆኑ ፉከራና ሽለላዎች እንያቸው፡-
ፉከራ በተግባር (በውጊያ) ላይ የሚፈጸም ነው፤ እንደ ተግባሩ ባይሆንም በስድ ግጥምም ይገለጣል።
ዱብ ዱብ ባይ እንደበረዶ
በልጅነቱ በረሃ ለምዶ
ይምጡ ባይ ይሰብሰቡ ባይ
ሲሰበሰቡ አንገዋሎ ጣይ
ሽለላ
ኧረ በለው በለው ኣስኪደው በዋንዛ
በእናት አገርና በሚስት የለም ዋዛ
ተው ተመለስ እሱ ነው ድንበሩ
የጀግኖች መኖሪያ አይነካም በሩ
ፉከራ ሽለላና ቀረርቶም እንዲሁ በጦርነቱ ትልቅ ዋጋ እንደነበራቸው በወቅቱ ተፎክረው ተሸልለው፣ ወዘተ ከነበሩ እና ለትውልድ በቃልም በጽሑፍም ከተላለፉ ፉከራ፣ ሽለላና ቀረርቶዎች መረዳት ይቻላል።
ጣሊያኖች በውጫሌ ውል ላይ ሸፍጥ በመሥራት ኢትዮጵያን በእጃቸው ለማስገባት ሙከራ ከማድረግ አልፈው የኢትዮጵያን ግዛት ደፍረው በመግባት መረብን ተሻግረው ኢትዮጵያን የወረሩት (ትግራይ አካባቢን) የዛሬ 126 ዓመት በመስከረም 1888 ዓ.ም ነበር። ይህ ድርጊታቸውም ንጉሠ ነገሥት ዳግማዊ አፄ ምኒሊክን እና ባለቤታቸውን እቴጌ ጣይቱን እንዲሁም መላ ኢትዮጵያውያንን በእጅጉ አስቆጣ።
ዳግማዊ አጼ ምኒሊክ ችግሩን ለመፍታት ዲፕሎማሲያዊ መንገዶችን ሞከሩ፤ ይሁንና ጣሊያኖች አሻፈረኝ ስላሉ፤ በዚህም አጼ ምኒሊክ እቴጌ ጣይቱም በእጅጉ ተቆጡ። ንጉሠ ነገሥቱ ክተት አዋጅ አስነግረው ተከተለኝ ሲሉ ሕዝቡን አሳሰቡ። ይህን ሠራዊት በጥቅምት ወር አጋማሽ ላይ ወረኢሉ ላይ ላግኝህ ብለው ጉዞ ተጀመረ። 100 ሺ እንደሚሆን የሚገለጸው ይህ ሠራዊት ከአገሪቱ የተለያዩ አቅጣጫዎች ወደ ሰሜን ዘመተ። በወቅቱ አገሪቱ መደበኛ ጦር አልነበራትም፤ በሰላም ጊዜ አርሶ አደርና አርብቶ አደር በጦርነት ጊዜ ደግሞ ወታደር ሆኖ የሚያገለግል ሕዝብ ነበር ያላት።
ዓድዋ ከአዲስ አበባ 1,066 ኪሎ ሜትር ርቀት ይገኛል። ለጦርነቱ መነሻ የሆነው የውጫሌ ውል የተፈፀመው በዚሁ ዘመን ከአዲስ አበባ በስተሰሜን 468 ኪሎ ሜትር ርቀት ግድም ከውጫሌ ግርጌ ከአምባሰል ተራራ ሥር ወሎ ውስጥ ንጉሥ ይስማ የተባለ በሚጠራ ሥፍራ ነበር።
በወቅቱ የጦርነት ጉዞ መነሻውን ከአዲስ አበባ ያደረገው ጦር አድዋ የደረሰው ስድስት ወር ተጉዞ ነው፤ ሠራዊቱን ከተከተሉት መካከልም አዝማሪዎችና ገጣሚዎች ይገኙበታል። በወቅቱም የቅኔ ተማሪዎች የቅኔ ትምህርታቸውን ትተው ወደ ጦር ሜዳ መሄዳቸውም በሚከተሉት ስንኞች ተቋጥሯል።
ወግጂልኝ ድጓ ወግጂልኝ ቅኔ
ጀግኖች ከዋሉበት እውላለሁ እኔ።
ቅድሚያ መቀመጫዬን እንዳለችው ዝንጀሮ ቅድሚያ አገሬን ሰላሜን ቀጥሎ ሰላም ሲሆን እማራለሁ ሲሉ በግጥማቸው ‹‹ወግጅልኝ ቅኔ›› ሲሉ ገልጸዋል ።
ሠራዊቱ ያሳየው ቆራጥነትና የከፈለው መስዋዕትነትም በስንኞች ተቋጥሯል።
ውረድ እንውረድ ውረድ ካናቱ
የሞተው ይሙት ታልቅስ እናቱ
ዳግመኛ እንግፋ እስካለበቱ ።
ጦሩ በፉከራ፣ በቅኔ፣ በሽለላ፣ በቀረርቶ ታጅቦ ሲጓዝ የነበረ ሲሆን፣ ይህም ከድካሙ እንዲነቃ ወኔውም እንዲነሳሳ እንዳደረገው ሰነዶች ያስረዳሉ።
በመስከረም የተንቀሳቀሰው ጦር በኅዳር መጨረሻ አምባአላጌ ደረሰ፤ ጉዞው ደግሞ በእግርና በፈረስ ስለሆነ መኪናም ስላልነበር አታካች ነው። አምባአላጌ አካባቢ ያለውን የተፈጥሮ ምሽግ በሻለቃ ቶዜሊ የሚመራው የጣሊያን ጦር አስቀድሞ ተቆጣጥሮታል። በወቅቱ በሥፍራው የደረሰው የኢትዮጵያ ጦር ጠቅላይ አዛዥ ራስ መኮንን ጣሊያኖች ቦታውን ለቀው እንዲወጡ በመደራደር ላይ ነበሩ፤በጣሊያን መድፈኞች እየተመቱ አበሾች ወደ ኋላ ሲያፈገፍጉ አይተው ፊታውራሪ ገበየሁ ‹‹ፈሪ! እንዴት ትሸሻላችሁ? እኔ እንዴት እንደምሞት ለንጉሡ ሄዳችሁ ንገሩ›› በማለት ፈረሳቸውን አስነስተው በግልቢያ በሚዘንበው የመድፍ ጥይት መካከል ገቡ።
እሳቸውን ሲያይ ሁሉም እየሮጠ ተከታትሎ ገብቶ ከመድፎቹ ጋር ተጨፋጭፎና ገድሎ መድፈኞችን ማረከ። ገበየሁ ግን ሞቱ ። ፊታውራሪ የተገደሉት ተራራው ላይ የመሸገውን የጠላትን ጦር አያያዝ አስሰው እንዲመለሱ ታዘው 1,200 የሚያህል ጦር እየመሩ ሄደው ውጊያ በመከፈቱና እሳቸው ከላይ እንደተገለጸው በእልህ ሳይሸሹ በመዋጋታቸው ነው። ሬሳቸው ከወደቀበት ቦታ የእኛዎቹ ጀግኖች አብረው በመውደቅ የእርሳቸውን አስከሬን አከበሩት። እሳቸውም ቢሞቱም የአምባአላጌ ድል ለኢትዮጵያ ሆነ። ለጦሩም ስነልቦና ትልቅ ሚና ነበረው።እናም
የዓድዋን ሥላሴ ጠላት አረከሰው
ገበየሁ በሞቴ ግባና ቀድሰው ።
የንጉሥ ፊታውራሪ የጐራው ገበየሁ
አላጌ በሩ ላይ ማልዶ ቢገጥማቸው
ለምሳም አልበቁት ቁርስ አደረጋቸው።
ተብሎ ተገጠመላቸው ። ይህም የጦርነቱ መጀመሪያ ሲሆን በዚህም የጣሊያን ጦር ድል ሆኖ ሻለቃ ቶዜሊም መገደሉንና የቀረው የጣሊያን ጦርም በድንጋጤ መበተኑን በፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ መጽሐፍ ላይ ተመልክቷል። ባለቅኔም
‹‹ አበዛው ገበየሁ ነጩን ሲጋግር
ታፈሰ እያረዱ ነጩን ሲመትር
መትረው ጋግረው ሔዱ ሳያዩ ግብር›› ሲል ተቀኝቷል።
ገበየሁን ከባሻህ አቦዬ ጋር በማጣመር ባለቅኔው ፡-
‹‹ ያ በሻህ አቦዬ ያ ጐራው ገበየሁ ሁለቱም ያበዱ
እንቅር አይልም ወይ አንዱ ሲሄድ አንዱ።›› በማለት ገልጿቸዋል።
ፊታውራሪ ገበየሁ በጦርነቱ ሲሰዉ፤ ‹‹ሳይደግስ አይጣላም እንዲሉ››እርሳቸውን የሚተካ ሌላ የዓድዋ ጀግና በዓድዋ ደምቆ ታየ፤ ባልቻ ሳፎ (ባልቻ አባ ነፍሶ)። ለዚህም ገበየሁ ቢሞት ተተካ ባልቻ ተብሎ እንደተገጠመላቸው በተክለጻዲቅ መኩሪያ መጽሐፍ ተመልክቷል።
ገበየሁ ቢሞት ተተካ ባልቻ
መድፍ አገላባጭ ብቻ ለብቻ፤
ፊታውራሪ ገበየሁ ጉርሙ በፈረስ ስማቸው አባ ጎራ ሲባሉ በአካባቢው አጠራር ደግሞ ገበየሁ ጎራው ይባሉ ነበር ። ፊታውራሪ ገበየሁ ወደ ዓድዋ ሲዘምቱ በጦርነቱ ወደ ኋላ ስሸሽ ከተመታሁ አሞራ ይብላኝ፤እኔ እንደ አባቶቼ አይደለሁምና ወግ አይገባኝም፤ከፊት ለፊት ስፋለም ከወደቅኩ ግን አስከሬኔን ትውልድ ቦታዬ ውሰዱልኝ ብለው ተናዘው ነበር። በወቅቱ ከጦርነቱ በኋላ ዓድዋ ሥላሴ ቤተክርስቲያን ተቀበሩ። በሞቱ በሰባተኛ ዓመታቸው ወደ ትውልድ ቦታቸው አንጎለላ ኪዳነምህረት አፅማቸው ተወስዶ አረፈ። ከጦርነቱ መልስ በጃንሜዳ የጦር አበጋዞች በፈረሳቸው ሲያልፉ የፊታውራሪ ገበየሁ ፈረስ ብቻውን ከፊት ከፊት ሲያልፍ ያዩት ዐፄ ምኒሊክ ተንሰቅስቀው እንዳለቀሱ ይነገራል።
በአምባላጌው አናት ደርሰው የጨበጣ ውጊያ የጀመሩት ኢትዮጵያውያን እየቀናቸው ሄደ ። ጄኔራል ቶዞሊ ከወዲህ ከወዲያ እየተዘዋወረ በሚያዋጋበት ጊዜ ድንገት ፊታውራሪ አባ ውርጂ ከሚባል የራስ መኮንን ሰው ጋር ተገናኘ፤ ሽጉጡን እስኪያወጣ ድረስ አባ ውርጂ ጊዜ አልሰጠውም። ትግል ገጥመው ተያይዘው ገደል ገቡ እና የሁለቱም የሕይወት ፍፃሜ ሆነ። በዚህ ምክንያት እንዲህ ተብሎ ተገጠመ፦
ጀኔራል ባህር ማጆር ቶዞሊ
ማን ይነካዋል ያለ ፈጣሪ
ገደል ሰደደው ውርጂ ፊታውራሪ ።
አንዳንድ ጸሐፊዎች ውርጂ የሚለውን አንድ በሚል ገልጸውታል። ሥርገው ሐብለሥላሴ አላጌ ላይ ከፊታውራሪ አባ ውርጂ ሌላ የሞተ ጊድን ገብሬ የተባለ ጀግና እንደነበር ጠቁመው፤ እርሱም የላስታና የዋግ የጦር መሪ ነበር ይላሉ። እኅቱም ጥይት በቀሚስ ጫፍ እየቋጠረች ስታቀብል አብራ መሞቷንም መረጃዎች ያመለክታሉ ። እነዚህ ሁለት ሰዎች ሕይወታቸው ለወገን ክብር ሲሉ የሰዉ በመሆኑ በግጥም እንዲህ ተብለው ተሞግሰው ነበር።
የጊድን አገር አይተኛውም በውን
ጦር መጣ ቢሉት ይነሳል አሁን
ጊድን ገብሬ የሜዳ ዝሆን
ፈረሱን ጫኑት ይነሳ እንደሆን ።
የጊድን እኅት ምጥን ወይዘሮ
ጥይት አቀባይ እንዳመልማሎ
የአምባአላጌ ውጊያ ከተደመደመ በኋላ ጉዞ ወደ መቀሌ ሆነ። በወቅቱ የአፄ ምኒሊክ ጦር ትግራይ ደርሷል። በሻለቃ ጋሊያኖ የሚመራ 1,300 የጣሊያን ጦር እንዳየሱስ ኮረብታ ላይ መቀሌ አጠገብ መሽጎ ተቀመጠ። እንዳየሱስ 2,225ሜትር ከፍታ ሲኖረው ዙሪያው በድንጋይ ካብ በጥብቅ ስለተሠራ በቀላሉ የሚደፈር አልነበረም። የውሃ ኩሬ የሚገኘው ከምሽጉ ውጪ ስለነበር፤የኢትዮጵያ ጦር የመጠጥ ኩሬውን ከቦ ጠበቀ። በተራራው ጣሊያን በበርሜል ውሃ አከማችቶ በቁጠባ ያከፋፍል ነበር ። በወቅቱ ጣሊያኖች በውሃ ጥም ተጎዱ። ውሃም ለዓድዋ ድል አንዱ ምከንያት እንደ ነበር ይገለጻል ። ወደ መቀሌው ታሪክ ስንመለስ በውሃ ጥም የተጎዱትን ጣሊያኖች አስመልክቶ አቅራሪ እንዲህ አለ
ነዳናቸው መቀሌ ከግንብ ወስደን አጐርናቸው
ካህያ ከፈረሱ ሬሳ አስታቀፍናቸው
ውሃውን ከልክለን ፈርስ አሸናናቸው
ምኒሊክ መሐሪ ነው ከደሴ ገስግሶ ፈቶ ሰደዳቸው
አድዋ አካባቢ ተራራማ ነው ፤ ሸልዶ ወይም ሶሎዳ ተራራ፤ ማርያም ሸዊቶ፤ አዲ አቡን፤ ረቢ አርእየኒ የተባሉት ገመገሞችና ተራራማ ሥፍራዎች ዋነኞቹ የጦር ግንባሮች ነበሩ። በመቶ ሺህ የሚሠላ የኢትዮጵያ ገበሬ ሠራዊት በአንድ ቀን ውጊያ ባለድል ሆነ ። በየካቲት 23ቱ የአድዋ ጦርነት በውጊያው ዝና ካገኙት መካከል ሊቀመኳስ አባተ ይጠቀሳሉ። በወቅቱ የተኮሱት የመድፍ ጥይት በጣሊያኖቹ መድፍ አፈሙዝ ተቀረቀረ።ገጣሚም እንዲህ አለ
አባተ አባ ይትረፍ ነገረኛ አዋሻኪ ሰው
ይህን መድፍ ከዚያ መድፍ አቆራረጠው
አበሻ ጉድ አለ ጣሊያን ወተወተ
ዓይነጥሩ ተኳሸ ቧ ያለው አባተ።
በዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን በጣሊያን ቅኝ ገዢዎች ሊደርስባቸው የሚችለውን ፈተና ለመግለጽም ገጣሚዎች ከዚህ በታች ያለውን ግጥም ስንኞች እንደቋጠሩ ሰነዶች ያስረዳሉ።
ምኒሊክ ተወልዶ ባያነሳ ጋሻ
ግብሩ ዕንቁላል ነበር ይሄን ጊዜ አበሻ
የዶጋሊው ባለድል ራስ አሉላ በዓድዋ ጦርነት ተፋላሚ ከነበሩት አንዱ ነበሩ፤ በሶሎዳ ተራራ ጀርባ በእንዳ ሸዊቶ ግንባር የጄኔራል ዳቦር ሜዳን ጦር ሲደመስሱ እንዲህ ተብሎ ተገጠመላቸው ።
እነዚህ ጣሊያኖች እጅግ ተደሰቱ
የአሉላ ጎራዴ ሲበርድ ስለቱ።
በጦርነቱ ደጃዝማች ባልቻ ሣፎ ሰውነታቸው ኮሳሳ ሆኖ መድፉን በቀላሉ ከወዲያ ወዲህ እያዟዟሩ ይተኩሱ ነበርና በግጥም ሲያደንቋቸው
እንደደጋ ገብስ እንዲያ ኮስሶ
ያስቆረጥማክ ጠላቱን ኮሶ
የዳኛው ጀግና ባልቻ አባ ነፍሶ ።
በመድፍ ጠላትን እያሻገሩ በሚያጠቁበት ጊዜ ከጠላት በተተኮሰ ጥይት ጆሮዋቸው ተቆረጠ ። ባለቅኔም
ማን እንዳንተ አርጎታል እርሳሱን ጉትቻ
የዳኘው አሽከር አባነፍሶ ባልቻ ።
ከድሉ በኋላም በደስታው የተቋጠሩ ስንኞች መካከል ከዚህ በታች ያሉት ይጠቀሳሉ። በአጠቃላይ ዓድዋ የጦርነት ብቃት የአገር ፍቅር ብቻ ሳይሆን የኪነጥበብ ፍቅር የታየባቸው ነበሩ። በዚሁ መልካም የድል በዓል አገራችንን ከድህነት ጠላት ለማውጣት እንታገል እንላለን።
ባመጣው ወጨፎ በሠራው እርሳስ
ወቃው አመረተው ያን የባሕር ገብስ
ዳኘው ምኒሊክ የኢትዮጵያ ንጉሥ።
ቅዳሜ ተግዞ እሁድ ተበራየ
መስኮብም ገረመው ጣሊያንም ጉድ አየ።
ዳኘው በዲሞትፎር በለው በለው ሲል
የቃኘው መኮንን ደጀኑን አፍርሶ ጦር ሲያደላድል
አባተ በመድፉ ምሳውን ሲገድል
ባልቻ በመትረየስ ነጥሎ ሲጥል
የጎጃሙ ንጉሥ በለው ግፋ ሲል
እቴጌ ጣይቱ ዳዊቷን ዘርግታ ስምዐኒ ስትል
ለቆሰለው ጀግና ውሃ ስታድል
እንዲህ ተሠርቶ ነው የዓድዋው ድል።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን የካቲት 23/2014