የካቲት በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ደማቅ ታሪክ የተጻፈበት ወር መሆኑን ባለፉት ሁለት ሳምንታት ስራዎቻችን ባቀረብናቸው ዘገባዎች ለማመለክት ሞክረናል። ከእነዚህ ዘገባዎች መካከልም የካቲት 12 የሰማዕታት ቀንን አንዱ ነው። የፊታችን የካቲት 23 ደግሞ የኢትዮጵያ ገናናነት የተመሰከረበት የዓድዋ የድል ቀን ይከበራል፤ በእዚህም ሳምንት እንገናኛለን።
ይህ የየካቲት ወር ታሪካዊነት ግን በእነዚህ ታሪካዊ ክስተቶች ብቻ የተወሰነ አይደለም። በኢትዮጵያ ትልቁ አብዮት የፈንዳውም በየካቲት ወር 1966 ዓ.ም ነው። ለዚህም ነው በተለምዶ ‹‹የየካቲት 66ቱ አብዮት›› እየተባለ የሚጠራው። የ66ቱ አብዮት የተባለበት ምክንያት ደግሞ ለዓመታት በተለያዩ ተቃውሞዎችና አመጾች የቆየው ሕዝባዊ ትግል ዋና ዋናዎቹ ክስተቶች የተፈጸሙት በዚሁ በወርሃ የካቲት በመሆኑ ነው።
ከእነዚህ ዋና ዋና ክስተቶች አብዛኞቹ ደግሞ በዚህ ወር በዚህ ሳምንት የተከሰቱ በመሆናቸው ርእሰ ጉዳዩን ለዛሬ አምዳችን መርጠነዋል። የየካቲት 66ቱ አብዮት፣ ኢትዮጵያውያን ለዘመናት ሲመሩበት የኖሩት ንጉሣዊ አገዛዝ አንገፍግፏቸው ለዓመታት ሲታገሉ ቆይተው ትግላቸው ተፋፍሞ ከፍተኛ ደረጃ የደረሰበትና በቃኝ ብለው በሥርዓቱ ላይ አንድ ሆነው የተነሱበት ነው።
በየካቲት 66 በዚህ ሳምንት በየአቅጣጫው ተቃውሞ ተቀጣጥሎ እንደነበርና ይህን ተከትሎም ንጉሰ ነገስቱ የተለያዩ እርምጃዎችን መውሰዳቸውንም መረጃዎች ያመለክታሉ። በኢትዮጵያ የተፋፋመውን አመጽ ለመቆጣጠር በንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት የተለያዩ እርምጃዎች ተወሰደዋል፤ ከእነዚህም መካከል ወታደሮችን በአዲስ አበባ ከተማ ቀበሌዎችና ‘ቁልፍ’ ቦታዎች ለጥበቃ እንዲሰማሩ ተደርጓል። የሕዝቡን ሸክም ለማቃለል የነዳጅ ዋጋ ቅነሳን የሚያካትት ኢኮኖሚያዊ እርምጃዎች እንደሚወስድ ይፋ ተደርጓል።
ለወታደሮች የደመወዝ ጭማሪ ለማድረግ መወሰኑ ተገልጿል። ስለዚሁ የካቲት 66ቱ አብዮት በፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ ‹‹የኢትዮጵያ ታሪክ (1847- 1983)›› መጽሐፍ እና በተለያዩ ሰነዶች ላይ እንደተመለከተው፤ የየካቲት 66ቱ አብዮት ተማሪዎች፣ የመንግስት ሰራተኞች፣ ወታደሮች፣ የፋብሪካ ሰራተኞች በሥርዓቱ ላይ ያደርጉት የነበረው ተቃውሞ በከፍተኛ ሁኔታ ተጋግሎ ታይቷል። በዚህ ሁኔታ የተቀጣጠለው አብዮት እየተፋፋመ ሄደ። አመጹም ወደ ሕዝቡ ወረደ።
የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ ‹‹ሕዝባዊ አመፅ›› በሚለው የመጽሐፋቸው ርዕስ በወቅቱ የነበረውን ሁነት ‹‹በየካቲት 1966 ገንፍሎ የወጣው ሕዝባዊ አመፅ በመሰረቱ የከተሜ ንቅናቄ ነበር። አልፎ አልፎ አንዳንድ ጉምጉምታ ቢሰማም ገጠሬው በአብዛኛው ድምጹን አጥፍቶ ቁጭ ብሎ ነበር። በከተሞች ግን የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች (ተማሪዎች፣ መምህራን፣ የመንግሥት ሠራተኞች፣ ወታደሮች እና ሥራ አጥ ወጣቶች) ሥርዓቱን አሻፈረኝ ብለው ተነሱ።›› ሲሉ አብራርተውታል። ብዙ ጥናቶች ያመለከቱትም ጠቅሰው፤ ይህ ሕዝባዊ አመጽ የተለኮሰው በነገሌ ቦረና የነበረው የ4ኛው ክፍለ ጦር ወታደሮች በጥር ወር መጀመሪያ ላይ ባነሱት አድማ መሆኑን አመልክተዋል።
በነገሌ ቦረና የነበረው የአራተኛ ክፍለ ጦር ወታደሮች ጥያቄ የደመወዝና ሌሎች የኑሮ ሁኔታዎችን የተመለከተ ቢሆንም፣ በውስጡ ግን ፖለቲካዊ ብሶቶች ነበሩበት። በመኮንኖችና በወታደሮች መካከል የነበረው የጌታና ሎሌ ግንኙነት ሁኔታውን አባብሶታል። በሕዝቡ ዘንድ ደግሞ የባላባትና የገባር ግንኙነትም ሕዝቡን ያመረረ ሥርዓት ነበር።
ውስጥ ለውስጥ ሲብላላ የቆየው የወታደሩ እንቅስቃሴ የመገናኛ ብዙኃንን ትኩረት አገኘ፤ ይህም የሕዝቡን ትኩረት በመሳብ አመጽ እንዲቀጣጠል አደረገ። የሥራ ማቆም አድማዎች ተጠናክረው ቀጠሉ ። የታሪክ ተመራማሪው የፕሮፌሰር ባህሩ መጽሐፍም ‹‹በመጀመሪያ የካቲት 11 ቀን 1966 ዓ.ም የአገሪቱ መምህራን ጠቅላላ የሥራ ማቆም አድማ መቱ›› ይላል። ተማሪዎች በሥርዓቱ ላይ ተቃውሞ ማሰማት ከጀመሩ በርካታ ዓመታትን ያስቆጠሩ ቢሆን፣ ይህ ወቅት ደግሞ ከዚህ ይበልጥ እንዲገፉበት አድርጓል።
የመምህራን የስራ ማቆም አድማው የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎችንና የወላጆችንም ድጋፍ እያገኘ መጣ። ባለታክሲዎች ደግሞ በወቅቱ የነበረውን የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ተከትሎ በነዳጅ ዋጋ ላይ የተደረገውን የ50 በመቶ ጭማሪ ምክንያት በማድረግ ተመጣጣኝ የታሪፍ ጭማሪ እንዲደረግ የሥራ ማቆም አድማ አደረጉ።
ይህ አድማ ደግሞ የተማሪዎችንና ሥራ አጥ ወጣቶችን ድጋፍ በማግኘቱ ወደ አመጽነት ተቀየረ። የታክሲዎች ጠላት ናቸው የሚባሉት አውቶብሶችንና ሌሎች ባለቤትነታቸው የመንግሥት ነው የሚባሉ ተሽከርካሪዎችን መሰባበር ተጀመረ።
ገንፍሎ የወጣው ሕዝባዊ ቁጣም ሥርዓቱን አስደነገጠው። ይህን ተከትሎ የንጉሱ አገዛዝ እርምጃዎች ቢወስድም እድሜውን ሊያራዝሙለት ግን አልቻሉም። አብዮት ፈነዳ፤ ልክ በዛሬዋ ቀን የካቲት 20 ቀን 1966 ዓ.ም የወታደሩ አመጽ ተስፋፍቶ አዲስ አበባ የሚገኘው የአራተኛ ክፍለ ጦር፣ የጦር ሠራዊት፣ አየር ኃይል እና የዋና መሥሪያ ቤት ወታደሮች በከተማው ቁልፍ ቦታዎችን በቁጥጥራቸው ሥር አዋሉ።
በጸሐፊ ትእዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ የሚመራው ካቢኔ የካቲት 21 ቀን ከሥራ ተሰናበተ። ንጉሡ ሥራውን በለቀቀው ካቢኔ መተካት የግድ ሆነባቸው። የመገናኛ ሚኒስትር የነበሩትን ልጅ እንዳልካቸው መኮንንን ጠቅላይ ሚኒስትር ጄኔራል ዐቢይ አበበን የመከላከያ ሚኒስትር አድርገው ሾሙ። የተደናገጠው መንግሥት መላ ያስቀመጠ መስሎት የካቲት 23 ቀን የነዳጅ ዋጋ ቀነሰ። አሁን እርምጃው ለውጥ አለመጣም።
ወታደሮቹም እርምጃ መውሰዳቸውን ቀጠሉ። በርካታ የጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተወልድ ካቢኔ አባላት የሆኑ ሚኒስትሮችንም በቁጥጥር ስር አዋሉ። በወቅቱ አዲስ አበባ ላይ ሊካሄድ ተዘጋጅቶ የነበረው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ስብሰባ በአመጹ ሳቢያ ተሰረዘ።
መረጃዎቹ እንደገለጹት፤ የየካቲት አብዮት ገናና ነበር። ‹‹አብዮት›› የተባለበት ምክንያትም፤ የታሪክ ማርሽ የቀየረ በመሆኑ ነው። የታሪክ ደማቅነቱ ብቻም ሳይሆን የፈጠረው ሹም ሽር የኢትዮጵያን መንግስት መሪውን ከተመሪው፣ ሰራተኛን ከአሰሪው፣ ሹሙን ከምንዝሩ ሳይለይ የገለባበጠ በመሆኑ ነበር። የየካቲት አብዮት የክስተት አብዮት ብቻ አልነበረም። ዛሬ ኢትዮጵያ ላለችበት ሁኔታ ፈር ቀዳጅ የሆኑ ሀሳቦች ይዞ የመጣ አብዮት የፈነዳበት ነው።
ከአብዮቱ በፊት የመሬት ሥሪት፣ የዴሞክራሲ መብት፣ የሰራተኛ የመደራጀት መብት፣ የብሔርና የብሔረሰብ መብት እና ሌሎችም ጥያቄዎች የዩኒቨርሲቲውን መድረክ ይዘውት ነበር።
ተማሪዎቹ የታገሉለት አብዮት በወታደሩ ተጠለፈ፤ ወታደሩ ራሱን ደርግ ብሎ በመሰየም ተማሪዎችን፣ ሰራተኞችንና ሌሎች ለአብዮቱ መምጣት አስተዋጽኦ ያደረጉትን ገሸሽ አድርጎ ስልጣኑን ለብቻው ተቆጣጠረ። ያለምንም ደም ኢትዮጵያ ትቅደም የሚለው መሪ ሃሳብ ፣ የተማሪዎች የዴሞክራሲ ጥያቄ እንደገና ጥያቄ ውስጥ ገቡ።
ከዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የለውጥ አቀንቃኝ ተዋንያን በአብዛኛው በጊዜው ለተነሱት ጥያቄዎች የ‹‹ግራ ዘመም ርዕዮት›› ነው ባዩ እየበዛ፤ በአማራጩ የ‹‹ቀኝ ዘመም›› አስተሳሰብ በአድሃሪነት ተፈርጆ ማረፊያ ቤት ተቀመጠ። ይህ እንቅስቃሴ ኢትዮጵያ ለሺህ ዘመናት የኖረችበትን ንጉሣዊ ሥርዓት እስከወዲያኛው ያሰናበተ አብዮት ሆነ። የየካቲት አብዮት ያስከተለውን መፈንቅለ መንግስትም ‹‹አዝጋሚው መፈንቅለ መንግሥት›› ይሉታል የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ባህሩ። ውስጥ ለውስጥ ሲብሰለሰል የቆየው የወታደሩ፣ የሰራተኛው፣ የተማሪው… ሁሉ ብሶት
ለዚህ ነው አዝጋሚው መፈንቅለ መንግሥት የተባለው። ፕሮፌሰር ባህሩ የአብዮቱን ዱብ ዕዳነት ሲገልጹ ደግሞ፤ ለአሥር ዓመታት ያህል የታገሉለትን ተማሪዎችንም እንደ ማዕበል ነው የበላቸው ይላሉ። ‹‹አብዮት የሚለውን ቃል ብዙዎች ያጤኑት ከአብዮት ፍንዳታ በኋላ ነው›› ይሉታል ፕሮፌሰሩ። የክስተቱን ድንገተኝነት ለመግለጽም ‹‹አብዮት ፈነዳ›› ተባለ። ልክ እንደማንኛውም ፍንዳታ አብዮቱ በመንግሥትም ሆነ በጠላቶቹ ላይ መደነባበርና መደናገርን አስከትሏል።
በዚህም ምክንያት ነው አገሪቱን ለፍፁም ወታደራዊ አገዛዝ አሳልፎ የሰጣት። ከሌሎች አገራት አብዮቶች የሚለየውም አብዮቱን ያቀጣጠለው አካል አብዮቱን መቆጣጠር አለመቻሉ ነው ተብሏል። የየካቲቱ አብዮት ከፈረንሳይና ከሩሲያ አብዮቶች ጋር እንደሚመሳሰል ነው የታሪክ ምሁሩ የሚገልጹት። በሦስቱም አገሮች አብዮቱ ንጉሣዊ ሥርዓትን አስወግዶ ለሽብር አመጽ ተዳርጓል።
ያም ሆነ ይህ የየካቲት አብዮት በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ጉልህ ሚና አለው። በመግቢያው አካባቢ እንደገለጽነው፤ የየካቲት አብዮት ሲባል አንድ ወይም ሁለት ቀን የተከሰተ ሳይሆን ወሩን ሙሉ በተለያዩ ቀናት የተከሰተ ነው። የአብዮቱ ዋና ዋና ክስተቶች የካቲት ላይ ስለነበሩ እንጂ ከዓመት በላይ የዘለቀ አብዮት ነበር። ከላይ ከገለጽናቸው በተጨማሪ በየካቲት ውስጥ ከተከሰቱት ጥቂቶችን አስታውሰናችሁ እናጠቃል።
ስለ ልጅ እንዳልካቸው መኮንን በጥቂቱ
ጳጉሜ 4 ቀን 1920 ዓ.ም የተወለዱት ልጅ እንዳልካቸው መኮንን አባታቸው ቢትወደድ መኮንን እንዳልካቸው፣ እናታቸው ደግሞ ወይዘሮ ዘውዲቱ መንገሻ ይባላሉ። የትውልድ ቦታቸው አዲስ አበባ ልዩ ስሙ ‹‹አቧሬ›› ነው። ጠላት አገራችንን በወረረ ጊዜ አባታቸው መኮንን እንዳልካቸው ከዘመቱበት የኦጋዴን ግንባር ሲሄዱ ልጅ እንዳልካቸው ከአባታቸው ተነጥለው ስለቀሩ አምስቱን የመከራ ዓመታት ያሳለፉት ሰሜን ሸዋ ውስጥ ከአያታቸው ከወይዘሮ አቦነሽ ተክለማሪያም ጋር ነበር።
አባታቸው በ1933 ዓ.ም. በድል ከገባው ሰራዊት ጋር እንደተመለሱ እንዳልካቸው መኮንን ከአያታቸው ጋር ወደ ትውልድ ከተማቸው መጡ።
ሁኔታዎች ሲረጋጉ ልጅ እንዳልካቸው የአንደኛና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በሚሲዮን እና በቀዳማዊ አጼ ኃይለሥላሴ ትምህርት ቤቶች (በኮተቤ) አጠናቀቁ። ልጅ እንዳልካቸው መኮንን፣ አገራቸውን በበርካታ መስሪያ ቤቶች ያገለገሉ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአታሼነት ስራቸው ይጠቀሳል።
ለስድስት ዓመታት ያህል በዚሁ መስሪያ ቤት ካገለገሉ በኋላ ምክትል ሚኒስትር ሆኑ። ከዚህ ጊዜ በኋላም ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ለጉብኝት ባህርማዶ በሚሄዱ ወቅት አብረው እየተጓዙ የአገራትን ሁኔታ የመጎብኘት እድል ገጥሟቸው ነበር። በ1948 የትምህርት ሚኒስቴር ምክትል ሚኒስትር ሆነው ተሾሙ።
በመቀጠልም በእንግሊዝ የኢትዮጵያ አምባሳደር፣ የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስትር፣ የካቢኔ ሚኒስትር፣ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ደግሞ የኢትዮጵያ ቋሚ መልእክተኛ፣ የፖስታ የመገናኛ እና የቴሌኮሙኒኬሽን ሚኒስትር በመሆንም አገልግለዋል። ኢትዮጵያ ከ1959 ዓ.ም እስከ 1961 ዓ.ም. በነበረውየ3 ዓመታት ጊዜ ውስጥ የጸጥታው ምክር ቤት ጊዜያዊ አባል ስለነበረች፤ ልጅ እንዳልካቸው ሁለት ጊዜ ተመርጠው የጸጥታውን ምክር ቤት በፕሬዚዳንትነት መርተዋል።
በዚሁ የጸጥታው ምክር ቤት የፕሬዚዳንትነታቸው ዘመን በመካከለኛው ምስራቅ፣ በቆጵሮስ፣ በሮዴሽያ፣ በናሚቢያና በቼኮስሎቫኪያ የደረሱ ቀውሶችን አስመልክቶ የተጠሩ ስብሰባዎችን መርተዋል። እንዲሁም በእስራኤልና በግብጽ መካከል ጦርነት በተካሄደበት ጊዜ አስታራቂ መልዕክተኛ ሆነው ያገለገሉትን ሚስተር ጉናር ጃሪንግን የሰየሙት ልጅ እንዳልካቸው መኮንን ነበሩ። ልጅ እንዳልካቸው መኮንን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት ጉባኤ ላይ ለሮዴዥያና ለደቡብ አፍሪካ ነጻነት ተሟግተው ነበር።
በየካቲቱ አብዮት ንጉሱ ለሁለተኛ ጊዜ በቴሌቪዥን ቀርበው የጸሐፌ ትእዛዝ አክሊሉን ካቢኔ የስንብት ጥያቄ ተቀብለው፣ በምትካቸውም ልጅ እንዳልካቸው መኮንንን ጠቅላይ ሚኒስትር ተደርገው ተሾሙ።
ልጅ እንዳልካቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው መሾማቸው አንዳንድ ደጋፊዎቻቸውንና መሰል መሳፍንትን ያስደሰተ ቢሆንም በአብዛኛው ተራማጅ ምሁራን እና በተማሪዎች ዘንድ ተቀባይነት አላገኘም። ልጅ እንዳልካቸው ይህን አገራዊ ኃላፊነት ሲቀበሉ ሁኔታዎችን መልክ ለማስያዝና ለማረጋጋት የተቻላቸውን አድርገዋል።
ልጅ እንዳልካቸው በተቃውሞ ሰልፍ መካከል መጋቢት 11 ቀን 1966 ዓ.ም. የሕገ መንግሥት አርቃቂ ጉባኤ አባላት ዝርዝር ይፋ አደረጉ። በዝርዝሩ የተጠቀሱት አባላት በጣት ከሚቆጠሩት በስተቀር አብዛኛዎቹ በዘውዳዊ ሥርዓት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ወይም ከሥርዓቱ ጋር ግንኙነት የነበራቸው በመሆኑ በመምህራንና ተማሪዎች ዘንድ ዝርዝሩ ተቀባይነት አልነበረውም።
ተቃውሞ ሰልፉና ጥያቄዎቹ እየተጠናከሩና ውጥረቱ በተለይ በአዲስ አበባ እየተባባሰ በመምጣቱ ይህንኑ የሚያስደርጉት ከሥልጣን የለቀቁት ባለሥልጣናት ናቸው የሚል በሰፊው ይወራ እንደነበርም አንዳንድ ሰነዶች ያመለክታሉ። ልጅ እንዳልካቸው መኮንን ከደርግ ጋር መስራቱ አስቸጋሪ ሆነባቸው።
ደርግም እንዳልካቸው አልተመቹትም። ከጠቅላይ ሚኒስትርነታቸው ማንሳት አስፈላጊ መሆኑን ስላመነበት ሊቀመንበሩ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያም ሀሳቡን በደርግ ስብሰባ ላይ አቀረቡት። ‹‹ኢትዮጵያ ትቅደም የሚለውን አላማችንን በስራ ላይ ለመተርጎም አስቸጋሪ እየሆነብን መጥቷል። ዋናውን የመንግሥት ስልጣን የያዙት ጠቅላይ ሚኒስትር እኛ እንደምንፈልገው ሊሄዱልን አልቻሉም። በእርግጥ የተማሩ ናቸው። ነገር ግን የመሳፍንት ወገን በመሆናቸው የእኛን እንቅስቃሴ አልወደዱትም።
ከእኛ ጋር ሳይመካከሩ ውሳኔ ይሰጣሉ። ይሾማሉ፣ ያዛውራሉ፣… ስለሆነም መንግሥታዊ አሰራሩንም ለመቆጣጠር ብሎም ለመምራት ተቸግረናል። ስለዚህ እንዳልካቸው ከያዙት የሥልጣን ቦታ መነሳት አለባቸው።›› ብለው ኮሎኔል መንግሥቱ ለተሰበሰቡት የደርግ አባላት ጠቆም አደረጉ። ከዚያም ልጅ እንዳልካቸው ከሥልጣናቸው ወርደው በቤታቸው የቁም እስረኛ ሆኑ። ከውጭ ግንኙነት እንዳያደርጉም የስልክ መስመራቸው እንዲቋረጥ ተደርጓል። በመጨረሻም ኅዳር 14 ቀን 1967 ዓ.ም ደርግ በጭካኔ ከገደላቸው 60ዎቹ ውስጥ አንዱ ሆነዋል።
ዋለልኝ አየለ
አዲስ ዘመን የካቲት 20 /2014