ኢትዮጵያ እና የቀድሞው አፍሪካ አንድነት ድርጅት የአሁኑ የአፍሪካ ኅብረት ቢፈቱት የማያልቅ እጅጉን የተሳሰረ ታሪክ አላቸው።ከመስራቾቹ አንዱ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ናቸው።የኅብረቱ መቀመጫ አዲስ አበባ ናት።አብዛኞቹ የኅብረቱ አባል አገራት በነጻነት ትግላቸው ወቅት ኢትዮጵያ በብዙ መልኩ ደግፋቸዋለች።ሌላም ሌላም፡፡
እዚህ ላይ ሊጨመር የሚገባው እና ብዙ ያልተወራለት ጉዳይ አለ፤ የኅብረቱን መዝሙር እና ሰንደቅ ዓላማም ያዘጋጁት እነዚሁ ኢትዮጵያውያን መሆናቸው።
የኅብረቱን መዝሙር ያዘጋጁት ብላቴን ሎሬት ፀጋዬ ገብረ መድህን ሲሆኑ፣ የኅብረቱን ሰንደቅ ዓላማ ያዘጋጁት ደግሞ ትውልደ ኢትዮጵያዊው ያዴሳ ቦጂያ ናቸው።ዛሬ ስለ እነዚህ የኢትዮጵያም የአፍሪካም እንቁዎች ጥቂት እንላለን።በቅድሚያ ስለ ሎሬት ፀጋዬ ሸገር ብሎግ የተሰኘ ድረ ገጽ ካሰፈረው ጽሑፍ ጥቂት እንዋስና እናስታውሳቸው፡፡
የመዝሙር፣ግጥም
ደራሲ ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን
ፀጋዬ ገብረ መድህን (1928-1998) ባዳ ተብላ በምትታውቅ አምቦ ከተማ አካባቢ በምትገኝ ተራራማ አካባቢ ተወለዱ። በአምቦ ማዕረገ ሕይወት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ትምህርት ቤት ከዚያም ጄኔራል ዊንጌትና በአዲስ አበባ የንግድ ትምህርት ቤት በአገር ውስጥ ትምህርታቸውን ተከታትለዋል፤ ከዚያም በቺካጎ ብላክስቶን በሕግ ትምህርት ተመርቀዋል፤ በ1952 በለንደን ከተማ የቴአትር ትምህርታቸውን ደግሞ በሮያል ኮርት ቴአትርና በፓሪስ ኮሜዲ ፍራንሴዝ ተከታትለዋል።
ያኔ በውጭ አገር ተምሮ ወደ አገር ቤት መመለስ ኩራት ነበርና እሳቸውም ወደ አገራቸው ተመልሰው ከ1954 እስከ 1964 ዓ.ም በብሔራዊ ቴአትር በአርቲስቲክ ዳይሬክተርነት አገለግለዋል። ከዚያም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቴአትር ትምህርት ክፍልን አቋቁመዋል። በ1960ዎቹ ደርግ አብዛኛውን የቴአትር ሥራዎቻቸውን ያገደባቸው ሎሬት ፀጋዬ፣ እሳቸውንም አስሯቸው ነበር።
ብላቴን ሎሬት ፀጋዬ በርካታ ግጥሞችን፥ የቴአትር ሥራዎችን የተለያዩ መጣጥፎችንና ዘፈኖችን አበርክተዋል። እንደ አውሮፓ አቆጣጠር በ2002 የብላቴን ሎሬት ፀጋዬ ገብረ መድህን ‹‹አፍሪካዊ በመሆኔ እኮራለሁ›› (“Proud to be African”) በሚል የጻፉት ግጥም በአዲስ በተመሰረተው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት በሕዝብ መዝሙርነት ከብዙ ተፎካካሪዎች ልቆ ተመርጧል።
በትምህርት እየጎለመሱ ሲሄድም ደራሲነቱን ገጣሚነቱን እንዲያ ሲልም ፀሐፊ-ተውኔትነቱን በዋነኛነት፣ በጎልማሳነት ዘመኑ ደግሞ ማኅበረሰባዊ ሃያሲነት እና የአፍሪካ የሰው ዘር፣ ቋንቋ እና ባህል ጠቢብነትን አክለውበት እስከ ዕለተ ሞታቸው ዘልቀዋል።
በነገራችን ላይ “ባለቅኔ ሎሬት” (Poet Laureate) የተሰኘው ማዕረግ የተገኘው ከጥንታዊት ግሪክ (በኋላም ሮማውያን) ጥበበኞችንና አሸናፊዎችን የማክበር፣ የመሾምና የመሸለም ልማድ እንደሆነ የታሪክ ማስረጃዎች ይጠቁማሉ።ወይራ የባለ ቅኔዎች የበላይ ጠባቂ የሆነው የአፖሎ ቅዱስ ዛፍ ነው ተብሎ በጥንታዊ ግሪካውያን ይታመንበት ስለነበር ነው፤ በተሸላሚዎች አናት ላይ በወይራ ዘለላ የተጐነጐነ አክሊል (Laurel Crown) ይደፋላቸው ነበር፡፡
በዘመናዊው የዓለም ታሪክ፤ “የባለ ቅኔ ሎሬት” ማዕረግ ሹመት ሆኖ በሥራ ላይ መዋል የጀመረው በ17ኛው ክፍለ ዘመን እንግሊዝ ውስጥ ሲሆን፣ ማዕረጉም የሚሰጠው የላቀ ሥራ ላበረከተ ባለ ቅኔ ነበር።ለፀጋዬ ገብረ መድኅን በ”ባለ ቅኔ ሎሬት ማዕረግ” መጠራት ምክንያት የሆነው በዓለም አቀፍ የባለ ቅኔ ሎሬቶች ሕብረት የዓለም ባለቅኔዎች ጉባኤ (United Poets Laureate International – World Congress of Poets) ነው።
በፊሊፒንስ ዋና ከተማ ሚኒላ ውስጥ የተመሠረተው የዚህ ዓለም አቀፍ ማኅበር ዓላማ፤ በጥበብ (በተለይም በቅኔ) አማካይነት ዓለም አቀፋዊ ወንድማማችነትንና ሰላምን ማራመድ ነው።ማኅበሩ በሁለት ዓመት አንድ ጊዜ በሚያካሂደው የዓለም ባለቅኔዎች ጉባኤ ላይ ከመላው ዓለም የተሰባሰቡ ባለ ቅኔዎች ሥራዎቻቸውን ለጉባኤው ያቀርባሉ፤ እርስ በእርስም ስለ ቅኔ ይወያያሉ፣ ከዚህ በተጨማሪም ቅኔን የተመለከቱ ጥናታዊ ጽሑፎች በጉባኤው የሚቀርቡ ሲሆን ለምርጥ ባለ ቅኔ ደግሞ የምስክር ወረቀት፣ ሜዳልያ እና የተከበረው ባለ የወይራ ዘለላ የወርቅ አክሊል (Golden Laurel Crown) ይበረከትለታል።
ከሐምሌ 14 እስከ 18 ቀን 1989 ዓ.ም በእንግሊዝ፣ ባኪንግሀምሻየር ክፍለ ግዛት፣ ሀይ ዋይኮምብ ከተማ ውስጥ በተካሄደው አሥራ አምስተኛው የዓለም ባለ ቅኔዎች ጉባኤ ላይ፤ ፀጋዬ ገብረ መድኅን “ኤዞፕ” የተሰኘውን ቅኔያቸውን ከማሰማታቸውም ሌላ ስነ ግጥም ጨለማን ድል አደረገ፤በዚህም ዓለም ዳነች›› “Poetry Conquered Darkness and the World was Saved” በሚል ርዕስ ጥናታዊ ጽሑፍ አቅርበዋል።
የዓለም ባለ ቅኔዎች አሥራ አምስተኛ ጉባኤ፤ ፀጋዬ ገብረ መድኅን በአገሩ ቋንቋና በእንግሊዝኛም ጭምር ያበረከቷቸውን ግጥሞች፣ ቅኔዎች እና ሌሎች የጥበብ ሥራዎችን በመመርመር፤ ሥራዎቻቸውም የሰው ልጅን እኩልነት፣ ነፃነት፣ ወንድማማችነትና ፍቅር አበክረው የገለጡ መሆናቸውን ተረድቶ ባለ ቅኔ ሎሬት የሚያገኘውንና የተከበረውን ባለ ወይራ ዘለላ የወርቅ አክሊል ሸልሟቸዋል።
እስከዚያን ጊዜ ድረስ ይህንን ባለ ወይራ ዘለላ የወርቅ አክሊል ከተሸለሙት ታዋቂ የዓለም ባለ ቅኔዎች መካከል የአሜሪካው ባለ ቅኔ ሎሬት ሮበርት ትንስኪ፣ የሩስያው ኢጐር ሚኮሌሴንኮ፣ የፈረንሳዩ አሲት ቻክሮቮርቲ እና የእንግሊዙ ጆን ዋዲንግተን ፌዘር እንደሚገኙበት ለማወቅ ተችሏል፡፡
ፀጋዬ ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት መዝሙር አበርክቷል፤ ይህ መዝሙር በኋላም አፍሪካ ኅብረት ተቀብሎ ያስቀጠለው መዝሙር ‹‹ሁላችንም አንድ እንሁን፤ አብረን እንደሰት›› Let us all unite and celebrate together በሚል ርዕስ የተጻፈ ነው።ይህ ግጥም በብዙ ቋንቋዎችም ተተርጉሟል።ሎሬት ፀጋዬ ግጥሙን ከጻፈው በኋላ ኬንያዊው አርተር ሙዶጎ ኬሞሊ ቅንብሩን በ1985 እ.ኤ.አ በሴኔጋል ዳካር ሰርቶታል፡፡
የሎሬት ፀጋዬ ግጥም መልዕክት ጠቅለል አርገን ስንመለከተው ሁላችንም አንድ እንሁን ለነጻነታችን የተከፈለውን ዋጋ እና ድል እንዘከር የሚል መልዕክት አለው።አፍሪካውያን ነጻነታቸውንና እና አንድነታቸውን ለመጠበቅ አብረው እንዲሠሩም ያስገነዝባል።
አፍሪካውያን እጣ ፈንታችንን የቀረጹትን፣ ያስተሳሰሩንን ገመዶች እንጠብቅ ይላል።በምድር ላይ ጽኑ ሰላም እና ፍትህ ይሰፍን ዘንድ የአፍሪካ ወንድ እና ሴት ልጆች አብረው መሥራት እንዳለባቸውም ያስገነዝባል።አንድ ሆነን የምንችለውን ሁሉ ለአፍሪካችን ለእስትንፋሳችን እናድርግ ይለናል።
ይህ መዝሙር በመጀመሪያ ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት በመዝሙርነት የጻፈው ሲሆን፣ የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን የተካው የአፍሪካ ኅብረት ሲመጣ ደግሞ መዝሙሩን ሙሉ ለሙሉ ተቀብሎታል።መዝሙሩ በተመረጠበት ዓመትም የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ለእዚህ ሥራው ለሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መዝሙር ሽልማት በሚል ሽልማት አበርክቶለታል።
ፀጋዬ በ1990 ዓ.ም ለሕክምና ወደ ማንሃታን በሄዱበት ነበር ያረፉት። ፀጋዬ ከማረፉ አራት ዓመታት ቀደም ብሎም በዶ/ር ኄራን ሠረቀብርሃን አማካይነት በዋሽንግተን ዲሲ የፀጋዬ ግጥሞች በሲዲ ተቀርፀው ተመርቀዋል። የስንብት ዝግጅት ይሆን። ትንቢት አስቀድሞ ለነገር እንዲሉ። የማሳረጊያ ግጥሙም ይህንን ተስፋ ቢስነትን አመላካች ይሆን?
የማይድን በሽታ ሳክም
የማያድግ ችግኝ ሳርም
የሰው ሕይወት ስከረክም
እኔ ለኔ ኖሬ አላውቅም የሚል ነው ግጥሙ፡፡
(አቤል ገ/ኪዳን)
አዲስ ዘመን ጥር 29/2014