ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ከውስጥ እና ከውጪ ሃይሎች ጋር የህልውና ጦርነት ላይ ናት። በእርግጥም ኢትዮጵያ በዘመናት መካከል ያጋጠሟትን ፈተናዎች እና ያጋጠሟትን የክፋት ኃይላት ሁሉ ድል በመንሣት ታፍራና ተከብራ ነጻነቷን አስጠብቃ ኖራለች። ጀግኖች እናቶችና አባቶች የውጭ ወራሪዎችን ብቻ ሳይሆን የውስጥ ባንዳዎችን በማንበርከክ የዛሬይቱን ኢትዮጵያ በነፍሳቸው ተወራረደው አቆይተዋታል። በታሪክ አጋጣሚ ዛሬም ኢትዮጵያ የአጠባ ጡቷን፣ የአጎረሰ እጇን የሚነክሱ ከሐዲዎች፣ ሊያዳክሟትና ሊበትኗት ከቅርብና ከሩቅ ከተነሡ ኃይላት ጋር በመመሳጠር አቆብቁበው ተነስተዋል። ስለዚህ ሃገሪቱ ዛሬ የገጠሟትን ፈተናዎችን መሻገር እንድትችል በስነ ልቦናውም የጸና ህዝብ እንደሚያስፈልግ የስነ ልቦናው ባለሙያ ዶክተር ምህረት ደበበ ይናገራሉ።
ከግልጽ ውጊያ ባሻገር ሌሎች ተግዳሮቶችን ተቋቁሞ በድል ለመወጣት ተጨማሪ ቁርጠኝነት መስጠትና ዝግጁነት ከመላው ኢትዮጵያውያን የሚጠበቅ መሆኑንም ያመላክታሉ። በሌላ በኩል ያለንበት ዘመን ትክክለኛ፣ ያልተረጋጋ መረጃዎች በግራም በቀኝም የሚዘምብበት እንደመሆኑ፤ ስነ ልቦናዊ ጫና ያሳድራል። በመሆኑም ራስን አትርፎ ሃገርን ለማትረፍ መረጃዎችን የምንመላለስበት መነጽር ፤መረጃዎችን የምንመላለስበት ሂደት ደግሞ የእለት ከዕለት ተግባራችን ላይ ተጽእኖዎችን እና ሚዛናዊ እንዳንሆን የሚያደርጉ ነገሮች ሲፈጸሙ ይታያል። ስለዚህ ሃገር አሁን ካለችበት ሁኔታ አንጻር የኢትዮጵያ ሥነ ልቦና ምን መሆን ይኖርበታል? ሃገር በጦርነት ውስጥ ስትሆን ስነ – ልቦናችን እንዴት ይገነባል? የሚሉ አንኳር ጉዳዮች ማንሳት ያስፈልጋል።
በዚህ ረገድ የአእምሮ ሕክምና ስፔሻሊስት እና የ ”ሌላ ሰው” ደራሲ የሆኑት ዶክተር ምህረት ደበበ ሲያብራሩ፤ የሃገር ህልውና ሁላችንንም የሚኮረኩረን፣ የሚከነክን ብቻ ሳይሆን የሚያስጨንቀን እና ምን ላድርግ ብለን በግለሰብም በመንግስትም የምናስበው ነገር ነው። በአሁኑ ጊዜ ለኢትዮጵያ ብዙ ገንዘብና መሳሪያ ብቻ ሳይሆን ብዙ የጽናት እሴት የሚያስፈልግበት ጊዜ ላይ ነን። በዚህች አገር ዛሬ ላይ የተገኘን ሁሉ በአንድ ሃሳብ ላይ ባንግባባም ማመን ያለብን ባንቀበለውም እውነት የሆነ ጉዳይ እንዳለን ያስታወሱት ዶክተር ምህረት፤የቆምንባት ምድር፣ የምንሰየምበት ዜግነት፣ የምንለይበት ማንነት በዚህች አገር ላይ የጸና ነው። ሀገር ለማጽናት ደግሞ ጽኑ ሆኖ መቆም ግድ ይላል ሲሉ በአሁኑ ወቅት ከገባንበት ሁኔታ ለመውጣት ጽናት እንደሚያስፈልግ ያመላከቱት።
ዶክተር ምህረት በተለየ መልኩ በአሁኑ ወቅት ለሃገር የሚያስፈልገው ጽናት የሚፈጠረው የመጀመሪያው ያለንን ችግር አጥርቶ መረዳት ከመቻል እንደሆነ ይናገራሉ። ተግዳሮቶቻችንን በትክክል ወይም በበቂ ካልተረዳን ለጽናት ያለን መነሳሳት በጣም ያነሰ ይሆናል። ለምሳሌ አሁን ያለውን የኢትዮጵያን ችግር በኢትዮጵያውያን ወንድማማቾች መካከል የተፈጠረ የሃሳብ አለመግባባትና የሃይል ግጭት ብቻ አድርገን ከወሰድነው የሚኖረን ጽናት በጣም ያነሰ ይሆናል።
ከሃገር ህልውና ጋር ስንመለከተው ኢትዮጵያ ውስጥ የተፈጠሩ አለመግባባቶችና አለመስማማቶች በአላማ ልዩነቶች እንዳሉ ሆነው ከውጪ ያለውንም አለም ዓቀፋዊም ሆነ አካባቢያዊ ሁኔታን ከተገነዘብን ፤የኢትዮጵያን ህልውና ከመኖር አንጻር ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያ ልትደርስ ከምትችለው ደረጃ እንዲሁም ትውልዳዊ እድልን ሊያጨናግፍ የሚችሉ ችግሮችን ስንረዳ ተግዳሮቶቹን በሃገር ውስጥ ካሉ ነገሮች ጋር ብቻ አናያይዘውም።
ሌላው ፅናትን የሚፈጥረው አንዱ የአላማ ትልቅነት መሆኑን የገለጹት ዶክተር ምህረት፤ የአላማ ትልቅነት ደግሞ በአሁኑ ጊዜ ባሉን ችግሮች ላይ ተመስርቶ የሚፈጠር ሳይሆን እድሎች ላይ ተመስርቶ የሚፈጠሩ ናቸው። በአለም ላይ ከምዕራብ ወደ ምስራቅ ከፍተኛ የሃይል ሽግግር፣ ብዙ ውጣ ውረዶች የሚደረጉበት ፣ትልልቅ የሃይል ለውጥ እየተደረገ ይገኛል። ብዙ አሃጉራትና ሃገሮች የነቁበት ጊዜ ስለሆነ በዚህ ውስጥ ብዙ ወዳቂና ተነሺ ሃገሮች ይኖራሉ ።ስለዚህ አሁን ለኛ ጽናት ትልቁ ምክንያት፤ያለብን ውስጣዊ ችግር ብቻ ሳይሆን፤ እንደ ሃገር የትነው ልንደርስ የምንችለው የሚለውንም ጉዳይ ማሰብ ያስፈልጋል።
“ጽናት ካለንበት ችግር ይልቅ፤ የምንደርስበትን ቦታ አጥርቶ የማየት ክፍሉ ይበልጣል የሚሉት ዶክተር ምህረት፤ ፅኑ ሰዎች ወደፊት የሚያስፈነጥራቸው የችግሩ ህመም ሳይሆን የእድሉ ትልቅነት ነው። በሌላ በኩል ደግሞ አለማችን ላይ ትልልቅ የሚባሉ ስልጣኔዎች የተፈጠሩት እንዲሁም እኛ ትልልቅ ጦርነቶችን ማሸነፍ የቻልነው ‘’የሚያጋጥመን ችግር ምን ያህል ሊያመን ይችላል” ከሚለው ተነስተን ሳይሆን፤የሚመጣውን ብሩህ ዘመን ፣የሚመጣውን ትልቅ እድል፣ ለሚቀጥለው ትውልድ ጥለን የምናልፈውን ነገር ከመመልከት መሆኑን ይናገራሉ። ስለዚህ በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያውያን ካለብን የእርስ በእርስ ቁርሾ ፣ግጭት ፣የአላማ ግልጽ አለመሆን በተሳሳቱ አላማዎች ከመቆምና እርስ በእርስ የራስን ነገር ከማጥፋት መውጣት እንደሚያስፈልግ በአጽንኦት ያስቀምጣሉ።
ጽናት ማለት ያለፈን ታሪክ የአሁኑን እድልና ወደፊት ልንደርስበት የምንችል ቦታ በግልጽ በማየት የሚፈጠር ትልቅ የሆነ ስነ ልቦናዊና ማህበራዊ እሴት መሆኑን የሚያመላክቱት ዶክተር ምህረት፤ የኋላ ታሪክን መመልከት ሌላው የጽናት ምንጭ መሆኑን ይናገራሉ።
የጥቁር ህዝቦች ድል የሆነውን የአደዋ ታሪክን ጨምሮ በሃገራችን ታሪክ ውስጥ በቂ የሆነ ፣ከኋላ ልንቀዳውና ጽናትን ሊፈጥርልን የሚችል ያለፈው ትውልድ ጥሎልን የሄደው ነገር መኖሩን ይጠቁማል። ኢትዮጵያ በኢኮኖሚው ከፍተኛ ደረጃ ላይ ስለደረሰች፤ በቴክኖሊጂ ፣በሚዲያ ፣በተለያዩ ዘርፎች ከፍተኛ ደረጃ ላይ ስለደረሰች ሳይሆን፤ “ያለፈው ትውልድ በውስጥ ጽናት ምን ሰርቶ አለፈ” የሚለውን በማየት መጽናት እንደሚቻል ስለሚያመላክት ነው። ስለዚህ በአሁኑ ጊዜ ይህ ትውልድ ከምን ጊዜውም በተለየ ሁኔታ የሚጠበቅበት ጽናት መሆኑን ያስገነዝባሉ።
በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ ብዙ ገንዘብ ፣መሳሪያ ሳይሆን ብዙ የጽናት ስነ ልቦናዊ እሴትን የሚያሻት ካለችበት ችግር ተስፈንጥራ የተሻለን ነገ ላይ የሚያደርሳት ስለሆነ ነው። ብዙ ጊዜ ጽኑ የሆኑ ሰዎች፣ ቤተሰቦች ፣ ድርጅቶች ፣ሃገሮች ችግርን እንደ መስፈንጠሪያ ቦርድ በመጠቀም ከነበሩበት ችግር ወደተሻለ ደረጃ የሚሄዱበት ሁኔታ ነው። ስለዚህ የመጽናት ስነ ልቦና ወይም የፅኑነት ስነልቦና ከሌሎች መሳሪያዎች ሁሉ ይበልጣል።
ጽኑ የሆኑ ሰዎችና ሃገራት አሸናፊነትንና የበላይነትን የሚቆናጠጡት በብዙ እጦት ውስጥ ሆነው ነው። ለዚህ በጽናት ውስጥ አለመናወጥ /ስፍራን አለመልቀቅ/ አለ። ጽናት ሁልጊዜ ወደፊት ተመልካች ነው ፤ወደ ኃላ የሚባል ጽናት የለም በፅናት ውስጥ መበታተን የለም። ጽናት የላላውን የሚያጠብቅ ፣የተበታተነውን የሚሰበስብ ፣ የደከመውን የሚያበረታ እንዲሁም ያላየነውን እምቅ አቅም የሚያወጣ ኃይል ነውና።
ዳንኤል ዘነበ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 25/2013