“ቁራሊዮ፤ ቁራሊዮ…” የሚለው ድምጽ ሲሰማ የሰፈሩ ልጆች ግርር ብለው ይወጣሉ። የቁራሊዮው መምጣት የሚያስደስታቸው ቁራሊዮ ሥራውን ጨርሶ ሲሄድ ሁሌም እየደጋገመ የሚናገራትን ንግግር ለማድመጥ ነው። ንግግሩን ልጆቹ ሰምተው እርሱ ከአካባቢው እስከሚለይ ድረስ በዜማ ይደጋግሙታል። በቁራሊዮ ድምጽ ተቀብለው፤ በቁራሊዮው የተለመደ መዝጊያ ንግግር ዜማ ይለያያሉ። “የከበርከው፤ የከበርሽው” የቁራሊዮ የመጨረሻ ንግግር ነው።
ለመጀመሪያ ጊዜ ቁራሊዮ ይህን ንግግር የተናገረው አንድ የማህበረሰብ አጥኚ በአካባቢው ተገኝቶ ለጥናቱ ግብዓት እንዲሆን ጥያቄ ሲጠይቅ ልጆች እየሰሙት መልስ በሰጠ ጊዜ ነበር። አጥኚው ብዙ ጥያቄዎች የጠየቀው ሲሆን በምላሹ ውስጥ “ያከበርከው” የሚል ቃል አይጠፋም ነበር። ከጥያቄዎቹ መካከል “በቁራሊዮ ሥራህ ጥሩ ዋጋ የሚያወጣው እቃ ምን አይነት ነው?” ሲባል “ሁሉም እቃ ጥሩ ዋጋ ያወጣል አክብረህ ከያዝከው።” ይላል በምላሹ። ሌላ ጥያቄ፤ “ቁራሊዮ በሥራህ ጉዳይ ሲጠሩህ ደስ የሚልህ ምን አይነት ሰዎች ናቸው?” ሲባል፤ ምላሹ “አክብረው የሚያናግሩኝ” ሲል ይመልሳል። … ጥያቄው ይቀጥላል ምላሹም ውስጥ “ያከበረከው” የሚለው ይቀጥላል። በዚህ መነሻነት ቁራሊዮ ሥራውን ጨርሶ ሲመለስ “ያከበርከው፤ ያከበርሽው” ሲል ይደመጣል። የሰፈሩ ልጆችም ተቀብለው “ያከበርከው፤ ያከበርከው፤ ያከበርከው” እያሉ በዜማ ይሸኙታል።
ከረጅም ዓመታት በኋላ ይህ የቁራሊዮ ሰው የፋብሪካ ባለቤት ሆኖ የአውድ ዓመት ፕሮግራም በቲቪ ላይ ይታያል። ልጆቹም ሰፈር ከመዋል አልፈው ወደ ወጣትነት ደርሰዋል። በልጅነታቸው የሚያውቁት ቁራሊዮ ያከበርከውን አንስቶ ሲያወራ ሰምተው እጅግም ተገርመው በያሉበት ይከታተሉታል፤ በልጅነት ትዝታ ውስጥ ሆነው።
የበዓል ሰሞን የሚተላለፉ መርሐግብሮች ታዋቂ የሚባሉ ሰዎችን የበዓል አከባበርን ማቅረብ ላይ ሲያተኩሩ ይስተዋላል። አንዳችን ከሌላችን ህይወት የምንማር መሆን ጥሩ የሚባል ሊበረታታም የሚገባው ነው። እያንዳንዱ ጉዞ ውስጥ ትምህርት አለ፤ ትምህርቱም ለተከታይ ትውልድ ይደርስ ዘንድ መቅረቡ ተገቢነት አለው። ተመልካቹ ግን ከራሱ የራቁ እርሱ የማይደርስበት አይነት ሰዎች ሆነው የሚመለከት ከሆነ ተሳስቷል።
ባለንበት ዘመን የተጽእኖ ፈጣሪነት ትርጉም እየተቀየረ ያለ ይመስላል። ሰዎች ብዙ ተከታይ ያላቸው ሆነው፤ በምን ጉዳይ ባለብዙ ተከታይ ሆኑ የሚለውን ስንዘረዝር ጥያቄ ውስጥ የምንገባ ሆነን ራሳችንን ልናገኝ እንችላለን። በታዋቂነትና በተጽእኖ ፈጣሪነት መካከል ልዩነት መፈለግም እንደሚገባ እንድናስብ በሚያደርግ ሁኔታ። ታዋቂ መሆንን ግብ አድርጎ መንቀሳቀስ ጥቂት የማይበሉ ሰዎች ቅኝት ሆኖም ይስተዋላል።
አዲስ ዓመት ኮቴው እየተሰማ ባለበት ስለ ቀጣዩ ዓመት አውጥተን በምናወርድበት ሰሞን “ያከበርከው፤ ያከበርሽውን” እንድንመለከት ወደድን። ዶክተር ማይልስ ሞንሮ “የህይወት ታላቁ አስከፊ ነገር ሞት ሳይሆን ዓላማ የለሽ ህይወት መሆን ነው” ይላሉ። ዓላማ ያለው ሕይወትን ለመኖር የምናከብረውን ማወቁ ተገቢነት አለው። ሰውን በማስቀደም እንዝለቅ፤
ሰው
በምድር ላይ እየሆነ ያለውን ሁሉንም እንቅስቃሴ ሰውን አውጥተን ለማየት እንሞክር። ትራንስፖርት ዘርፉን ከሰው ለይተን እንየው። ትምህርት ቤቶችን ከሰው ለይተን እንያቸው። ሆስፒታሎቻችንም እንዲሁ። ሆቴልም ቢሆን ወይንም ሚድያ። ግብርና ቢሆን ኢንዱስትሪ ወዘተ ከሰው ለይተን እንመልከተው። ምን ይታየን ይሆን? ምንም ሊታየን አይችልም። እጽዋትም ሆኑ አእዋፍትን፣ ጸሐይም ሆነች ከዋክብትን፣ የወቅት መፈራረቅም ሆነ እሳተ ጎሞራ ሁሉም ሰውን ማእከል አድርገው ሲታዩ ነው ትርጉማቸው የሚታየው። ሁሉም ስለ ሰው ልጆች የተሰናዱ ሆነው ይታያሉ። የሰው ልጅን በልዩነት መመልከት የግድ እንደሚለን በቅጽበት በጥሞና መመልከት ብቻ ተገቢ ነው።
ያከበርከው፤ ያከበርሽውን በምናስብበት ጊዜ ሰውን መመልከቱ አስፈላጊ ነው። በአምላክ ጉዳይ ላይ ሁሉም ሰው ተመሳሳይ ግንዛቤ ባይኖረውም በተፈጥሮ አይኑ ተመልክቶ የተቀራረበ አይነት መረዳትን ለመያዝ ሲሞክር ሰውን ያገኛል። ሰው ልዩ ፍጡር ነው። አንበሳን በቁጥጥሩ ስር አድርጉ ለጎብኚዎች የሚያስጎበኝ። እንዴት አድርጎ ወቅቶችን መጠቀም እንዳለበት በሺ ዓመታት ውስጥ ስሌቱን አግኝቶ መስመሩን ያሳመረ።
ለህይወት ያለን ግንዛቤ ጤናማ ይሁን አይሁን ለመመርመር ስናስብ ስለሰው ያለንን ግንዛቤ በመመርመር ብንጀምር ከብዙ ድካም ያተርፈናል። ሰው በቃ ሰው ነውና። በእድሜው፣ በጾታው፣ በትምህርት ደረጃው፣ በደረበው ማእረግ ወዘተ ሳይሆን ሰው እንዲሁ ሰው በመሆኑ ብቻ ልዩ ቦታን የተሰጠው ሆኗልና። ያከበርከው ምን እንደሆነ በምትጠይቅበት ጊዜ ለሰው ያለህን ቦታ መርምር። ያከበርሽውን በምትዘረዝሪበት ጊዜ ለሰው ያለሽን ቦታ መርምሪ። ሰው አስቀድመን እንዳልን ሰው ነው።
ሁሉም ነገራችን ምንጩ ፈጣሪ ቢሆንም፤ በራሱ መንገድ የምንገልጸው መሆኑን መረዳት ይገባል። መልካም ሰዎች ከአምላክ እናገኝ ይሆናል፤ መልካም ሰዎችን በዙሪያችን ማቆየት ግን የእኛ ኃላፊነት መሆኑን መረዳት አለብን።
ያከበርከው በህይወትህ ውስጥ ትርጉም እንደሚሰጥ መረዳቱ ካለህ ሰውን እንዴት እንደምትመለከት ዛሬ መርምር። የእይታ ለውጥ የአዲስ ዘመን መነሻ ቢሆን ምንኛ ባተረፍን። ሰዎችን በገንዘባቸው ብዛት ለክተሃቸው ይሆን? በትምህርት ደረጃቸው ወይንስ በምን? ዛሬ ቆም ብለን ማሰብ የሚገባን ማንኛውም ሰው ጨቅላ ይሁን አዛውንት፣ ባለ ማስተርስ ይሁን ፊደል ያልቆጠረ፣ ባለቢሊየን ይሁን እጁን ለምጽዋት የዘረጋ፣ ወዘተ ማንም ሰው ክቡር ነው። መከበር የሚገባው። በአስተሳሰብ ውቅራችን ውስጥ በተፈጥሮ አይናችን ከምናያቸው ፍጡራን ሁሉ ልዩ ቦታ ልንሰጠው የሚገባ።
ከራሳችን እልፍ ስንል ደግሞ ቤተሰባችንን እናገኛለን። ቤተሰብ ትልቅ ተቋም ነው። በአክብሮትና በጥንቃቄ መያዝ ያለበት ሰው የሚባለው የከበረ ፍጡር የሚገኝበት ትልቅ ተቋም። ከራስ አልፈን ቤተሰብን እናገኛለን። በመቀጠል የሥራ ባልደረቦች እያልን መጥቀስ እንችላለን።
ከሰዎች ሁሉ በፊት ስለሚቀድመው ሰው ማሰብ ደግሞ የግድ ይላል። ሰው ሁሉ በእርግጥ እኩል ነው። ሰው ሁሉ ክብሩ ነው። ሰው ሁሉ በሰውነቱ ቦታ ሊሰጠው የሚገባ ነው። ከሰዎች ሁሉ በፊት ግን ራንስ መመልከት መቻል፣ ቤተሰብን፣ የሥራ ባልደረቦችን ወዘተ እያለን መመልከቱ ተገቢነት ይኖረዋል። ከሁሉ የሚቀድመው ራስ መሆኑ መሰመር አለበት።
ያከበርከውን ለማየት ስንሞክር ሰውን አስቀደምን። ለሰው የምንሰጠው ውድ ስጦታን እናስከትል። በአክብሮት ልንይዘው የሚገባን አንድ ዋና ነገር። ጊዜ!
ጊዜ
የቤንጃሚን ፍራንክሊን “ጊዜ ገንዘብ ነው” የሚለውን አባባል ከሊኦ ቶልስቶይ “ሁለቱ ሃያል መሳሪያዎች ትእግስትና ጊዜ” ናቸው የሚለውን አቀናጅተን ስናይ ጊዜ ከገንዘብም በላይ የሆነ በህይወት ውስጥ ዘርፈ ብዙ ትርጉም እንዳለው እንረዳለን።
“የሀበሻ ቀጠሮ” የተሰኘው ያልተጻፈውን ህግ ለራሳችን አንብበን ስለ ጊዜ ያለንን መረዳት እንፈትሽ። ሰው በመሆናችን ውስጥ ካሉን ሃብቶች መካከል ቀዳሚው ጊዜ ነው። በጊዜ ውስጥ መሆን የምንሻውን ለመሆን ጉዞ እናደርጋለን። በጊዜ ውስጥ የሆነውን መርምረን በነገው ጊዜ ውስጥ ማስተካከያውን እንተልማለን። ትምህርት ለመቅሰም ይሁን ገንዘብ ለመስራት፤ ወደ ስልጣን ለመውጣትም ይሁን ከስልጣን ለመውረድ ጊዜ ትርጉሙ ብዙ ነው። ለማከናውን ባቀድነውና በተጨባጭ በተከናወነው መካከል ሰፊው ልዩነት ለጉዳዩ የተሰጠው ጊዜም ሆኖ ይታያል።
ያከበርከውን በምትመረምርበት ወቅት ጊዜን መመርመሩ አስፈላጊ ነው። ያከበርሽው ምን እንደሆነ በምትጠይቂበት ቅጽበት ስለጊዜ ላታስቢ በፍጹም አትችይም። “ጊዜ ዳኛ ነው”ይባላል፤ አዎን ዳኛ ነው። ጊዜ ዳኛ ብቻም አይደለም “ጊዜ አቃቢ ህግም” ነው። ጊዜ መምህርም ነው። ጊዜ ሐኪምም ነው። ጊዜ መጽሐፍም ነው። ጊዜ ፊልምም ነው። በአጭሩ ጊዜ ሁሉንም ነገር ነው።
የቁራሊዬው የተለመደ ንግግር የህጻናቱን ዜማ በምናባችን ለማሰብ እንሞክርና ላከበርነው ነገር የምንሰጠው ውድ ስጦታ ጊዜ መሆኑን እናስምርበት። እርግጥ ነው ለምንወደው ሰው ገንዘባችንን ልንሰጥ እንችላለን። ለምንወደው ሰው ቁሳቁስን ልናበረከት እንችል ይሆናል፤ ጊዜን መስጠት ግን ከስጦታዎቹ ሁሉ በፊት ቀድሞ የሚመጣ ነው።
መስጠትን የህይወቱ መርህ ላደረገ ሰው ከመቀበል ይልቅ መስጠትን ያስቀድማል። አልበርት ኤንስታይን “የሰው ልጅ ዋጋ መቀበል በቻለበት አቅም ሳይሆን በመስጠቱ ይለካል” ማለቱን ልብ እንላለን። መጽሐፍ ቅዱስም “ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብጽኡ ነው” በማለት የመስጠትን ዋጋ ይገልጸዋል። የሚሰጠው ነገር ምንድን ነው የሚለውን ማወቅም እንዲሁ ተገቢነት ይኖረዋል።
ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ በአዳሪ ት/ቤቶች ተገኝተው ይጎበኞቸው የነበሩ ተማሪዎች ነበሩ። እኒህ ተማሪዎች በንጉስ መጠየቃቸው በወቅቱ የሚፈጥርባቸውን ልዩ ስሜት ሲናገሩ እንዲሁም ሲጽፉ ስሜታቸው ልዩ እንደሆነ እናስተውላለን። እኒህ ሰው ካለባቸው ኃላፊነት ውስጥ ተማሪዎችን መጎብኘትን ቦታ የሰጡት ተማሪዎች መጎብኘት የሚገባቸው መሆናቸውን እንደ ሰው በመቆጠራቸው አድርገን እንረዳው። ሰውን በቀዳሚነት ማንሳታችን ልብ እያልን። ለሰው የሰጡት ጊዜ ሲሆን ደግሞ ውጤቱ በተማሪዎች እርጅና ዘመን እንኳን ሳይቀር የሚታወስ ሆነ። ከሰዎች ሁሉ አስቀድመን ራሳችንን ተመልክተን ለራሳችን የምንሰጠው ቀዳሚው ነገር ምንድን ነው ብንል ምላሹ ጊዜ የሚል ነው። አዎን ለራስ የሚሰጥ ጊዜ። ከራስ ቀጥለን ቤተሰብ አልን አሁንም ለቤተሰብ የምንሰጠው ቀዳሚ ነገር ጊዜ ነው። ጊዜ!
ለጊዜ ትኩረት መስጠት ሲባል ለምን ጉዳይ ምን አይነት ሰዓት የትኛውን ሰዓት ብሎ መደቦ መጠቀምን ይጠይቃል። በእውቀት ደረጃ ብዙ ሰዎች ጊዜን በአግባቡ መጠቀም እንደሚገባ ቢያስቡም እንዴት የሚለው ግን ጥያቄ ይሆናል። ዓላማ ተኩር ህይወትን ስንኖር ጊዜያችንን የሚፈልጉ ጉዳዮችን ዘርዝረን ለየትኛው ጉዳይ ምንያህል ሰዓት እንዴት ባለ ሁኔታ ውስጥ የሚለውን ምላሽ መስጠትን ይጠይቃል። በማህበራዊ ሚዲያ ዘመን ብዙ ነገሮች ወደ እኛ ይመጣሉ። ሁሉንም ማስተናገድ የምንችልበት ጊዜ ሊኖረን አይችል። ስለሆነም ጊዜን መጠበቅን ስናስብ ይህ ወቅት ግድ የሚል መሆኑንን መረዳት ይገባል።
ያከበርከው እርሱ ዋጋው ውድ ሆኖ በህይወትህ ይኖራልና ጊዜህን አክብር። ክቡር ለሆነው የሰው ልጆች ልትሰጠው የምትችለው ትልቁም ነገር ጊዜ መሆኑን ተረዳ። ከሰው ውስጥ ለራስ ቅድሚያ መስጠቱን ተገቢነት አንስተናል። ጊዜ ለራስ መስጠት ሲታሰብ ጎልቶ የሚታየው ጊዜን የሚፈልግ የራስ ጉዳይን ማንሳቱ አክብረን እንድንይዝ ያደርገናል እርሱ የራስ እምቅ አቅም/ተሰጥዖ ነው።
የራስ እምቅ-አቅም/ተሰጥዖ
“የህይወት ታላቁ አስከፊ ነገር ሞት ሳይሆን ዓላማ የለሽ ህይወት መሆን ነው” የሚለውን በመግቢያችን ላይ ያነሳነውን የዶክተር ማይልስ ሞንሮን ሃሳብ እንድገመው። ሰው በመሆናችን ውስጥ ብቻ አቅም አለ። አንዳንዱ ጥሩ ተናጋሪ የመሆን አቅም አለው፤ አንዳንዱ ደራሲ፣ ሌላው መሪ፣ ሌላው ነጋዴ፣ ሌላው አዳዲስ ግኝት አፍላቂ ወዘተ።
የራስ እምቅ አቅም ላይ አተኩሮ መስራት የህይወት ዘመንን በፍሬያማነት ለመጨረስ የሚረዳ ነው። ጊዜ ደግሞ ትልቁ ግብዓት። እምቅ አቅምን ወይንም በልዩ ሁኔታ የራሳችን የሆነውን አቅም ማወቅ ብቻ ወደ ውጤት ሊያደርስ አይችልም። አንድ ቀን ተዓምራታዊ በሆነ መንገድም በመክሊታችን ልንገለጥ አንችልም። ጊዜን መስጠት ይጠይቃል። መክሊታችንን ለመፈለግ ጊዜ መስጠት፤ ካወቅን በኋላ በእርሱ ላይ አተኩሮ ለመስራት ጊዜ መስጠት ይገባል።
ራስን ማክበር ራስን በመፈለግ ውስጥ ትርጉም አለው። እምቅ አቅም የሌለው ሰው የለም። ተሰጥዖ ይዞ የማይወለድ ሰው የለም። ሰው ሆኖ ምንም የሌለው የሚባል ሰው የለም። በትምህርት አሰጣጣችን ውስጥ ተማሪዎች ተሰጥዖቸውን ፈልገው እንዲያገኙ፤ ያገኙትንም በተግባር በሥራ ላይ እንዲያውሉት ማድረግ ባለመቻል በብዙ እንደከሰርን አስባለሁ። ኢትዮጵያውያን ከሀገራቸው ውጭ ሲሄዱ ተገርመው ከሚናገሩበት ነገር መካከል ሀገር ቤት ሥራ ገና አልተጀመረም የሚለው ነው። ብዙ የሚሰሩ ሥራዎች ሀገር ቤት ውስጥ መኖሩ የሚያሳየን በግለሰቦች ውስጥ ያለ ወደ ፍሬ ያልተለቀቀ እምቅአቅም መኖሩን ነው።
የልጆች አስተዳደግ እንደሁም የትምህርት አሰጣጣችን እያንዳንዱ ሰው በመክሊቱ ላይ እንዲያተኩር ማድረግ ላይ ቢሰራ ፍሬያማ ያደርጋል። ፍሬያማነቱ ከግለሰብ ወደ ቤተሰብ፤ ከቤተሰብ ወደ አካባቢና ሀገር እልፍ ሲልም ለሌሎች ሀገራት ዜጎችም ሊሆን ይችላል። ዓለም ሁሉ የእኔ ብሎ በጋራ የሚጠቀምባቸው አያሌ ግኝቶች መነሻቸው አንድ ግለሰብ ነው። ለራሱ ቦታን የሰጠ፤ በውስጡ ያለውን ጥያቄ ለመመለስ ጊዜን የሰጠ፤ ከሰጠውም ጊዜ ለሌሎች የሚጠቅምን ነገር ማበርከት የቻለ።
የራስን እምቅአቅም ፈልጎ መግለጥን ሲታስብ ሁለት ነጥቦች ሁሌም ግምት ውስጥ መግባት አለባቸው። የመጀመሪያው እምቅ አቅሙን መፈለግና ማውጣት ዋናው ኃላፊነት የግለሰቡ መሆኑን ሁለተኛው የግለሰቡ የምድር ቆይታው ስኬት በተሰጥኦ ወይንም እምቅ አቅሙ ላይ የተመሰረተ ሥራን ሲሰራ እንደሆነ መረዳት።
ልጆች በባህሪያቸው ያዩትን ነገር ሁሉ ለመሆን የመጣር ፍላጎት አላቸው። ብዙ ነገሮችን ነካክቶ የራስ ወደሆነው ለማዘንበል የሚረዳ ሊሆን ይችላል። ይህ አይነቱ አካሄድ ግን በእድሜ ልክ ሁሉ ከቀጠለ የጊዜ ብክነትን ሊያስከትል ይችላል። እድሜን በአግባቡ ያለመጠቀም ብክነት። ሰዎች የሚያደርጉትን እያየን አንድ ሰሞን ያየነውን ለመሆን ጥረት የምናደርግ ከሆነ እርሱ አደጋ አለው። የኦሎምፒክ ሰሞን የአትሌቶቻችንን ድል ተከትሎ በየሰፈሩ ሩጫ የሚጀምር መኖሩ እሙን ነው። የዓለም ዋንጭን መነሻ አድርጎ ወደ ኳስ የሚገባውም እንደዚያው። መጽሐፍ ምርቃትን ተመልክቶ መጽሐፍ መጻፍን የሚጀምርም እንዲሁ እያልን ብዙ ልንጠቅስ እንችላለን። በሌሎች ሰዎች መነሻነት በውስጣችን ያለው ተሰጥኦ ሊነሳሳ እንደሚችል ይታመናል። ነገርግን ሁልጊዜ እንደ አዲስ ያየነውን ሁሉ እየሞከርን ስንሄድ ጤናማነት አይደለም። መፍትሄው ለራስ በቂ ጊዜ በመስጠት ትኩረት ልናደርግ የሚገባውን የህይወት መክሊታችንን መለየት ነው። ካገኘነው አክብረን መያዝ፤ በመክሊቱም ማትረፍ።
በመክሊት ለማትረፍ፣ እምቅ አቅማችንን በሚገባ ለማውጣት ወዘተ የሚያስፈልገን መንፈስ አለ፤ እርሱም የኃላፊነት መንፈስ ነው።
ኃላፊነት
ለትራንስፖርት የምንገለገልበት ታክሲ ውስጥ ጀምሮ እስከ ሀገር የበላዩ ሰው ድረስ ኃላፊነት የሚለው ቃል ቅርባቸው ሊሆን የተገባ ነው። ባለታክሲው የተሳፋሪዎችን ደህንነትና ምቾት ጠብቆ ሊያደርሳቸው የተገባው መዳረሻ ጋር ለማድረስ እጁን መሪው ላይ አድርጓል። የሀገር መሪው እንዲሁ። የኃላፊነት ስሜት ማንም ሰው ሊኖረውና አክብሮ ሊይዘው የተገባ ነው። በጥቂት የታመነ ለብዙ ይሾም ዘንድ ዛሬ በእጁ ባለው ነገር ላይ ያሳየው ታማኝነት ሊተረጎም ይገባል። በምድራችን ኢትዮጵያ ከቤታችን ጀምሮ እስከ አደባባይ ብዙ የሚባል የተስፋ ዝርዝር ብዙ ነው። ምንያህሉ ወደ ሥራ ወደ ውጤት ተቀየረ ብለን ስንጠይቅ የምናገኘው ምላሽ ውስጥ ኃላፊነት መንፈስ ሰፊውን ስፍራ ይዞ እናገኛለን።
የኃላፊነት ስሜት ለማንኛውም ሰው አስፈላጊ ነው። ዓለማችን ኃላፊነት በማይሰማች ሰዎች ተመርታ የደረሰባትን መከራ በታሪክ ገጾቿ መዝግባ ይዛለች። ዛሬም ኃላፊነትን ትርጉም ሳይሰጡ፤ ለኃላፊነት የሚገባውን ትኩረት ነፍገው የምናያቸው ቤቱ ይቁጠራቸው።
ዘመን መለወጫ ሲታሰብ ሁሉም በዓሉን አክባሪ በኃላፊነት ወጥቶ የሚገባ መሆን እንዳለበት መታሰብ አለበት። በዓልን ለማክበር ከመጠን በላይ ጠጥቶ እያሽከረከረ የሰዎችን ህይወት የሚነጥቀውን ሰው እንዴት ስለኃላፊነት የበቃ አድርገን ልናቀርበው እንችላለን? በምንም አይነት ሁኔታ ውስጥ ቢሆን የኃላፊነት ስሜት የሚሰማቸው መሪዎች ሆነ ዜጎች በሌሉበት ሀገር ውስጥ ልማት ከጥፋት ሊመዝን አይችልም።
ቁራሊዮ “ያከበርከው፤ ያከበርሽው” የሚለው የተለመደ አባባሉ ውስጥ በኃላፊነት ነገሮችን ማድረግን እንማርበታልን።
መጪው ዓመት ያከበርነው የሚቆጣጠረን ዓመት መሆኑን ለመናገር ነብይ መሆንን አይጠይቅም። መቼም የሚሰራ እውነት ስለሆነ። ጥያቄው ዛሬ ያከበርነው ምንድን ነው? የሚለው ነው። ጊዜያችንን የምንሰጠው፤ በኃላፊነት ስሜት የምንተገብረው። ሠናይ ጊዜ።
በአገልጋይ ዮናታን አክሊሉ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 22/2013