“ሀኪም አድነው” ወይም “ማይ ክርስቶስ” በሚል ቅፅል ስሙ ይታወቃል:: ይህ ቅጽል ስም የወጣለት ደግሞ እነዚህን ቃለት በሚሠራቸው ሥራዎች ውስጥ በመጠቀሙና የስሞቹ ገፀ ባህሪ ሆኖ በመጫወቱ ነው:: የስሙ አውጪ ደግሞ አድማጭ ተመልካቹ ነው:: ኮሜዲያን ምትኩ ፈንቴ፤ የዛሬው የዝነኞች እረፍት ውሎ አምድ እንግዳችን ነው::
ውልደትና እድገቱ ጎጃም ቡሬ ገሊላዊት በዓታ በምትባል የገጠረ መንደር ውስጥ ነው:: በተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወርም እስከ 12ኛ ክፍል ትምህርቱን የተከታተለ ሲሆን፤ በቴአትር ትምህርት ዲፕሎማና የተለያዩ የምስክር ወረቀቶችን ማግኘት ችሏል:: እንደማንኛውም ልጅ ትምህርት ቤት ገብቶ በጊዜ ሂደት ደግሞ ፍላጎቱ ምን ላይ እንደሚያተኩር ተረድቶ ራሱን ኪነ ጥበቡ ዓለም ውስጥ ማግኘቱን ይናገራል:: ከዚያም ወደ ቴአትር ክበባትና ወደ ሚዲያ በመምጣት በሬዲዮና በቴሊቪዥን ሥራዎቹን ማቅረብ ችሏል::
መጻፍ፣ አስቂኝ ነገሮችን ማሰብ፣ መድረክ ላይ ማቅረብ፣ ፊልሞችን መድረስ፣ ቴአትርና ኪነ ጥበብ ውስጥ ያሉ ሥራዎችን ከመጻፍ ጀምሮ እስከ መስራት የደረሰ ስመ ጥር ኮሚዲያን ነው ምትኩ ፈንቴ:: ከኮሜዲ ሥራዎች እንደ ሰው በልኬና ሀኪም አድነው ጎልተው ይውጡና ብዙኃኑን ያዝናኑ እንጂ፤ በርካታ የኮሜዲ ሥራዎችን በተለያዩ መድረኮች ላይ አቅርቧል:: አጫጭር ፊልሞች ላይም በብዛት ተሳትፏል::
በኪነ ጥበብ ስራዎች ላይ በተለያየ መልኩ ተሳትፎ እያደረገ ያለው ምትኩ ከዚህ በኋላም የራሱን ፊልሞች በሲኒማ ደረጃ ሰርቶ ለማቅረብ መንገድ ላይ መሆኑንም ነው የሚናገረው:: ዩቲዩብ ቻናሎችና ሚዲያዎችም ከዚህ ቀደም ከነበረው ተሳትፎው የበለጠ አሳድጎ በአዳዲስ ሥራዎች ብቅ ለማለት የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ ነኝ ብሏል::
ምትኩ፤ የኮሜዲ ሥራ ከባድ ነገር እንደሆነና በየሰዓቱና በየደቂቃው ማሰብን፣ ማንበብን ጥሩ ተመልካች መሆንን፣ ነገሮችን ማቅለልን የሚጠይቅ ሥራ እንደሆነ ይገልጻል:: እርሱም ራሱን በኮሜዲ ሥራ ውስጥ ካገኘበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ድረስ ከእነዚህ ተግባራት እንዳልራቀ ያብራራል::
ኮሜዲያን ምትኩ ምንም እንኳን ብዙዎች በኮሜዲ ሥራዎቹ ቢያውቁትም በተለያየ ገፃባህሪያት በመላበስ ተጫውቷል:: ከአስቂኝ በተለየ አሳዛኝ ድራማዎችና ፊልሞች ላይም ተሳትፎ አድርጓል:: ነገር ግን ቀድሞ ተመልካቹ የኮሜዲ ስራዎቹን በመውደዱ እሱም ወደ ማዝናናቱ ላይ አዘንብሏል::
አንዳንድ ጊዜ ብዙ ሰዎች ኢትዮጵያውያን አይስቁም ፤ኮሜዲያንነቱ እንዴት አዋጣችሁ ብለው ጥያቄ እንደሚያቀርቡለት ይናገራል:: ምትኩ በበኩሉ ሰው ካልተዝናና እንደታመመ አድርጎ ነው የሚቆጥረው:: እናም በዚህ መንገድ ሰውን ለማሳቅ ብዙ እንደማይቸገር ይናገራል:: መሳቅ ኮሜዲያኑን በማሰብ ብቻ ሳይሆን ከተነገረው ጉዳይ ጋር ነው ይላል:: ጥልቁን የአዕምሮ ክፍል እንደመጠቀምም ጭምር ስለሆነ ሰዎች መዝናናት እንዳለባቸውም ይመክራል::
እንደ እርሱ አባባል፤ የኢትዮጵያ ህዝብ ዝም ብሎ ፌዝ ሳይሆን በሚነገረው ነገር ውስጥ ያለውን ቁምነገር ስለሚመለከት ነው የሚዝናናው:: ከመጣንበት ታሪካዊ የኮሜዲ ሥራዎች አንጻርም ይህንን መመልከት ይቻላል:: ለምሳሌ የአለቃ ገብረሀና ቀልዶችን ለውጥ ሊያመጣ ከሚችል አንድ ነገር ጋር የሚያያዙ በመሆናቸው ነው ሰዎች የሚደሰቱባቸው:: ይህ ምን ያህል ሰው ኮሜዲ ውስጥ ፍሬ ነገርን እንደሚፈልግ ማሳያ ነው:: ከዚህም ባሻገር የኮሜዲ ሥራ ውስጥ በድምጽና ተግባራዊ እንቅስቃሴም ሀሳቡ ለተመልካች እንዲመቸው ማድረግ ይቻላል::
ኮሜዲያን ሥራ ይዘው ሲቀርቡ ሁለት አይነት ተመልካቾች እንዳሉ ማወቅ አለባቸው:: እነዚህም ሥራውን የሚቀበሉና የማይቀበሉ ናቸው:: በምትኩ እይታ፤ ሁለቱም ትክክል ናቸው:: “የማይፈልግህ ተመልካች ለማበርታት ያግዛል:: ከሚፈልግህ ደግሞ የሞራል ስንቅ ይገኛል” ይላል::
የእረፍት ጊዜው
ኮሜዲያኑ ማንበብ በእረፍት ጊዜ ቆይታው የሚደጋግመው አንዱ ተግባር እንደሆነ ይናገራል:: በዚህም ብዙ ሀሳቦችን እንደሚያገኝና አዕምሮውንም እንደሚያበለጽግ ይጠቅሳል:: በግርግር ውስጥ ውዬ ማደር አልችልም የሚለው ኮሜዲያን ምትኩ፤ ለብቻው ሆኖ ማሰብንም በእረፍቱ ጊዜ እንደሚያከናውን ገልጿል:: ተመስጦ ደግሞ የኮሜዲያን ምትኩ ሌላኛው ልምድ ነው:: የተለያዩ ጉዳዮች በጥልቀት መመርመርና ስለ ጉዳዩ ማሰብ ያስደስተዋል:: ታዲያ የሚያስበው መርጦ ሳይሆን ማንኛውንም አይነት ሀሳብ ነው:: “አዕምሮው በማሰብ ጡንቻ እንዲያወጣ” ማድረግ ይቻላል ይላል:: ለዚህ ነው ማሰብ ላይ የሚያተኩረው:: ለእርሱ ማሰብ የማንበብ አሊያም የመመልከት ያክል ጥቅም ይሰጠዋል:: በቀን ውስጥ በሚያገኘው እረፍቱ የማሰብና ማሰላሰል ነገር አይለየውም::
ከዚህ ባሻገር በጫካ፣ ሜዳና ተራራዎች በመገኘት ተፈጥሮን የማድነቅ ዝንባሌም እንዳለው ይገልጻል:: በተፈጥሮ ሱስ ተይዣለሁ፤ ተፈጥሮአዊ ቦታዎች ላይ መገኘትም አዘወትራለሁ ይላል:: በእረፍት ጊዜው ከአረንጓዴ መስክና ተፈጥሮአዊ መስህብ ያላቸው ስፍራዎች ላይ ማዘውተር ይወዳል:: በተለይ ጫካ ውስጥ ውሎ ቢያድር አውሬ የሚያስደነግጠውና የሚያስፈራው እንዳልሆነ በልበ ሙሉነት ይናገራል::
ከመሰል ጓደኞቹ ጋር በመገናኘት ሀሳብ መለዋወጥም እንዲሁ የእረፍቱ ጊዜ አንዱ ተግባር ነው:: በዚህ ጊዜ ቀልዶችን ይነጋገራሉ፤ ቀልዶችን ያዳብራሉ፤ አዲስ ሀሳብ ያፈልቃሉ:: ቀልዶችን ለኮሜዲያን ነግሮ ከሳቁ ሀሳቡ ጥሩ መሆኑን ይገነዘባል:: በእንዲህ አይነት ሁኔታ ሲገናኙ ሀሳብ ሲለዋወጡና ሲወያዩ እንደሚውሉ ኮሜዲያን ምትኩ ይናገራል:: በመሆኑም ከጓደኞቹ ጋር የእረፍት ጊዜውን ማሳለፉ እውቀትን፣ ሀሳብንና ሌሎች ድጋፎችን እንዲያገኝ አስችሎታል:: በህይወቱ ውስጥ የኒቨርሲቲዎቼ የሚላቸውም ጓደኞቹን ነው:: ጓደኛ እውቅት፤ ቤተሰብ ሞራል ገንቢ ናቸው የሚል እምነት እንዲኖረው ያደረገው ይህ ሁኔታ እንደሆነም አመላክቷል::
ገጠመኝ
“ሰዎች ለቅሶ ቤት እያለቀሱ ሲያዩኝ ለቅሶውን ያቋርጡና በትኩረት ይመለከቱኛል:: በአለቃቀሳቸውም እየተጠነቀቁ ይመጣሉ:: እንዲህ የሚያደርጉት በአለቃቀሳቸው የምቀልድ ስለሚመስላቸው ነው:: አንዳንዶችም የለቅሶ ቤት ሁኔታውን ሳይሆን በፊት የሰራሁትን የኮሜዲ ስራ አስታውሰው ሊስቁ ይችላሉ:: ለቅሶ ቤት ኮሜዲያኖች ሲገኙ ሊቀልዱ ነው የመጡት ብለው ነው ሰዎች የሚገምቱት:: ሌላው አገር ኮሜዲያኑ በአንድ ሰው ከቀለደ ሌላኛው ሰው ለምን በኔም አልቀለደም ይላል:: እዚህ ግን እጅህን ከጠቆምክ ራሱ ብዙ ነገር ሊገጥሙ ይችላሉ” ይላል ኮሜዲያን ምትኩ::
መልዕክት
ክፉ ሀሳብ እንጂ ክፉ እናት የለንም የሚለው ኮሜዲያን ምትኩ፤ “እናታችን አገራችን ናት፤ አገራችን ደግሞ ክፉ ሀሳብ የላትም:: እኩያን የሆኑትና ክፉ ሀሳቦችን የሚያመነጩት ሰዎች ናቸው” በማለት፤ እነዚህ አካላት አንድ አገር እንጂ ሌላ አገር እንደሌለን በማሰብ ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ ያሳስባል::
ኮሜዲያኑ፤ በተለይ አሸባሪው ህወሓት ተኩስ የከፈተባቸው አንዳንድ አካባቢ ያሉ ህጻናት ጣራ ላይ ዝናብ ቆርቆሮ ሲመታ ጥይት የጮኸ እየመሰላቸው ሲደነግጡ አስተውያለሁ በማለት፤ በተለይ በግፈኞች ምክንያት የደፈረሰው ሠላም እንዲሰፍንና ሰዎች ከጭንቀት የሚላቀቁበት ጊዜ እንዲመጣም ተመኝቷል::
አዲሱ ገረመው
አዲስ ዘመን ነሃሴ 16/2013