በሰፈር ውስጥ ያሉ ሆያ ሆዬ የሚሉ ታዳጊዎች ምክክር እያደረጉ ነው። ምክክራቸው ከሆያሆዬ ስለሚያገኙት ገንዘብ ነው። ገንዘቡ ምን ያህል ሊሆን እንደሚችል፤ እንዲሁም እንዴት ሊከፋፈሉት እንደሚገባ ሞቅ ባለ ምክክር እየመከሩ ነው። ምክክሩን ተከትሎ ገንዘብ ያዥ መረጡ። በመቀጠል የጭፈራው ግጥምና ቅደም ተከተሉ ምን መምሰል እንዳለበትም ተወያዩ።
በሞቀ ውይይታቸው ውስጥ ሳሉ በአካባቢው የተወደዱና የተከበሩ ሽማግሌ እያለፉ ነው። እርሳቸውም “ልጆች ምን እያደረጋችሁ?” ሲሉ ጠየቋቸው። ታዳጊዎችም በፍጥነት “አባባ ለሆያሆዬ እየተዘጋጀን ነው።” ሲሉ ምላሽ ሰጡ። ከታዳጊዎቹ መካከል አንዱ የእርሳቸው የልጅ ልጅ ነው። የልጅ ልጃቸውም ፈንጠር ብሎ መጥቶ አጠገባቸው ሲቆም “አዲሴ እያሉ ጸጉሩን ደባበሱት። ከልጆቹም መካከል አንዱ “አባባ የአዲስን ስም ለምን አዲሴ እያሉ ይጠሩታል” ብሎ ጠየቃቸው። እርሳቸውም “ልጆቼ የአዲሴ ስም ታሪኩ ረጅም ነው። የአዲሴን ስም አወጣጥ ብታውቁ ደግሞ ሆያሆዬን እንዴት ማየት እንዳለባችሁም ትረዳላችሁ።” ታዳጊዎችም የጓደኛቸውን የአዲስን ስም ትርጉም ለማወቅ ጓጉ። “እሺ አበባ ንገሩን“ አሉ በአንድ ድምጽ።
አባባም ማብራሪያውን ጀመሩ “አዲስ የተወለደው የእንቁጣጣሽ ዋዜማ ላይ ነበር። ከጥቂት ቀናት በኋላም አስራ ሁለት አመቱን ይደፍናል። አዲስ የተባለውም አዲስ አመት እየመጣ በመሆኑ ነው። በወቅቱ የእናቱ ጤንነት ችግር ውስጥ ስለነበረ ይህ ልጅ በሰላም ይወለድ ይሆን የሚለው ስጋት የሁላችንም ነበር። እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን በሰላምም ተወለደ። ለመስከረም ዋዜማ በመወለዱ እንዲሁም እናቱ አዲስ የጤናን ህይወት መለማመድ እንደምትችል በማመኗ ነበር ልጁን አዲስ ያለችው። ሁላችንም በጣም ደስ አለን። እኔም አዲሴ እያልኩ እጠራዋለሁ። እውነት ለመናገር እናቱ ይህን በምትልበት ጊዜ የነበረችበት ሁኔታ እጅግ ከባድ ነበር። ምናልባትም የእርሷንም ህይወት ሊወስድ ይችልም ነበር። ነገር ግን በውስጧ ያለው የአዲስነት መንፈስ ነበር። ነገሮች መልካም ይሆናሉ፤ አዲስም አየር በቤተሰባችን ላይ ይነፍሳል ብላም አሰበች። ሁላችንም ለአዲስ አመት መዘጋጀት ቀርቶ ሀዘንን በምናስብበት ወቅት ብርቱዋ እናቱ ግን አዲስ ስለሚሆን የህይወት አቅጣጫ አስባ ተስፋዋን ታለመልም ነበር። በህክምና እርዳታ በቤተሰብ ጎረቤትም ጸሎት ጤናዋ እየተሻሻለ መጣ።
እናንተም ሆያሆዬ ስትሉ የሆያሆዬን ትርጉም ካሰባችሁት ስለአዲስ ተስፋ እየዘመራችሁ ነው። አዲስ አመት ከመሆኑ በፊት ጅራፍ የሚጮኸው፤ እንዲሁም የሆያሆዬ ጭፈራ ውስጥ ያለው መልእክት አዲስ ነገር እየመጣ መሆኑን የሚያመላክት ነው፤ የመሻገር ብስራት።
ልጆቼ እውነት ነው ቀናቶች በራሳቸው የሚሰሩት ነገር ላይኖር ይችላል። አዲስ ነገርን ለማየት ግን በሰው ውስጥ ሊኖር የሚገባው የተስፋ ጉልበት አለ። ከሚታየው ጨለማ አሻግሮ መታየት ያለበት የተስፋ ብርሃን። እናንተም ሆያሆዬን ስታስቡ በጭፈራ ከምታገኙት ገንዘብ ባሻገር አዲስ ተስፋን እያያችሁ መሆኑን እርግጠኛ ሁኑ። አዲስ አመት በትምህርቴ የተሻለ ውጤት የማስመዘግብበት፤ በአካሌ የምገነባበት፤ በመንፈሳዊ አቅም የምጎለበትበት፤ ከሰዎች ጋር በሚኖር መስተጋብር ፍሬያማ የምሆንበት ወዘተ ብለን ከውስጣችን ብንቀበለው አቅም ይሆነናል። እኛም ልጅ እያለን በሆያሆዬ ስለምናገኛት ገንዘብ ብዙ ተጨንቀን አውጥተን አውርደን እንዘጋጅ ነበር። ጥሩ ነው በብርቱ መዘጋጀታችሁ ዋናው ነገር ግን አዲስ መንፈስን ይዞ አዲስ አመትን መቀበል ነው።
አዛውንቱ መካሪ ከታዳጊዎቹ ተለይተው የተወሰነ እንደሄዱ ሁለት የአካባቢው ነዋሪዎች ቆመው ሲያወጉ ደረሱ።
አዲስ ፖሊስና አዲስ ፖሊሲ
ቆመው የሚያወጉት ሁለቱ የአካባቢው ሰዎች አንደኛው ፖሊስ ሲሆን ሁለተኛው የአካባቢው የህዝብ እንደራሴ ነው። ከሁለቱም ጋር መልካም ጉርብትና አላቸው። ፊታቸውን ወደ ሁለቱ ጎልማሶች አዙረው “ፖሊስና ፖሊሲ አውጪ” አሉ። ሁለቱም ጎልማሶች በፈገግታና በአክብሮት ተቀበሏቸው።
ጸጥታ ለማስጠበቅ ሃላፊነት የተቀበለው አካል ፖሊስ ነው። ፖሊስ ጸጥታ ለማስጠበቅ በሚረዳው ደረጃም የታጠቀ ነው። ከአቅሙ በላይ ሲሆን ሌላ ሃይልን ወደ ጉዳዩ ይጋብዛል። አጠቃላይ ሀገርን የመምራት ሃላፊነት ያለበት የፖለቲካ አመራር ደግም ፖሊሲዎችን ያወጣል፤ ተግባራዊም ያደርጋሉ። በሀገር የሚተገበሩ ፖሊሲዎች የዜጎችን ህይወት በመቀየርም ሆነ ባለመቀየር ረገድ ድርሻቸው ሰፊ ነው። አዲስ የዜጎች ህይወት፤ ከአዳዲስ እይታዎች ይቀዳሉና።
ሁለቱ ጎልማሶች ከአዛውንቱ ጋር እየተጨዋወቱ ቆይተው ሽማግሌውም ሊሰናበቷቸው እየተዘጋጁ “ልጆቼ በተሰማራችሁበት ዘርፍ ሁሉ ውጤታማ እንድትሆኑ፤ መጪው አመት የፍሬ እንዲሆንላችሁ እመኛለሁ። ይህ በእዚህ እንዳለ ሁላችንም ለግላችን ፖሊሲ አውጪውም ሆነ ጠባቂው ፖሊስ ማን መሆን እንዳለበት ግን መጠየቅ አለብን። ፍሬያማ ዘመንን ሁሉም ሰው ይፈልጋል። የተሻለ ኑሮን ሁሉም ያልማል። እያንዳንዱ ሰው ግን ለራሱ ፖሊሲ አውጪ መሆን አለበት።
አዲስ አመት በመጣ ቁጥር ደጋግመን አዲስ፣ አዲስ፣ አዲስ … ብንል ለውጥ እንደማይመጣ ያለፍናቸው የበረከቱ አመታት ያስተምሩናል። አዲስ እንዲሆን ዘምረን ለምን አዲስ እንዳልመጣ ትምህርት መውሰድ አለብን። ሁሉም መፍትሄው ያለው ራሳችንን መመልከቱ ላይ ነው። ራሳችንን ስንመለከት ለውጥ የሚያስፈልገን አቅጣጫ እንለያለን። ራሳችንን ስንመለከት ለውጥ ለሚያስፈልገው አቅጣጫ ላይ ሊደረግ የሚገባውን የአካሄድ ለውጥን እንቀይሳለን። ለራስ ፖሊሲን መደንገግ ይህ ነው። ጤናማ ፖሊሲ ኖሮት የሚተገብር ግለሰብ ለማህበረሰብ ያለው አስተዋጾ ከራሱ አልፎ አዎንታዊ ነው። የራሱ ጠባቂም ፖሊስ ነው። በመጠጥ ተጠላልፎ ወድቆ የሚገኝ፤ ሰላም በመንሳቱ የሚታወስ አይሆንም። ብዙ በማውራት የሌሎችን ሃሳብ የሚያፍንም አይደለም። ቤተሰቡ የእርሱን መገኘት አንዳች ሸክም እንደሆነ ነገር የሚቆጥሩትም አይደለም። ይህ ሰው አዲስ፣ አዲስ ብሎ የሚዘምር ብቻ ሳይሆን ለአዲስ ጉዞ መርሆችን የሰነቀ፤ አካሄዱን የተለመ፤ እርምጃውን እየመረመረ የሚራመድም ሰው ነው።
አዲስ አመት በመልካም ምኞት ብዛት አንዳች ወደፊት ማስፈንጠሪያ መሆን ቢቻል የእስከአሁኑ ብዙ ለመሆን በረዳን ነበር። ወደራሳችን እንመልከት። ልንቀይረው የሚገባውን ነገር አንድ ሁለት ብለን ዘርዝረን እናስቀምጥ። ህይወታችን የሚመራበት እውነትንና መርህን በግልጽ አውቀን እንተግብር። አተገባበሩም ፍሬ የሚያፈራ እንዲሆን እናድርግ።”
ሽማግሌው ንግግራቸውን እያደረጉ እያለ የፖሊሱ የመጀመሪያው ልጅ አባቱን ቡና ሊጠራ መጥቶ ተገናኙ።
ዛሬ ምን ተማርኩ
ቡና ሊጠራ የመጣውን የፖሊሱን ልጅ አባባም ተመልክተው“አቡሽዬ ሆያ ሆዬ የለም እንዴ?” ብለው ጠየቁት። ልጁም አይኑን ወደ አባቱ አድርጎ ራሱን እያፍተለተለ አንገቱን ደፋ። አባትዬውም “ያልጨረሰው ጥናት ስላለው ነው አባባ“ ሲል መለሰላቸው።
አባባም “አይ የአንተ ነገር፤ በቃ ፖሊስነቱን ሁሉም ቦታ ላይ ታደርገዋለህ። ምን ሆነሃል፤ ኋደኞቹ ወጥተው ሆያ ሆዬ እያሉ ልጅህ ቀልቡን ሰብስቦ የሚያጠና ይመስልሃል?” ሲሉ ጠየቁ። ፖሊሱም ለራሱ እኮ ነው አባባ፤ ዛሬ ላይ ቁጭ ብሎ አጥንቶ እውቀት ካልያዘ ለነገ ይቸገራል ብዬ ነው።” ሲል መለሰ። አባባም “እርሱ ባልከፋ ልጅህ በትምህርቱ እንዲበረታ ማድረግህ ባልከፋ ግን ትምህርት ማለት ‘ዛሬ ምን ተማርኩ’ ብሎ በመጠየቅ መልስ ሊገኝለት የሚገባ መሆኑን መዘንጋት የለበትም። ዛሬ ምን ተማርኩ መልስ የሚያገኘው ልጁ ተረጋግቶ ሲማር፤ ደስ ብሎት ሲያጠና ነው። ልጆች እንዲማሩ፤ እንዲያጠኑ አድርገናቸው ዛሬ ምን ተማርኩን መመለስ ካልቻሉ ፈተና ለማለፍ ብቻ ይሆናል የሚማሩትም ሆነ የሚያጠኑት። እውቀት እንዲዋሃደን ደስ ብሎን የምንማር፤ በግብና በዓላማ የምንማር መሆን አለብን። የጎረቤት ልጅ የደረጃ ተማሪ ስለሆነ ልጃችንን የደረጃ ተማሪ ካልሆንክ ብሎ ማስጨነቅ የለብንም። ልጆች መጫወት ሲገባቸው እየተጫወቱ፤ ማጥናት ሲገባቸው እንዲያጠኑ በማድረግ በሚዛን ጊዜያቸውን እንዲጠቀሙ ማድረግ አለብን።”
የአባባን ንግግር በጥሞና የሚሰማው ልጅ ዛሬ ምን ተማርኩ እያለ አዲሱን አመት ለመቀበል ዝግጁ መሆን እንዳለበት ለራሱ እየነገረ ነበር። አዲስ አመት በመጣ ቁጥር ደረጃውን ለማሻሻል የሚያቅድ ቢሆንም ምን ተማርኩ እያለ ራሱን እየጠየቀ አለመሆኑን ተረዳ። እያንዳንዱን ቀን ምን እንደተማረ የሚጠይቅ ሰው በእያንዳንዱ እለት ውስጥ የሚቀዳ የህይወት ትምህርት ሊኖር እንደሚችልም አሰበ።
አዲስ የተማሪነት ልብ ሊኖረን እንደሚገባ በመረዳት ውስጥ አዲስን አመት ተስፋ ብናደርግ መልካም ነው። ኢትዮጵያ የበረከቱ ተማሪዎች ያሉባት ሀገር ነች። ተማሪዎች እውቀትን በአግባቡ ቀስመው ለአዎንታዊ አስተዋጽኦ እንዲሆኑ ማድረጉ ለነገ ሊባል የሚችል ስራ አይደለም። ትውልድን በመቅረጽ ሂደት ውስጥ እያንዳንዱ ቀን እድል ነው። እድልነቱም ተማሪው እውቀት ባደረገው ልክ ይለካል። ከአንድ ምእራፍ ወደ ሌላ ምእራፍ በእውቀት እያደጉ ለመሄድ እያንዳንዱ ተማሪ የሚያውቀውን መለካት መቻል አለበት።
የጋብቻ ጥያቄው
የጋብቻ ጥያቄ ማቅረብ እንዲሁም ቤተሰብ ለመመስረት ሲታሰብ አዲስ አመት አብሮ ይነሳል። በአዲሱ አመት አገባለሁ፤ ወይንም ሽማግሌ እልካለሁ ወዘተ ልንልም እንችላለን። ጋብቻን የሚያህል ታላቅ ነገር በአዲስ አመት ውስጥ ጎልተው ከሚጠሩ እቅዶች መካከል ቢሆን የሚገርምም አይደለም። የጋብቻው ጥያቄ ሰምሮ ወደ ትዳር ሲኬድም አዲስ ህይወት ይጀመራል። ከፍ ያለ የሃላፊነት ስሜትም ይፈጠራል።
ሆያሆዬ የሚሉት ልጆች የሚያቀርቡት ጭፈራ ግጥም ስንኙን ስንሰማው ቤተሰብ መስርቶ የተከበሩ መሆኑ ያለውን ቦታ ያሳያል። ታዳጊዎቹ በጭፈራቸው ውስጥ መልካም ምኞታቸውን ያሰማሉ። መልካም ምኞታቸውም ልጅ ወልዶ በመሳም ይሁን ንብረት በማፍራት ሊገለጽ ይችላል።
በህይወት ጉዟችን ውስጥ ደስታም ሆነ ፈተናም የምናስተናግድበት ቦታ ጋብቻ ነው። በጋብቻ ህይወት ውስጥ ያለ ሰውም ሆነ ከጋብቻ ውጭ በላጤነት ህይወትን የሚመራ ሰው አዲስ ቀናትን አሻግሮ ሲያይ ራስን መመልከቱ የተገባ ነው። ለጤናማ ቤተሰብ ግንባታ እኔ የራሴን አስተዋጽኦ ተወጥቼያለሁ ወይ ብሎ መጠየቅ ተገቢነት ይኖረዋል። በአዲሱ ዓመት ውስጥ ወደ ጋብቻ ለመሄድ ማቀድ አንድ ነገር ሆኖ ሳለ በጋብቻ ውስጥ የራስን ሃላፊነት ለመወጣትም መዘጋጀት ይገባል።
በተመሰቃቀለ ቤተሰብ ውስጥ ስንቱ ዋጋ ከፈለ? ስንቶቹ ልጆችስ ባልተገባ መንገድ ማደግ ተፈረደባቸው? ለመልካም እንዲሆን አስበነው የገባንበት ትዳር ሌሎች ትዳርን እንዲፈሩ የሚያደርጋቸው ሆኖ በብዙ አዝነንስ ይሆን? በየአቅጣጫው አዳዲስ የትዳር መንገዶችን ዓለማችን ታስተናግድ ዘንድ ምሳሌያዊ የሚሆን ቤተሰብን መመስረት ተራራ መሰለ።
እናት አባቶቻችን ያጣጣሙትን አይነት የቤተሰብ ህይወት እንኳን ማጣጣም የማይችል ትውልድ እየመሰልን እንዳለን ለመረዳት እሩቅ መሄድ አያስፈልገን ይሆናል።
የጋብቻን ጥያቄ አቅራቢ ሽማግሌዎችም፣ ሚዜዎ ችም ሆኑ ሌላው ቤተሰብ ደስታችንን ተካፍለው በጥቂቱ ነገራችንን ተከታትለው ወደመጡበት የሚመለሱ ናቸው። ለትዳራችን ቦታ ሰጥተን በንጽህና እንዲሁም በመቀባበል ለመምራት የራስን ስራ መስራቱ የራሳችን ሃላፊነት ሆኖ የሚቀር ነው። የራስን ሳይሰሩ ጠባቂ ብቻ ሆኖ፤ አዲስ አመት አዲስ ነገር ይዞልን እንደሚመጣ መጠበቅ ትርጉም የለውም። በቤተሰቡ ሰላምን የሚሻ ሰው ሁሉ ከአዲስ አመት ተስፋ ከማድረጉ በፊት ራሱን መመልከቱ ተገቢነት አለው። ባልና ሚስት ድርሻቸውን ሲወጡ፤ ልጆችን ተከታትለው ሲያሳድጉ፤ መቀባበል ሆነ መተሳሰብ ሲኖር እያንዳንዱ ቀን ውስጥ አዲስ ነገርን ይዛ ትመጣለች። በሥራ ቦታ ሰላም ብናጣ ምናልባት በቀላሉ ሥራ እንቀይር ይሆናል፤ የትዳር ሰላም ማጣት ግን በቀላሉ የሚተው ነገር አይደለም። ትውልዱ ለትዳር እንዲሁም ለቤተሰባዊ ሃላፊነት ራሱን እያዘጋጀ እንዲያድግ ማድረግ አስፈላጊ ነው። አዲስ፣ አዲስ … ወዘተ ከሚለው የነሐሴ ወርና የጳጉሜ ቃላቶቻችን ባሻገር ትኩረት ወደ ውስጥ ለማለት ነው።
የአካባቢው የተከበሩ ሽማግሌ ወደቤታቸው እያዘገሙ ሳለ እንግዳ ሰው ገጠማቸው። ግለሰቡም አቅጣጫ ጠፍቶት የሚፈልግ ነበር። መሄድ የሚፈልገው ወደ እንደራሴው ጊቢ ነበር። እርሳቸውም አቅጣጫውን አሳይተው የአዲስ አመት ዋዜማ የህይወት አቅጣጫ ፍለጋ ምክንያት የሚባዝኑ ሰዎችን እያሰቡ ወደ ቤታቻው ዘለቁ።
አቅጣጫ ፍለጋ
ከእዚህ በፊት ወደማናውቀው አካባቢ ለመሄድ ስንነሳ አቅጣጫውን ለማግኘት ጥረት እናደርጋለን። ባለንበት ዘመን ካርታን ተከትሎ መሄድ ጅምር ቢኖርም በእኛ ዘንድ ግን ያን ያህል በስፋት የተለመደ አይደለም። አቅጣጫን መሳት ልብን ያደክማል። አቅጣጫ መሳት የሚያስከፍለውም ዋጋ አለ።
በህይወት ጉዟችን ውስጥ አቅጣጫ ትልቁ ነገር ነው። አቅጣጫን ማስተካከል ጤናማ ፍላጎት ነው። አቅጣጫን ማስተካከል ግን ለሁሉም ቀላል አይደለም። ስህተት እንደሆነ ከምናስበው ነገር ለመውጣት ከራሳችን ጋር መማማሉ የተለመደ ነው። ሆኖም ያሰብነውን ማድረግ ሳንችል ቀርተን ራሳችንን እናገኘውና እንገረማለን። አመት መጥቶ በሄደ ቁጥር በተሳሳተ መንገድ ውስጥ ያለው አቅጣጫችን እንዲስተካከል ተስፋ እናደርግም ይሆናል።
አቅጣጫ ፍለጋ በብዙ የህይወት ክፍል ውስጥ ሊገጥመን ይችላል። በትዳር ህይወት ጉዳይ፣ በሥራ ጉዳይ፣ በማህበራዊ ህይወት፣ ከሱስ በመውጣት፣ ገንዘብ በመያዝ ወዘተ አቅጣጫ ፍለጋ ውስጥ እንሆን ይሆናል። ከትናንት ትምህርት ውስጥ የሚቀዳ ነገን ስናስብ መሆን ወደ ምንፈልገው እንድንደርስ የሚያደርገን እይታም የያዘ ነው። የአዲስ አመት ዋዜማ ውስጥ ያሉት ሳምንታትን በስፋት አእምሮአችን በአቅጣጫ ፍለጋ ተሞልቶ እናየው ይሆናል። አቅጣጫ ፍለጋ አስፈላጊ ነገር ነው። አቅጣጫ ፍለጋ ሊበዛልን የሚገባ ጉዳይ ነው። አቅጣጫ ፍለጋ በግልጽነት ራሳችንን መርምረን የምንተልመው ሊሆን የተገባ ነው።
ዛሬ ወደ ውስጣችን ስናዳምጥ በተሳሳተ መንገድ እንደሆን የሚሰማን ምን ጉዳይ አለ? ውስጣችንን ባዳመጥን ቁጥር የሚያስቃስተንም ይሆን? እንዲህ አይነት ስሜትን ተሸክመን ወደ አዲስ አመት ከመግባት ስሜቱን አዳምጦ መስተካከል የሚገባው ጉዳይ ላይ ውሳኔ ማሳለፍ ተገቢነት ይኖረዋል። በተደጋጋሚ ሞክረን ባልተሳካልን ነገር ተስፋ ወደመቁረጥ ከመሄድ የቀደመው ግምገማችን ውስጥ የነበረውን ጉድለት በመገምገም አሁንም ለሌላ ሙከራ በእችላለሁ መንፈስ መነሳት ያስፈልጋል።
አዲስን ቀን አዲስ የሚያደርገው በራሱ በቀኑ ሳይሆን በውስጣችን በሚፈጠረው አዲስ መነሳሳት ነው። አዲሱ መነሳሳት በጥንካሬ ሲሆን አቅጣጫ ፍለጋውን ያቀለዋል። አቅጣጫ ፍለጋው ወደ ውጤት ከመምጣት ባሻገር ነገ ላይ ለሚገጥመን ፈተና የሚረዳ ትምህርትን ከትናንት ማግኘት የምንችለው በአዲስ ልብ በመነሳሳት ነው።
በሂደት ውስጥ እየተገነባ የሚሄድ ነገር ጥንካሬም እንዲሁም መሰረት ይኖረዋል። አዲስ፤ አዲስ፤… የሙሉ ቃላት በሚደመጡበት የአዲስ አመት ዋዜማዎች ውስጥ ሆነን ማሰብ ከሚኖርብን ነገር መካከል የያዙትን ስለማጠናከር ነው።
የያዙትን ማጠንከር
አንተ ተራ ሰው አይደለህም። አንቺም እህቴ ተራ ሴት አይደለሽም። ሁላችንም አንዳች የምንቆጥረው ነገር በሰውነታችን ውስጥ አሉ። ዛሬ የያዘነውን ቆጥረን እና እውቅና ሰጥተን ወደ ተሻለው ለመሄድ ማለት ተገቢ ነው። ድንገት በቅጽበትና በሎተሪ መልክ የሚገኝ ውጤትን ከመጠበቅ እያንዳንዱን ያለንን ነገር በአግባቡ በመጠቀም ወደ ከፍታ መራመድን መተለም አለብን። ፈተና ሁሌም የሚኖር ነው፤ በውስጣችን ባደግን ቁጥር የበለጠ እየቀለለን የሚመጣ።
ታዳጊዎቹ ሆያሆዬ እያሉ ነው፤ ባለጅራፉም ጅራፉን እያጮኸ፤ በእንቁጣጣሽ ቀን ደግሞ ወጣት ሴቶች አበባየሁ እያሉ ሊደመጡ ወዘተ አዲስ፤ አዲስ፤ አዲስ… ። የአዲሴ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሆና በውስጧ አዲስን ነገር መፍጠር እንደቻለች ሁላችንም የአዲሱን አመት የመጀመሪያ ቀን በልዩ ሁኔታ ከመጠበቅ በፊት በቀሩት ቀናት በታላቅ እድልነት እየመጣ ላለው አመት በውስጣችን እንዘጋጅ። በግልጽ ራእይ፤ በግልጽ ግብ፤ ለግባችን በሚሆን የተግባር ሰውነት፤ በመልካም ባህሪና እሴት ወዘተ።
በአገልጋይ ዮናታን አክሊሉ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 15/2013