የኢትዮጵያ ወጣቶች ሰላምና ብልጽግና ተልዕኮ ሊግ የተቋቋመው በኢፌዴሪ ሲቪል ማህበረሰብ ኤጀንሲ በአዋጅ 2011 ነው። ሊጉ የተቋቋመው በመጀመሪያ ወጣቱን በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ለማድረግ ነው። ሁለተኛው ዘላቂ ሰላም በአገሪቱ እንዲሰፍን የበኩሉን ሚና እንዲጫወት ታስቦ ነው። ዘላቂ ሰላም የሚመጣው በፖሊስ ኃይልና በፍትህ አካላት ብቻ ሳይሆን ስለ ሰላም ግንዛቤ በመስጠትና በማስተማር ሰላም ማምጣት ይቻላል የሚል እምነት አለ። ስለዚህ ዘላቂ ሰላም እንዲመጣ የኢትዮጵያ ወጣቶች ሰላምና ብልጽግና ተልዕኮ ሊግ ስለ ሰላም ወጣቱን ያስተምራል ማለት ነው። በስድስተኛው አገራዊ ምርጫ ሊጉ ቅኝት ከማድረግ አንስቶ በምርጫ አስፈፃሚነት ውስጥ ተሳትፎ አድርጎ ነበር። ከሊጉ ፕሬዚዳንት አቶ ብርሃኑ በቀለ ጋር በምርጫ ስራዎች ዙሪያ ቆይታ አድርገናል። መልካም ንባብ።
አዲስ ዘመን፡- የነበረው ተሳትፎና ትዝብቱ ምን ይመስላል?
አቶ ብርሃኑ፡– ስድስተኛውን አገራዊ ምርጫ አስመልክቶ ከምርጫ ቦርድ በተሰጠን ኃላፊነት መሰረት የመራጮች ስነ ዜጋ ትምህርት ስልጠና ስንሰጥ ነበር። በሊጉ ለ133 ሺህ 500 ዜጎች የመራጮች ስነዜጋ ትምህርትና ስልጠና ተሰጥቷል። ከነዚህ መሀል ሴቶችና ወጣቶችን እንዲሁም አካል ጉዳተኞችን ያካተተ ስልጠና ነበር። ሊጉ በስድስተኛው አገራዊ ምርጫ በሶስት ማለትም ቅድመ ምርጫ፣ በምርጫው ወቅት እንዲሁም ከምርጫው በኋላ በሚል ከፍሎ ሲንቀሳቀስ ነበር። አሁን የምርጫው ወቅት ተጠናቆ የድምጽ ቆጠራው ተግባር እየተከናወነና ውጤቱም እየተገለጸ ነው። በዚህ ወቅት አንዳንድ ቦታዎች ችግሮች ይፈጠራሉ የሚሉ ስጋቶች ነበሩ። በአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ግን ምንም አይነት የጸጥታ ችግርና የሰላም መደፍረስ አልነበረም። በዚህም ውጤታማ የምርጫ ወቅት እንደ ነበር አይተናል።
ምርጫው ያለማንም ጣልቃ ገብነትና ምንም አይነት የመንግስት ተጽዕኖ ሳይኖር የተከናወነ ነው። ምርጫው ተጠናቆ ውጤት የሚገለጽበት ወቅት ላይ አለመግባባቶች ይኖራሉ ተብሎ ቢፈራም በአሁኑ ምርጫ ግን ይህ ሁኔታ አልተፈጠረም። ምክንያቱም ወጣቱ ያለምንም ህይወት መጥፋት፣ ንብረት መውደምና ያለምንም ችግር ቅሬታውን በተቋቋሙ ፍርድ ቤቶች ማቅረብ የሚችልበት ሁኔታ በመፈጠሩ ነው። በተቋቋመው ፍርድ ቤት ማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ በተወካዮቻቸው መሰረት ቅሬታ ማቅረብ ይችላሉ። ነገር ግን ወጣቱን ወዳልሆነ መንገድ እንዲያመራ መገፋፋት አስፈላጊ አይደለም። ንብረትና የሰው ህይወት እንዳይጠፋ ሁሉም በኃላፊነት ስሜት መንቀሳቀስ አለበት። ወጣቱ በዚህ ደረጃ ተንቀሳቅሶ ጥያቄ ካለው ገለልተኛ ሆኖ ለተቋቋመው ፍርድ ቤት ማቅረብ ይችላል።
አዲስ ዘመን፡- ሊጉ በታዛቢነት የት የት ቦታዎች ላይ ተንቀሳቅሷል? ምን ምን ተግባራትንስ አከናውኗል?
አቶ ብርሃኑ፡– በምርጫው ወቅት የመታዘብ ስራው አስቸጋሪ ሁኔታዎች ነበሩት። በምርጫው 45 ሲቪክ ማህበራት የታዛቢነት ፈቃድ አግኝተው ሲንቀሳቀሱ ነበር። ሊጉ በምርጫው ወቅት የመታዘብ ስራ ላይ ብዙም ትኩረት አላደረገም ነበር። ምክንያቱም ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በጀት ባለመልቀቁ የታሰበውን ያክል የመታዘብ ስራው አልተከናወነም። ሊጉ አብዛኛውን ገንዘብ ያዋለው በስነዜጋ ትምህርትና ስልጠና ላይ ነበር። በዋናነት አስተሳሰብ ላይ መስራት አስፈላጊ በመሆኑ ወደዛ ትኩረት ተሰጥቷል። ለታዛቢነት የአገር ሽማግሌዎችና የተለያዩ ሲቪክ ማህበረሰቦች ተሳትፎ አድርገዋል። ሊጉ ለሶስት ወራት ተከታታይ የመራጮች ስልጠና ሲሰጥ ቆይቷል። ለስልጠናም ወደ ሁለት ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገ ሲሆን የበጎ ፈቃድ አሰልጣኞቹም ወጣቶች ነበሩ።
የመራጮች ሰልጠና ሲሰጥ ግብዓት ለማቅረብ፣የስልጠና ቦታ ለማዘጋጀት እንዲሁም ሌሎች አስፈላጊ ነገሮችን ለማሟላት ሊጉ ገንዘብ አውጥቷል። በዚህም መታዘብ ላይ ብዙ ተሳትፎ አልተደረገም። ነገር ግን የተወሰኑ አባላትን በማሰማራት የቅኝት ስራዎች የተከናወኑ ሲሆን በምርጫው ወቅት ህብረተሰቡ ሰላማዊ በሆነ መንገድ ድምጹን ሲሰጥ መዋሉን መታዘብ ተችሏል። ስራዎችም በጥንቃቄ የተከናወኑ ሲሆን የፀጥታ አካላትም በተጠንቀቅ ኃላፊነታቸውን ሲወጡ ነበር። በወቅቱ ጎላ ያለ ህገወጥ ተግባር አልታየም ነበር።
ሊጉ ቅኝት ባደረገበት ወቅት በምርጫ ቦርድ በኩል ሊስተካከሉ የሚገባቸው ጉዳዮች እንዳሉ የተስተዋለ ሲሆን ለምሳሌ የምርጫ ወረቀት ማጓጓዝን ብንመለከት የምርጫ ወረቀቱ ቀደም ብሎ ወደ ምርጫ ጣቢያ መምጣት ሲገባው በምርጫው እለት በመከናወኑ ምርጫውን አጓቶ ነበር። የምርጫ ቁሳቁስ ከሁለት ቀናት በፊት መድረስ ሲገባቸው አለመድረሳቸው መራጮችን ለረጅም ሰልፍ ዳርጓቸዋል። በተለይ ይህ ሁኔታ ክልሎች ላይ ተስተውሏል። ይህ ሁኔታ የምርጫ አስፈፃሚዎችን ድክመት የሚያሳይም ነው። በተለያዩ አካባቢዎች የማስተባበር ችግሮችም ነበሩ። በቀጣይ ምርጫ ቦርድ ችግሮችን ለይቶ የሚፈታበት መንገድ ማበጀት አለበት።
ሌላው በየምርጫ ጣቢያው የተመደቡት ምርጫ አስፈፃሚዎች ውስጥ ሊጉ አንድ ሺህ አምስት መቶ አባላቱን አሳትፏል። በተመደቡት አስፈፃሚዎች በኩል የስልጠና ክፍተት (ቅድሚያ አስፈፃሚዎቹ ቀድመው የምርጫውን ሁኔታ አውቀው መግባት የነበረባቸው ከመሆኑ አኳያ) ቢኖርም ያሉባቸውን ችግር እዛው እርስ በእርስ በመተራረም ስራቸውን አከናውነዋል።
በመታዘቡ ሂደት መራጮች በስህተት ለሁለት ተፎካካሪ ፓርቲዎች ድምፅ የሰጡበት ሁኔታ የነበረ ሲሆን፤ የተሰጡ ድምፆች እንዲጣሉ ተደርገዋል። እነዚህ ችግሮች ቀስ በቀስ በመተራረም እንዲስተካከሉ ተደርጓል። በምርጫው ቀን ጠዋት ላይ ረጃጅም ሰልፎች ይስተዋሉ የነበረ ሲሆን ለሰልፉ መርዘም የምርጫ አስፈፃሚው አካል በቂ ስልጠና ላለማግኘቱ ማሳያ ነው።
በአንዳንድ አካባቢዎች ያልተፈቀዱ የምርጫ ጣቢዎች ተቋቁመው መገኘት እንደ ችግር የታየ ሲሆን ይህን ሁኔታ ምርጫ ቦርድ በፍጥነት እንዲያስተካከል ተደርጓል።
አዲስ ዘመን፡- ሊጉ በተዘዋወረባቸው ምርጫ ጣቢዎች ያጋጠሙ ችግሮች ምን ነበሩ?
አቶ ብርሃኑ፡– ሊጉ በተንቀሳቀሰባቸው ምርጫ ጣቢያዎች ከታዛቢና ከፓርቲዎች የተስተዋሉ ችግሮች ነበሩ። አንዳንድ ፓርቲ ደጋፊዎች በቡድን ሆነው ያለ ምርጫ ቦርድ ፈቃድ እንታዘባለን ብለው ማስቸገራቸው በዋናነት ይጠቀሳል። በወቅቱ የፀጥታ አካላት ችግሩ ሳይባባስ እዛው ሊፈቱት ችለዋል። ፓርቲዎቹ እራሳቸው የወከሏቸው ታዛቢዎች ምርጫ ጣቢያ የተገኙ ሲሆን ደጋፊዎቻቸው ያሳዩት ያልተገባ ባህሪ ሊስተካከል የሚገባው ነገር ነው። ሌላው የምርጫ ታዛቢዎች ያሳዩት ስነምግባር አስተማሪ የሚሆን ነገር ነው። በምርጫው ወቅት ታዛቢዎች በዝምታ ሁኔታዎችን መከታተል እንጂ ለማውራት አይፈቀድላቸውም። ይህን አክብረው ሰርተዋል። ዓለም አቀፍ ታዛቢዎችም ምርጫውን በሰላማዊ መንገድ ታዝበዋል። በምርጫው ከበድ ያለ ችግር አልተፈጠረም። መራጩ ህዝብ በተቻለው አቅም ሁሉ ለመረጠው ፓርቲ ድምጹን በመስጠት ጥሩ ሽነ-ምግባር አሳይቷል።
አዲስ ዘመን፡- በስድስተኛው አገራዊ ምርጫ የወጣቱ ተሳትፎ በማስተባበርም ሆነ በመምረጥ የነበረው ሁኔታ እንዴት ነበር?
አቶ ብርሃኑ፡- የአገራችን ወጣቶች በስድስተኛው አገራዊ ምርጫ ያሳዩት ሥነ ምግባር በጣም የሚመሰገን ነበር። ለቀጣይም በተለያዩ አገራዊ ሁኔታዎች ላይ ሊቀጥል የሚገባው ነው። ምርጫው ሰላማዊ በሆነ መንገድ እንዲካሄድ ከጸጥታ አካላት ጋር በመተባር ሲያስተባብሩ ነበር። በተለይ ረጃጅም ሰልፎች በነበሩበት ወቅት ወጣቱ ከፍተኛ ትብብር በማድረግ ምርጫው እንዲከናወን አድርጓል። በዚህም የምርጫው ሁኔታ በተፋጠነና በሰላማዊ መንገድ ሊጠናቀቅ ችሏል። ስለዚህ ወጣቱ በምርጫው ወቅት ያሳየው ተሳትፎ አመርቂ ነበር ማለት ይቻላል። የአዲስ አበባ ወጣት ነዋሪዎች ላሳዩት ትብብር ሊመሰገኑ ይገባል።
አዲስ ዘመን፡- በቀጣይስ የምርጫው ውጤት በሚገለጽበት ወቅት ወጣቱ በምን አይነት ሁኔታ መቀበል አለበት?
አቶ ብርሃኑ፡– ከምርጫ በኋላ የሚነሱ ግርግሮችና ውዥንብሮችን ወይም ረብሻዎች የሚፈጠሩት በውጤት ወቅት ነው። ወጣቱ በሰለጠነ መንገድ የሚንቀሳቀስ ከሆነ ችግር አይመጣም። ወጣቱ ይመራኛል ብሎ የሚያስበውን ፓርቲ ሊመርጥ ይችላል። በምርጫው ለተፎካከሩት ሁሉ ድምጽ መስጠት ስለማይችሉ ለሚፈልጉት ድምጻቸውን ይሰጣሉ። ነገር ግን ድምጽ የሰጧቸው ፓርቲዎች ያላሸነፉ ከሆነ ብጥብጥ የመፍጠር አዝማሚያ የሚያሳዩ ይኖራሉ። እነዚህ ወጣቶች አላስፈላጊ ዋጋ ከሚከፍሉ ማድረግ ያለባቸው በተወካዮቻቸው አማካኝነት በገለልተኛ ፍርድ ቤት ጉዳያቸውን ማቅረብ እንጂ ግርግር ውስጥ መግባት የለባቸውም። ግርግር ሲፈጠር የግለሰብና የመንግስት ሀብት ስለሚወድምና የሰው ህይወት ስለሚጠፋ ይህን መንገድ መከተል የለባቸውም። ይህን ሁኔታ የሚከተሉ ከሆነ በወንጀል ተጠያቂ ሆነው በመስሪያ እድሜያቸው እስር ቤት ይገባሉ። ሌላው ደግሞ በሚፈጠሩ ግርግሮች ህይወታቸውን ሊያጡ የሚችሉ ወጣቶች ሊኖሩ ስለሚችሉ ይህ አይነቱ ተገቢ ያልሆነ ተግባር ለማንም ስለማይጠቅም ሊከሰት አይገባውም።
አዲስ ዘመን፡- ሊጉ ምን ምን ስራዎችን ለማከናወን እቅድ ይዟል?
አቶ ብርሃኑ፡- የኢትዮጵያ ወጣቶች ሰላምና ብልጽግና ተልዕኮ ሊግ የተቋቋመበት አንዱ ዓላማ የሰላም ግንባታ ስልጠና መስጠት ነው። ሊጉ ለወጣቶች የሰላም ግንባታ ስልጠና የሚሰጥ ሲሆን ሌላኛው ስራው ደግሞ የስራ ፈጠራ ክሂሎት ስልጠና መስጠት ነው። ለወጣቱ የስራ ፈጠራ ክሂሎት ስልጠና የሚሰጠው የስራ እድል በመፍጠር እራሳቸውንና አገራቸውን እንዲጠቅሙ ነው። ወጣቱ ተቀጣሪ ሆኖ ከሚሰራ የራሱን ስራ ፈጥሮ መስራት ውጤታማ ስለሚያደርግ ነው። የሰላም ግንባታ ስልጠና የሚሰጠው በየቦታው የሚታዩ የሰላም ችግሮችን ለመፍታት ነው። ይህም ወጣቱ የሰላም አምባሳደር እንዲሆን እገዛ ያደርጋል።
ሌላው የሊጉ ስራ አረንጓዴ አሻራ ላይ የበኩሉን ድርሻ መወጣት ነው። በክረምቱ ወራት በተለያዩ አካባቢዎች ችግኝ ለመትከል እቅድ የተያዘ ሲሆን በሊጉ ውስጥ ከሚገኙት አባላት ውስጥ አስር ሺህ ወጣቶችን ለማሳተፍ እቅድ ተይዟል። ከእነዚህ መሃል ሃምሳ ወጣቶችን ከእያንዳንዱ ክልል በመመልመል በተለያዩ ክልሎች እየተጓዙ ችግኝ እንዲተክሉ ይደረጋል። ለምሳሌ በኦሮሚያ ክልል የሚገኙ ወጣቶች አማራ ክልል ሄደው ችግኝ እንዲተክሉ ይደረጋል። በሌሎችም ክልሎች እንዲሁ ይደረጋል። ይህም የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱን ለማጠናከር እገዛ ያደርጋል።
በክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ለመስጠት ሊጉ ዝግጅት ያደረገ ሲሆን በጤናው ዘርፍ የተመረቁ ወጣቶች በጤና ጣቢያዎችና በሆስፒታሎች ሄደው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት እንዲሰጡ ይደረጋል። በክረምት ወራት በጎርፍ የሚጠቁ አካባቢዎችን በመለየት ቅድመ መከላከል ስራዎችን ለማከናወን ዝግጅት ተደርጓል። በዚህ ስራ ላይ የተዘጉ የውሃ ማስተላለፊያ ቦዮች እንዲከፈቱ የማድረግ ስራ ይሰራል። በትምህርቱ ዘርፍ ደግሞ የጎልማሳ ትምህርት እንዲሰጥ ይደረጋል።
መርድ ክፍሉ
አዲስ ዘመን ሰኔ 25/ 2013