ሀገር ታፍራና ተከብራ የምትኖረው የአየር የምድርና የየብስ ክልሏን ነቅቶ የሚጠብቅ ከማንኛውም ዓይነት የጠላት ወረራና ጥቃት ሊከላከል ሊጠብቃት የሚችል ዘመናዊ የመከላከያ ኃይል ሲኖራት ብቻ ነው፡፡የሀገር መከላከያ ሠራዊት የሀገር ዋስትና መከታና አለኝታ ነው፡፡ ዜጎች ሊከበሩ ሀብት ሊያፈሩ አንቱ ተብለው ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ገንዘብና ሀብት ዋጋ የሚኖረው የተከበረ የታፈረ ሰላም ሲኖር እና የህግ የበላይነት ሲከበር ብቻ ነው፡ሀገርንና ሰላሟን የሚጠብቀው ሕዝቡ ቢሆንም መከላከያው ደግሞ መሳሪያ የታጠቀ የሀገሩን ሰላምና ዳር ድንበርዋን ለመጠበቅ በተጠንቀቅ ቆሞ የሚገኝ የሕዝብ ልጅ ነው፡፡ድሮም ዛሬም እንዲሁ ነበር፡፡ ትላንትም እኛ ዛሬም እኛ፡፡
ካልተከላከሉት ዳርና ዳር ቆሞ …መሬትም ይሸሻል…ሀገርም ይሄዳል… እያየ አግድሞ እንዲሉት ሆነና ሀገር ጠባቂዋን አስከባሪዋን ጀግናዋን ሁሌም ታከብራለች፡፡ትወዳለች፡፡ታነግሳለች፡፡ ሰላምና ነጻነቷን ክብሯን ግንባሩን ሰጥቶ ከጠላት ተፋልሞ የሚጠብቅላት መከላከያ ኃይል ከሌላት ሀገር ትደፈራለች፡፡ ትናቃለች፡፡ዜጎቿም ነጻነት አልባ ክብር አልባ ይሆናሉ፡፡በትንሹ የመንደር ጎረምሶች፤ የጎጥ አለቆች፤ የቡጢኞች፤የጋጠ ወጦችና ስርአተ አልበኞች መጫወቻ መሆን ይከተላል፡፡ እንዳሻቸው እየፈነጩ እያስገበሩ እየደለቁ ሌላውን ነጻነቱን ገፈው የሚኖሩበት ሁኔታ ይፈጠራል፡፡
ለዚህ ነው ለመከላከያ ኃይላችን ያለንን ጥልቅ ፍቅርና አክብሮት እጅግ የላቀ የሚሆነው፡፡ ምድር ሃይላችን ቀንና ሌሊት በረሀና ሀሩር ብርድና ዝናብ ሳይል በቀበሮ ጉድጓዱ ውስጥ ሆኖ ዳር ድንበሩን የሚጠብቀው ፤አየር ኃይላችንም የሰማዩን ክልላችንን ሲቃኝ ውሎ የሚያድረው ሀገሬ ኢትዮጵያ እኔ እያለሁ አትደፈሪም ነው መልእክቱ፡፡ ደልቶት ተመችቶት አይደለም፡፡ልጆቹን፣ሚስቱን፣ ቤተሰቡን ፣እናት፣ አባቱን ትቶ ነው ለሀገር ጥበቃ የሚንከራተተው፡፡
ይሄንን ጀግና ያላከበርን ከቶ ማንን እናከብራለን ? ለመከላከያ ሠራዊታችን ታላቅ አክብሮት ከሌለን ለሀገራችንና ለሕዝቧም አክብሮት ሊኖረን አይችልም፡፡ ዘንድሮ የሚከበረውን የመከላከያ ሠራዊት ቀን ልዩ የሚያደርገው በለውጡ ማግስት የሚከበር መሆኑ ነው፡፡መሪ መፈክሩም ‹‹ለውጡን እንጠብቃለን ፣እናስቀጥላለን፣ሕዝባዊ ወገንተኝነታችንም የበለጠ ይረጋገጣል›› የሚል ነው፡፡መከላከያ ሠራዊታችን የሀገራችን ሕልውና ሰላምና ደህንነታችን ማረጋገጫ የጥቃት መከላከያ ጋሻና መከታችንም ነው፡፡ በኢትዮጵያ ምድርና ሰማይ ስር ሆናችሁ ሌት ከቀን ሀገራችሁን ለምትጠብቁ የሀገር መከላከያ ሠራዊት አባላት በመሉ ክብርና ምስጋና በያላችሁበት ይድረሳችሁ፡፡
ኢትዮጵያ በተለይም ከጣሊያን ወረራ በኋላ በቂ ትምህርት ስላገኘች ዘመናዊ የጦር ኃይል ለመገንባት በእጅጉ ደክማለች፡፡ በጣሊያን ወረራ ምክንያት የተቋረጠው የሆለታ ገነት ጦር መኮንኖች ትምህርት ቤት እንደገና በድል ማግስት ተመስርቶ ሥራውን ጀምሮም ነበር፡፡በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነው የክብር ዘበኛ ወታደራዊ አካዳሚ የዛሬው ቤላ ግቢ በስዊድን አሰልጣኝ መኮንኖች እየተመራ ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ዙር መኮንኖችን አስተምሮ ለዘመናዊው ሠራዊት ግንባታ እርሾ ሆነው ከክብር ዘበኛው ክፍለ ጦር አልፈው የሀገራችን መከላከያ ከፍተኛ አዛዥ ጀነራሎች ለመሆን በቅተው አገልግለዋል፡፡የሀረር ጦር አካዳሚ ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ እስከ ተቋረጠበት ጊዜ ድረስ እስከ 21ኛ ኮርስ መኮንኖችን አስመርቆ አልፏል፡፡ የሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤትም እልፍ መኮንኖችን አፍርቷል፡፡ኢትዮጵያ ሠራዊቷን ለማዘመን ወቅትና ጊዜ የጠየቀውን መሳሪያም አስታጥቃለች፡፡ድንቅ አየር ኃይል ፤ባሕር ኃይል ገንብታም ነበር፡፡ ታሪካችን በመውደቅና በመነሳት መካከል ያለ በመሆኑ ለጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ ምስጋና ይድረስና እነሆ ዛሬ ደግሞ አዲስ ጎጆ ወጪ ሆነን ባሕር ኃይላችንን እንደ አዲስ ልንገነባ ደፋ ቀና እያልን ነው፡፡ ኢትዮጵያ በዘመናዊ ሠራዊት ግንባታዋ ውስጥ መኮንኖችዋን በተለያዩ የዓለም ሀገራት በመላክ አስተምራለች፡፡አሜሪካ ፣እንግሊዝ፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣እስራኤል፣ሩሲያ፣ ኩባ ፣ቼኮዝሎባኪያ፣ ቡልጋሪያ፣ቻይና ወዘተ፡፡ የተለያዩ የጦር ክፍሎችንም አደራጅታለች፡፡ታንከኛ፣መድፈኛ፣አየር መ ቃ ወ ሚ ያ ፣ ሜ ካ ና ይ ዝ ድ ፣ ተ ዋ ጊ መሐንዲስና የጦር ሰፈር ሥራ መሐንዲስ፤ የሠራዊቱ ሕክምና ክፍልና አገልግሎት በርካታ የሠራዊት ዶክተሮች ነርሶች የጤና መኮንኖች አስተምራ ያበቃች ሀገር ነች፡፡
የሌሎች ሀገራት መኮንኖችና ወታደሮችን ሀገርዋ አምጥታ ያስተማረች ሀገር ነች- ኢትዮጵያ፡፡ ለአፍሪካ የነጻነት ተዋጊዎችም መጠጊያ ስልጠናና ትጥቅ የሰጠች ሀገር ነች የእኛ ኢትዮጵያ፡፡ አሰልጣኞቹም የኢትዮጵያ መከላከያና ፖሊስ መኮንኖች ነበሩ፡፡ የሚያኮራ ታሪክ ያለን ሀገርና ሕዝብ ነን፡ ፡ በጀግንነቱ የተወደሰ የተከበረ ሠራዊት ባለቤቶች ነን፡፡ ኢትዮጵያ ኃያልና ገናና የሆነ ሠራዊት ብትገነባም በውስጥ የነበረው እርስ በርስ ጦርነት ታላቅ የትውልድ መስዋዕትነት ተከፍሎበታል፡፡
የኢትዮጵያ ፖለቲከኞች ለሀገሩ ክብር ሲታገል ሲደማ ሲቆስል የአካል መስዋዕትነት ሲከፍል የኖረን የቀድሞ ሠራዊት ልክ የአንድ ሥርዓት ታማኝ አገልጋይ አድርገው እስከ መመልከት ደርሰው ነበር፡፡ዛሬ ግን ክብሩ እየተመለሰ ታሪኩና ሞራሉ እያንሰራራ ይገኛል፡፡ለሀገሩ ክብር የተዋደቀው ጀግና በገዛ ሀገሩ ላይ ክብሩ ተዋርዶ የጀግንነት ልዕልናው ተሰርቆ እንጀራ ፈላጊ ተንከራታች ሆኖ አሳልፏል፡፡እሱን ለታሪክ እንተወው፡፡
በምስራቅ ኢትዮጵያ የሀገራችንን ድንበር 700 ኪሎ ሜትር ጥሶ በመግባት እስከ አዋሽ ድረስ የእኔ ግዛት ነው ያለውን የዚያድ ባሬ ፉከራና ቀረርቶ ያመከነው በወቅቱ የነበረው ጀግናው የኢትዮጵያ አየር ኃይል የኢትዮጵያ ሠራዊትና የሚሊሺያው ጦር ነበር፡፡ሶማሊያ ኢትዮጵያን ስትወር ኢትዮጵያ በዘመኑ በንጉሱ አማካኝነት ከአሜሪካ መንግሥት ገዝታ ነገር ግን ወደ ሀገር ውስጥ ያልገባው የጦር መሳሪያ እንዲሰጣት ደርግ ሲጠይቅ በወቅቱ የነበረው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ካርተር ገንዘብ የከፈልንባቸውን የራሳችን ሀብት የሆኑት መሳሪያዎች አልሰጥም ብሎ በመከልከሉ ኢትዮጵያ እንድትወረር በገሀድ ፈቀደ፡፡ ግና የሀገር ፍቅር ወኔያቸው እንደፋመ እሳት የሚንተገተገው ኢትዮጵያውን ጀግኖች በታላቅ መስዋዕትነትና ተጋድሎ ወራሪውን ኃይል ደምስሰውና ረግጠው በማስወጣት የሀገራቸውን ዳር ድንበር አስከበሩ፡፡
ቢያንስ እስከ 300 ሺህ ኢትዮጵያውያን በጦርነቱ መስዋዕትነት ከፍለዋል፡፡ የታንከኛ፤ የሜካናይዝድ፤ የአየር በአየር ውጊያ ፣የእግረኛ ሳንጃ ለሳንጃ ውጊያ ሁሉ ኢትዮጵያውያን ጀግኖች ግንባርና ደረታቸውን ሰጥተው ለሀገራቸው ክብርና ነጻነት እስከ ዘለዓለም አሸለቡ፡፡ ‹‹ስንኖር ኢትዮጵያዊ ስንሞት ኢትዮጵያ›› ነን፡ ፡ ከአፈሯ ስር የምንቀር መልሰን የምናብብ የማንፈራ አበቦች ነን፡፡ሞተንም ጀግና የምንተካ፤ ሞተዋል የማንባል፤ ሞትንም ድል የምናደርግ፤ ግን ግን መቼም በኢትዮጵያ ሀገራችን የማንደራደር አንበሶች ነን፡፡ ሺህ ሞት መጣ ቢሉት አንዱን ግባ በለው የምንል፡፡ውዶቻችን በየዘመናቱ ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር ሲሉ ወድቀው በደም ማሕተም ታላቅ ጀግንነት ሰርተው ሲያልፉ አደራው በትውልዱ ጫንቃ ላይ የወደቀ መሆኑ መዘንጋት የለበትም፡፡ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እጅግ ከፍተኛ በሆኑ ሀገራዊ ውጣ ውረዶች ውስጥ አልፏል፡፡ዳሩ በሀገርና በእናት አይቀየሙም ሆነና የዛሬውም ከትላንቱ ብዙ እውነት ይማራል፡፡
በርትቶና ተግቶ ሀገሩን መጠበቅ፤ ፖለቲካ ጅዋጅዌ ውስጥ አለመግባት፣የኢትዮጵያን ዳር ድንበር የአየር የየብስና የምድር ክልል ምንጊዜም ዝግጁ ሆኖ መጠበቅ፡፡ኢትዮጵያ በፊትም ዛሬም ምርጥ ተዋጊ ሠራዊት ያላት ሀገር ናት፡፡ እንኳን ለቤቴ ይመታል ለጎረቤቴ እንዲሉ የራሱን ሀገር ክብር በታላቅ ጀግንነት ጠብቆ የኖረው የኢትዮጵያ ሠራዊት በዓለም አቀፍ ደረጃ ግዳጅ ተሰማርቶ ኮርያና ኮንጎ ተልኮ የሀገሩን ስም በታላቅ ጀግንነት አስጠርቷል፡፡ተወድሷል፡፡ ነጭ ከጥቁር የጦር መሪዎች አስደግድጓል፡፡ምርጥና ጀግና ተዋጊ የጦር ገበሬ መሆኑ በዓለም አደባባይ ተመስክሮለታል፡፡
በዓለማችን ምርጥ ጀነራሎች ለውጊያ ብቃቱና ለጀግንነቱ ተመስክሮለታል፡፡ የዛሬው የአባቶቹ ልጅ የሆነው የዚህ ትውልድ መከላከያ ሠራዊትም በደቡብ ሱዳን፣ በሱዳን/ አብዩ፣በሩዋንዳ፣ብሩንዲ፣ላይቤሪያና ሶማሊያ በሰላም ማስከበር ግዳጅ ተሰማርቶ አኩሪ ግዳጅ ፈጽሟል፡፡ኢትዮጵያውያን የጦር ጀግኖች በተፈጥሮአቸው ወታደር የሆኑ ንቁና ጠንካራ፣ጥቃትን አሜን ብለው የማይቀበሉ ጀግኖች ናቸው፡፡መጠቃት መደፈርን እንደ መረረ ኮሶ የሚቆጥሩም ናቸው፡፡
ከኢትዮጵያ በፊት እንውደቅ እንሙት የሚሉ መሆናቸውንም ዓለም የመሰከረላቸው ናቸው፡፡ የጣሊያንን ዘመናዊና እጅግ የደረጀ ከፍተኛ የጦር መሳሪያዎችን የታጠቀ በወታደራዊ ሳይንስ የተካኑ ጀነራሎች የሚመሩትን ወራሪ ሠራዊት ነው የኢትዮጵያ ሠራዊት ገጥሞ በራሱ የጦር መሪዎች፤ በራሱ ስልት እየተጠቀመ እንዳልነበሩ አድርጎ የፈጃቸው፡፡ የኢትዮጵያ ሠራዊት በተሰለፈበት የውጊያ አውድማ ሁሉ ባለክብርና ባለግርማ ሞገስ ሲሆን ድል አድራጊ ጀግናም ነው፡፡
ለኢትዮጵያ መታፈር መከበር በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር የትውልድ መስዋዕትነት ተከፍሏል፡፡ዛሬ ቆመን የምንራመድበትን መንገድና ነጻ አየር ዝም ብለን ያገኘነው የሚመስላችሁ ወደኋላ ሄዳችሁ የአያቶቻችሁን የአባቶቻችሁን ታሪክ አስታውሱ፡፡ዛሬም ያለው መከላከያ የትናንቱ የኢትዮጵያ ትውልድ ቀጣይ ነው፡፡ በእሱም ደም ውስጥ ሞልቶ የሚንተከተከው ኢትዮጵያዊ ደም አለ፡፡ የኢትዮጵያ የመከላከያ ኃይል ጥንትም ሆነ ዛሬ ለሀገሩና ለወገኑ ታማኝ ቀናኢ ነው፡፡
በታላቅ ኩራትና የሀገር ፍቅር ስሜት የሚገልጹት የኢትዮጵያዊነት የነደደ ስሜት ዛሬም ለዚህች ሀገር ታላቅ ስንቋ ነው፡ ፡ የዘንድሮ የመከላከያ ቀን የካቲት ሰባት ሲከበር ለውጡን ለማስቀጠል፤ ሕዝባዊነትን ለማረጋገጥ ታላቅ ቃል ኪዳን በመግባት ነው፡፡የብዙዎቹ እናት ኢትዮጵያ ዛሬም ወደፊትም በጀግኖች ልጆቿ መስዋዕትነት ተከብራ ትኖራለች፡፡ ጥንትም ሆነ ትናንት ለኢትዮጵያ አንድነት መከበር ታላቅ መስዋዕትነት የከፈሉት ጀግኖቻችን አንጸባራቂ ኮከቦች ናቸው፡፡
ኢትዮጵያ በጥንት ዘመን የነበራት ገናናነትና ክብር ይመለሳል፡፡በስልጣኔና በዕድገትም ወደላቀው ምእራፍ ወደ ታላቅነት ዘመንዋ ትስፈነጠራለች፡፡ የሀገር መከላከያችንን በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ ለማውገዝ የሚሞክሩት መርገምቶች ከእነሱ ቅርምራሚ ፖለቲካዊ አጀንዳ በፊት ኢትዮጵያ የምትባል ገናና ሀገር ነበረች፡ ፡ ዛሬም አለች፡፡ወደፊትም ትኖራለች፡፡ በወሬ ሳይሆን በደም በአጥንት አያቶቻችንና አባቶቻችን ከጠላቶቻቸው ተፋልመው ያስረከቡንን ሀገር በእኛም መስዋዕትነት ክብርዋ ሳይነካ ትቀጥላለች፡፡ብርቱው ክንድዋ ይበርታ !!