ኃይሉ ሣህለድንግል
ኢትዮጵያውያን የዛሬ ሶስት ዓመት ሀገራዊውን ለውጥ ሲጎናጸፉ መንግስት ለዘመናት ሲጠይቁት የቆዩትን የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ እውን ለማድረግ እንዲሚሰራ ማረጋጋጫ መስጠቱ ይታወቃል:: ለውጡ በሶስት ዓመት ጉዞው ካከናወናቸው በርካታ ተግባሮች አንዱም ይሄው ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታው መደላድል የመፍጠር ስራ ነው::
በለውጡ ኢትዮጵያውያን በእጅጉ ተደስተው ድጋፋቸውን በተለያዩ መንገዶች አረጋግጠዋል:: መንግስትም አላሰራ ያሉ የህግ ማእቀፎች እንዲሻሻሉ በማድረግ፣ አዳዲስ ተቋማትን በማቋቋምና ሌሎች የሪፎርም ስራዎችን በማካሄድ ለውጡ ተቋማዊ እንዲሆን ለማድረግ ሰርቷል:: ከተሻሻሉት ህጎች መካከልም የምርጫ ህግ እና የበጎ አድራጎት ማህበራት ማቋቋሚያ ህግ በአብነት ይጠቀሳሉ::
ከዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ አኳያ ያሉትን ብንመለከት በህዝብና በፖለቲካ ፓርቲዎች ዘንድ ከዚህ ቀደም ተአማኒነት ያልነበረው ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በአዲስ መልክ እንዲዋቀር ተደርጓል:: ቦርዱም በተሻሻለው የምርጫ ህግ መሰረት 6ኛውን ሀገራዊ ምርጫ ለማካሄድ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል:: ምርጫው ባለፈው ዓመት ሊካሄድ ታቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ በኮሮና ወረርሽኝ መከሰትና መስፋፋት ሳቢያ መራዘሙ ይታወሳል:: ምርጫውን ዘንድሮ ለማካሄድ እየተሰራ ነው::
ምርጫውን ለማካሄድ የሚያስችለው ሁሉም ስራ በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ መሰረት እየተከናወነ ይገኛል:: መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፤ በምርጫው 47 የፖለቲካ ፓርቲዎች ይሳተፋሉ:: 8ሺ209 እጩዎች የተመዘገቡ ሲሆን፣ ከእጩዎቹ መካከልም 125ቱ በግል ለመወዳደር የቀረቡ ናቸው::
ያለንበት ወቅትም ሀገሪቱ በእጅጉ ምርጫ ምርጫ እያወደች የምትገኝበት ነው:: ፓርቲዎችና የግል ተወዳዳሪዎች የምረጡኝ ቅስቀሳቸውን እያደረጉ ይገኛሉ:: ህዝቡ የመራጭነት ካርዱ ተመዝግቦ እንዲወስድ ቅስቀሳው ተጠናክሮ ቀጥሏል:: ለምርጫው የሚያስፈልጉ ሌሎችም ተግባሮችም እየተከናወኑ ይገኛሉ::
እነዚህ ሁሉ ስኬታማ የሚሆኑት ህዝቡ በምርጫው ድምጽ ለመስጠት የሚያስችለውን ካርድ በተቀመጠለት የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ሲወስድ መሆኑ ይታወቃል:: የመራጮች ምዝገባው ከተጀመረ በርካታ ቀናት ቢሆኑትም፣ ምዝገባው ሊጠናቀቅ ጥቂት ቀናት እየቀሩ ባለበት በአሁኑ ወቅት የተዘመገበው መራጭ ብዛት እዚህ ግባ የሚባል አይደለም እየተባለ ነው:: ምርጫ ቦርድም የሚጠበቀውን ያህል መራጭ አለመመዝገቡን ባለፈው ሳምንት አስታውቋል::
ህዝቡ በነቂስ ወጥቶ ድምጹን ይሰጥበታል ተብሎ በሚጠበቀው በዚህ ሀገራዊ ምርጫ በመራጮች ምዝገባ ላይ መቀዛቀዝ ለምን ታየ? ብሎ መንግስት መጠየቅ ይኖርበታል:: እኔ ግን መራጩን አስመልክቶ በትኩረት ያልተሰሩ ስራዎች እንዳሉ ይሰማኛል::
ህዝብ ድምጽ መስጠት የሚያስችለውን ካርድ ላለመውሰድ የሚችልባቸው ችግሮች ሊኖሩ ይችላሉ:: ችግሮቹን መጠቆም የሚችለው አንድም ህዝቡ እንደመሆኑ መንግስት ህዝቡን ጠጋ ብሎ “እህ” ብሎ ማዳመጥ፣ ህዝቡም በየደረጃው ላለው አካል ችግሮቹን መጠቆም ይኖርባቸዋል::
በተለይ ዜጎች ችግሮቹን ለመፍታት የመፍትሄ አካል እንዲሆን ሲጠይቅም በንቃት መሳተፍ ይኖርባቸዋል:: ምርጫው የእነሱ ጉዳይ መሆኑን መገንዘብ ግዴታቸው ነው:: ዜጎች በሚፈለገው ልክ ለመምረጥ እየተመዘገቡ አለመሆናቸው ምርጫውን ከሩቅ እየተመለከቱ ነው ያሰኛል:: አሁን ለምን ?
እንደ እኔ ምልከታና ያለፉት ጊዜያት ልምዶች እንደሚያመለክቱት የኢትዮጵያ ህዝብ ለበርካታ ጊዜያት በምርጫ ስም ጉድ ተሰርቷል:: በምርጫ ሲነገድበት ኖሯል:: በዚህ ሁኔታ ውስጥ የኖረን ህዝብ ድምጽ ለመስጠት የሚያስችለውን ካርድ ለመውሰድ ለምን እስከ አሁን አልተመዘገበም ብሎ መጠየቅ ብዙም የሚያስኬድ አይመስለኝም::
ህዝቡ በመረጠው መንግስት ተዳድሮ አያውቅም:: ሳይወድ በግድ እየተጎተተ በማስፈራሪያ ካርድ እንዲወስድ ከዚያም በግድ ወጥቶ እንዲመርጥ ሲደረግ ነው የኖረው:: በከተማ የምርጫ ካርድ ያልወሰደና ያልመረጠ አንዳንድ አገልግሎቶችንና የስራ እድል እንዳይገኝ ይደረግ ነበር:: ይሄ እንዲያውም ገራገሩ እርምጃ ነው::
በገጠርም ተመሳሳይ ችግሮች ነበሩ:: ይህ ሁኔታ ዜጎች ሁለተኛ ፊታቸውን ወደ ምርጫ እንዳያዞሩ አድርጓቸዋል ብሎ መናገር ይቻላል:: በዚህ የተነሳ ዜጋው ከፍተኛ የሆነ የምርጫ ጥላቻ (ፎቢያ) ያደረበት ለመሆን ተገዷል::
በዚህ ከባድ ሁኔታ ውስጥ ያለፈ ዜጋ በዚህ ምርጫ በተያዘው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ወጥቶ ለመምረጥ የሚያስችለውን ካርድ አለመውሰዱ አያስገርምም:: ዜጎች በሚጠበቀው መልኩ ለመምረጥ እንዲመዘገቡ ለማድረግ በቅድሚያ ከዚህ የምርጫ ጥላቻ ማላቀቅ ይገባል::
ለመምረጥ አለመመዝገብ በምርጫው ላይ እምነት አለማሳደር ወይም ተጠራጣሪ መሆንንም ሊያመለክት ይችላል:: የኢትዮጵያ ህዝብ ለዴሞክራሲ ሥርዓት ካለው ጽኑ ፍላጎት አኳያ ሲታይ ይህን ምርጫ ይጠራጠራል ብሎ መገመት ሊከብድ ቢችልም “ይህ ለምን ሊሆን ቻለ” ብሎ ራስን በመጠየቅ ለመፍትሄው መስራት ያስፈልጋል::
በምርጫው የእምነት ማጣትና ተጠራጣሪነት ካለ ማስወገድ የሚቻለው ህዝቡ የምርጫውን ሂደት እንዲከታተል እና በውስጡም እንዲያልፍ በማድረግ ነው :: በእዚህ በኩል መንግስት ፣ ፓርቲዎች፣ የግል ተወዳዳሪዎችና የሲቪክ ማህበራት ሚና ከፍተኛ መሆኑ ታምኖበት ጊዜ ሳይሰጠው ሊሰራበት ይገባል::
በሀገራችን መልካም ነገሮች ቢኖሩም፣ ፈተናዎችም በዚያው ልክ አሉ:: የህዝቡም ሕይወት የዚሁ ነጸብራቅ ነው:: እርግጥ ነው ዜጎችን የኑሮ ውድነት፣ የኮሮና መስፋፋት፣ እዚህም እዚያም የሚከሰቱ የሰላምና የፀጥታ ችግሮች እንቅልፍ ነስተዋቸዋል::
በዚህ ሁኔታ ውስጥ ያለ ህዝብ ስለምርጫ ማሰብን ትርፍ ተግባር አርጎ ሊቆጥር ይችላል:: ምርጫ የተጠቀሱትን ችግሮች ለዘለቄታው ሊፈታ እንደሚችል ላይገነዘብ ይችላል:: ይህን ማስገንዘብና ህዝቡ ለምርጫው እንዲመዘገብ መስራት ትኩረት ተሰጥቶት ሊሰራበት ያስፈልጋል:: ለዚህ ደግሞ መንግስት ፣ ፓርቲዎች፣ የግል ተወዳዳሪዎች ሚና ከፍተኛ ነው::
ህዝቡም ከፈተናው ማዶ አዲስ ህይወት እንዳለ መረዳት ይኖርበታል:: በችግሮች ተደነቃቅፎ መውደቅ የለበትም:: አሻግሮ ማየት አለበት:: ያለፉት ሶስት የለውጥ ዓመታት ያስጨበጧቸው ለውጦች አሉ፤ በቀጣይም ተስፋዎች አሉ:: እነዚህን ወደላቀ ደረጃ ለማድረስ ይህ ምርጫ ወሳኝ መሆኑን ተረድቶ ከምንም ነገር ቅድሚያ ሰጥቶ ምርጫውን ሊያስበው ይገባል::
ዜጎች በመጪው ምርጫ ላይ መወሰን የሚችሉበትን እድል ለመጠቀም አሁንም ጊዜው አልረፈደባቸውም:: ለምርጫው መመዝገብ እና የሚመርጡትን ለመለየት ደግሞ የምርጫውን ሂደት በሚገባ መከታተል አለባቸው:: ምርጫውን ከሩቅ በመመልከት በሚፈለገው የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ላይ አሻራን ማኖር አይቻልም:: ነጻነትንና መብትን በመግፋት ሌላ አምስት ዓመት መጠበቅ ነው የሚሆነው::
በምርጫው ለመሳተፍ ከተመዘገቡ ፓርቲዎች እና የግል ተወዳዳሪዎች እጩዎች በስተጀርባ ምን ያህል ህዝብ እንዳለም መገመት አይከብድም:: አሁን ተመዘገበ የሚባለው መራጭ ብዛት ግን ይህን የፓርቲዎቹንም ሆነ የግል ተወዳዳሪዎቹን ቁመና አይገልጽም:: ፓርቲዎችና የግል ተወዳዳሪዎች በዚህ በኩል ብዙ ስራ እንዳለባችሁ ልታውቁ ይገባል::
ሀገራችን እንደ ቀድሞው አይደለችም፤ ነገሮች ተቀያይረዋል፤ በዚህ ላይ የሚጠበቀው ህዝብ በሙሉ በምርጫው በንቃት ቢሳተፍ ታሪክ መቀየር የሚችልበት እድል አለ:: የሚፈለገውን እጩ ለመምረጥ የምርጫ ካርድ በመያዝ ዝግጁነትን ማረጋገጥ ይገባል:: ይህን በማድረግ በምርጫው በንቃት መሳተፍ ካልተቻለ በለውጡ ወቅት የታየውን የዴሞክራሲ ጭላንጭል ማደብዘዝ ይከተላል:: አሁንም ጊዜው አልረፈደም:: ዜጎችን ከምርጫ ጥላቻና መጠራጠር በማውጣት ንቁ ተሳታፊ ማድረግ ይገባል:: ሰላም!
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 12/2013