ዘካርያስ ዶቢ
የበጋ ወቅት ውስጥ ገብተናል።ቅዝቃዜውና ጸሀዩ የሰውን ልጅ ብቻ ሳይሆን አረንጓዴ ስፍራዎችን የሚገዳደር እየሆነ ነው። ይህን ሁኔታ ደግሞ በአዲስ አበባ በየአደባባዩ እና መንገድ አካፋዮቹና ዳርቻ ቦታዎች ላይ በሚገኙ አረንጓዴ ስፍራዎች ላይ በግልጽ እንመለከታለን።
ክረምት ላይ አስውበውን ከቆዩ አረንጓዴ ስፍራዎች ጥቂት የማይባሉት መደንገጥ ጀምረዋል።አንዳንዶቹ ቅጠላቸውን መሸከም አቅቷቸዋል፤ ማርገፍ ነው የሚቀራቸው። ቅጠላቸው ላይ የተሸከሙት አቧራ በራሱ የበጋውን እየጠና መምጣት ያመለክታል።
አንዳንድ አረንጓዴ ስፍራዎች ግን በዚህ የበጋ ወቅትም ከእነ ልምላሜያቸው ናቸው፤ በአካባቢያቸው አሁንም ክረምት ያለ ነው የሚመስለው። ምክንያቱ አረንጓዴ ስፍራዎቹ ውሃ በሚገባ የሚያገኙ መሆናቸው ላይ ነው።
እነዚህ ስፍራዎች በተቋማትና ባለሀብቶች እንክብካቤ የሚደረግላቸው ናቸው ብዬ አሰብኩ፤ እነዚህ አካላት ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን አረንጓዴ ስፍራን በአግባቡ በመያዝ ይታወቃሉ። ክፋቱ በጣም ጥቂት መሆናቸው ላይ ነው፡፡
ሌሎች በመንገድ አካፋይ እና ዳርቻዎች እንዲሁም ሰፋፊ አደባባዮች ላይ የሚገኙት የአረንጓዴ ስፍራዎች ከእነ በውበታቸው እንዲቆዩ ማድረግ ያልተቻለው ለምን ይሆን? የማወራው በየአደባባዩና መንገድ ዳር ላይ ስለሚገኙ አረንጓዴ ስፍራዎች ብቻ ነው። ስለትላልቆቹ የአዲስ አበባ አረንጓዴ ስፍራዎች እያልኩ አይደለም፡፡
በሀገራችን በአሁኑ ወቅት በአረንጓዴ ስፍራዎች ልማት አስፈላጊነት ላይ በቂ ግንዛቤ የለንም ተብሎ አይታሰብም። ከተሞች ግንብ እና መንገድ ብቻ መሆን እንደሌለባቸው ተነግሮናል፤ እኛም ግንዛቤውን ጨብጠናል። ለእዚህም ተብሎ ነው አንድም በየአመቱ በክረምት ወቅት በችግኝ ተከላ ላይ ረጅም ጊዜ የምናሳልፈው፡፡
በአረንጓዴ ስፍራዎች እየተመናመነ መምጣት በእጅጉ ተጎጂ እየሆኑ ከመጡት መካከል ከተሞች ይጠቀሳሉ። በተለይ እንደ አዲስ አበባ ያሉት ግንባታ ሰፊውን ይዞታቸውን እየበላባቸው የሚገኙት ከተሞች ለነዋሪቻቸው ምቹ ሊሆኑ እንደማይችሉ ታስቦ የአረንጓዴ ልማት በስፋት እየተካሄደ ይገኛል። እስቲ በየክረምቱ ለችግኝ ተከላ ያልተወጣበትን አመት ጥቀሱልኝ።መጠኑ ይለያይ እንጂ በየአመቱ በክረምት ወቅት ችግኝ ተክለናል።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ እንደ ሀገር ከተያዘው በቢሊኖች የሚቆጠሩ ችግኞችን የመትከል መርሃ ግብሮች ጋር በተያያዘ የችግኝ ተከላው ይበልጥ ተጠናክሮ ቀጥሏል። መርሀ ግብሩ ከተሞች ለአረንጓዴ ስፍራዎች ልማት ትኩረት እንዲሰጡ የሚያበረታቱ ናቸው። ከዚህ በተጨማሪ በየተከተሞቹ የሚካሄዱ የአረንጓዴ ስፍራ ልማቶች በጀት እየተያዘላቸው ይካሄዳሉ፡፡
አዲስ አበባን ብንመለከት በጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ አስተባባሪነት ሶስት ግዙፍ የአረንጓዴ ልማት ስራዎች ተከናውነዋል። የአረንጓዴ ስፍራ ያለህ ሲባልባት ለቆየችው አዲስ አበባ እነዚህ አረንጓዴ ስፍራዎች ልዩ ትርጉም አላቸው።የከተማዋ ነዋሪዎችና እንግዶቿ የእረፍት ጊዜያቸውን ዘና ብለው እንዲያሳልፉ፣ እውቅት እንዲቀስሙ የሚያደርጉ ብቻ አይደሉም፤ ወደ ከተማዋና ሀገሪቱ የሚመጡ ጎብኚዎችን የቆይታ ጊዜ የሚያራዝሙ እንደሚሆኑም ታምኖባቸዋል።
ከዚህ በተረፈም ሌሎች የአረንጓዴ ልማት ስራዎችን ለመስራት ወሳኝ ሚና ይጫወታሉ።እጅግ በጣም ጥሩ ማሳያዎች ናቸውና።እነዚህ ስፍራዎች ብዙ ሀብት የፈሰሰባቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የራሳቸው ድግስ አርገው ቆመው ያሰሯቸው ናቸው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በክረምቱ ወቅት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በመገኘት ችግኞችን ተከለዋል። በዚህ የበጋ ወቅት ደግሞ በአዲስ አበባ የተለያዩ ጊዜያት ምሽት ላይ እየወጡ ችግኞችን ሲያጠጡ መገናኛ ብዙሃን አመልክተውናል።
እኛ ግን በተለይም የአረንጓዴ ስፍራውን የሚመሩ በየደረጃው የሚገኙ አካላት ከእነዚህ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ወርቃማ ስራዎች ቅንጣቷን እንኳ ወስደን ዘላቂነት ባለው መልኩ መተግበር የቻልን አይመስለኝም።
የመንግስት ባለስልጣናት በተለይ በተለይ በከተማ አስተዳደር በክፍለ ከተማና በወረዳ ደረጃ ያሉ አመራሮች ይህን አርአያነት ያለው ተግባር ለማውረድ እየተጋችሁ እንዳልሆነ ይታየኛል፡፡
አረንጓዴ ስፍራዎቻችን ገና የበጋ ወቅት እየገባ ባለበት ሁኔታ መደንገጣቸው ሁላችንም ሃላፊነታችንን እየተወጣን ላለመሆኑ ማሳያዎች ናቸው። በመግቢያዬ ላይ እንደጠቀስኩት የከተማችን አረንጓዴ ስፍራዎች የኛን ክትትል እየፈለጉ ናቸው፤ እንክብካቤያችንን እየጠየቁ ናቸው። ላለፉት ወራት የአይን ማረፊያ ሆነው የቆዩት አረንጓዴ ስፍራዎቻችን እየገረጡ ናቸው።ምክንያቱ ውሃ እንዲያገኙ አለመደረጉ ላይ ነው፡፡
እነዚህ ስፍራዎች በዚህ አይነት ሁኔታ ውሃ ሳያገኙ የሚቆዩ ከሆነ በሚቀጥለው ክረምት እነሱን መንጥረን ሌሎች ችግኞችን ለመትከል እንገደዳለን። አይጠፉም ዝናብ ሲጥል ይነሳሉ ተብሎ ታስቦ ከሆነ እኛ የተከልናቸው የደን ውጤቶችን ለማልማት አይደለም፤ አካባቢያችንን ነፋሻ እንዲያደርጉልን፣ እንዲያስውቡልንና ለአይን ማረፊያ እንዲሆኑን ብለን ነው።
የገረጣ ወይም ሊደርቅ የተቃረበ የአረንጓዴ ስፍራ ምንም አያደርግልንም። ስሙን ሁሉ ልናስቀየር እንገደዳለን። አረንጓዴ ስፍራው አረንጓዴ ካልሆነ ለምን አረንጓዴ ስፍራ ይባላል፡፡
ለክረምት እና ለዝናብ ወቅት ብቻ አረንጓዴ እንድንሆንባቸው ታስቦ ከሆነ ለምን ደከምን፤ ሙጃ አለልን አይደል፤ ክረምት ሲመጣ የሚበቅል ክረምት ሲወጣ የሚደርቅ ሙጃ ነው። ልንዋብባቸው አየር ልንቀይርባቸው የተከልናቸው እንደመሆናቸው ሁሌም እንክብካቤ ልናደርግላቸው ይገባል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሁሉም እርከኖች ለእዚህ ስራ ትኩረት መስጠት አለባቸው። እነዚህ አረንጓዴ ስፍራዎች አረንጓዴ ሆነው እንዲዘልቁ በጀት የመመደብ ሰራተኛ የማሰማራት ሃላፊነት አለባቸው። ይህን ማድረግ የማይችሉ ከሆነም ስፍራዎቹን ሊንከባከቡ የሚችሉ ባለሀብቶችንና ተቋማትን ማስተባበር ይጠበቅባቸዋል።
ከተማ አስተዳደሩ አረንጓዴ ስፍራዎችን በመንከባከብ በኩል አቅሙን እያጎለበተ መሄድ ይኖርበታል። እነዚህ ስፍራዎች የከተማ ውበት ንጽህና መገለጫ እንዲሁም የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከልና በመላመድ በኩል ሚናቸው ከፍተኛ እንደመሆኑ ስፍራዎቹ ውሃ የሚያገኙበትን ሁኔታ መፍጠር ሰራተኞችን ማሰማራት የሚያነጋግር አይደለም፡፡
በቂ ቦቴዎችን ማዘጋጀት ፣ሰፍራዎቹ አካባቢ የቧንቧ ውሃ በማስገባት ሮቶ አዘጋጅቶ ውሃ በማዘጋጀት ውሃ የሚያገኙበትን ሁኔታ ለማመቻቸት ጊዜ መውሰድ የለበትም። ከተማ አስተዳደሩ አደባባዮችን ራሱ ይዞ መስራትም ይኖርበታል። በቃ ስራ ነው።እነዚህን ቦታዎች ሸፋፍኖ ማለፍ አይቻልም፤ አደባባይ ናቸው። መፍትሄው መንከባከብ ብቻ ነው፡፡
በአንዳንድ አካባቢዎች እየተካሄደ ያለውን ከባለሀብቶችና ከተቋማት ጋር አብሮ የአረንጓዴ ስፍራን የመንከባከብ ስራ አሁንም ማጠናከር ይገባል።ከእዚህ አካላት ጋር እስከ አሁን የተሰሩ ስራዎች በተወሰነ መልኩም ቢሆን ለውጦች አምጥተዋል። የሜክሲኮ አደባባይ አረንጓዴ ስፍራ ለእዚህ በምሳሌነት ሊጠቀስ ይችላል።
ተሞክሮውንም ወደ ተለያዩ አካባቢዎች እያሰፉ መሄድ ያስፈልጋል። በዚህ ላይ በመመስረት መስራት እንደ እኔ እንደ እኔ ጉዳት እየደረሰባቸው የሚገኙትን የአረንጓዴ ስፍራዎች ለመታደግ ያስችላል፡፡
ህብረተሰቡ እና ሌሎች ተቋማት አረንጓዴ ስፍራዎችን ተቀናጅተውም ይሁን በየግላቸው የሚንከባከቡባቸው ሁኔታዎችም መፍጠር አለባቸው። ለምን ሞግዚት አይደረግላቸውም። በአንዳንድ የኮንደሚኒየም መንደሮች ግለሰቦች በሚገርም መልኩ አረንጓዴ ስፍራዎችን ፈጥረው በሚገባ እየተንከባከቡ ይገኛሉ። ይህም ግለሰቦች ሳይቀሩ የአረንጓዴ ስፍራዎቹን ለመንከባከብ እንደማያንሱ ያስገነዝባል፡፡
የአረንጓዴ አካባቢ ልማቱ ክረምት ላይ ብቻ የተወሰነ እንዳልሆነ ይታወቅ። በክረምት አረንጓዴ ለብሰን በበጋ ለምን እናወልቃለን። ሁሌም በትኩረት ካልሰራን ክረምትም ባንሰራ ይሻላል። በክረምት ብቻ አረንጓዴ ለመልበስ ሙጃ ይበቃ አይደል!
አዲስ ዘመን ታህሳስ 25/2013