አሸባሪው አል-ሸባብ ሰሞኑን በኬንያ ዋና ከተማ ናይሮቢ ውስጥ በሚገኝ አንድ ሆቴል ላይ በፈፀመው ጥቃት 21 ሰዎች ተገድለዋል፡፡ የኬንያ ቀይ መስቀል ማኅበር የሟቾች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ትንበያውን አስቀምጧል፡፡ የቡድኑ ታጣቂዎች በሆቴሉ ላይ ጥቃት ከፈጸሙ በኋላ ከ700 በላይ ሰዎችን ማትረፍ የተቻለ ሲሆን፤ ሁሉም ጥቃት አድራሾች በኬንያ የፀጥታ ኃይሎች እንደተገደሉም ተነግሯል፡፡ ጥቃቱ እንዲፈፀም ያመቻቹ ሁለት ግለሰቦችም በቁጥጥር ስር ውለዋል ተብሏል፡፡ ከሟቾቹ መካከል አስራ ስድስቱ ኬንያውያን ሲሆኑ አንድ አሜሪካዊ፣ አንድ ብሪታኒያዊ እንዲሁም ሦስቱ ዜግነታቸው ያልተገለፀ የአፍሪካ ዝርያ ያላቸው ሰዎች እንደሆኑ ተዘግቧል፡፡
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት በጥቃቱ አንድ አሜሪካዊ እንደተገደለ አረጋግጧል፡፡ የሟቹን ማንነት ከመግለፅ ግን ተቆጥቧል፡፡ በኬንያ የሚገኘው የብሪታኒያ ኤምባሲም በጥቃቱ አንድ ብሪታኒያዊ እንደተገደለ አሳውቋል፡፡
የአልቃይዳ የምሥራቅ አፍሪካ ክንፍ ነው የሚባለው አል-ሸባብ ጥቃቱን የፈፀምኩት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እየሩሳሌም የእስራኤል ዋና ከተማ ናት ብለው እውቅና በመስጠታቸው እንደሆነ ገልጿል፡፡ ጥቃቱ የተፈፀመውም አንድ የኬንያ ፍርድ ቤት እ.አ.አ በ2013 በዌስትጌት የገበያ ማዕከል ከተፈፀመ ጥቃት ጋር በተያያዘ የተጠረጠሩ ሦስት ግለሰቦች ክሳቸውን እንዲከላከሉ ብይን ከሰጠ ከአንድ ቀን በኋላ እንዲሁም የሰሞኑ ጥቃት አልሸባብ ሶማሊያ ውስጥ በሚገኘው የኬንያ ጦር ሰፈር ላይ ጥቃት ፈፅሞ በርካታ የኬንያ ወታደሮችን በገደለ ልክ በሦስተኛ ዓመቱ ነው፡፡
በጥቃቱ 21 ሰዎች ተገድለዋል ቢባልም አል-ሸባብ ግን 47 ሰዎች እንደተገደሉ በወታደራዊ ዘመቻ ቃል አቀባዩ አብዱልአዚዝ አቡ ሙሳብ በኩል ገልጿል፡፡ ቃል አቀባዩ የቡድኑ ታጣቂዎች የሆቴሉን ሕንፃ እንደተቆጣጠሩትና በርካታ ‹‹ጠላቶቻቸው›› ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን ለአልጀዚራ ተናግሯል፡፡ የኬንያ ፖሊስ ኃይል ዋና አዛዥ ጆሴፍ ቦይኔት ጥቃቱ የተጀመረው ከአንድ ባንክ ፊት ለፊት የቆሙ ሦስት ተሸከርካሪዎችን በማቃጠልና በአጥፍቶ ጠፊ ጥቃት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የኬንያ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የአገሪቱ ፀጥታ ኃይሎች ጥቃቱ በተፈጸመበት ሆቴል ውስጥ የነበሩ ሰዎችን የማስወጣትና በጥቃት ፈፃሚዎቹ ላይ እርምጃ የመውሰዱ ዘመቻ መጠናቀቅን አስመልክቶ ባደረጉት የቴሌቪዥን ንግግር፣ በጥቃቱ ማዘናቸውን ገልጸው ለሞቱት ቤተሰቦች መጽናናትንና ለተጎዱት ደግሞ ማገገምን ተመኝተዋል፡፡ ጥቃቱ እንዲፈጸም ያመቻቹና የገንዘብ ድጋፍ ያደረጉ አካላት ሁሉ የእጃቸውን እንደሚያገኙም ተናግረዋል፡፡
የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ሙሳ ፋቂ ማሃማት ጥቃቱን አውግዘው የኬንያ የፀጥታ ኃይሎች የሰጡትን ምላሽም አድንቀዋል፡፡ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬስ በበኩላቸው ድርጊቱን ‹‹የጭካኔና ሽብር ተግባር›› በማለት ኮንነውታል፡፡
ምሥራቅ አፍሪካዊቷ ኬንያ ወታደሮቿን ሶማሊያ ውስጥ ማስፈሯ ለአል-ሸባብ ተደጋጋሚ የጥቃት በትር እንደዳረጋት ይነገራል፡፡ ኬን ወታደሮቿን ሶማሊያ ውስጥ ካስገባችበት ከጥቅምት 2004 ዓ.ም ጀምሮ አል-ሸባብ በኬንያ ላይ ጥቃቶችን ሲፈፅም ቆይቷል፡፡ በደቡባዊ ሶማሊያ የሰፈሩት የኬንያ ወታደሮች ወደ ሶማሊያ የገቡት ኬንያ ከሶማሊያ ጋር በምትዋሰንበት ድንበር አካባቢ የፀጥታ ቀጣና ለመፍጠር ቢሆንም በአሁኑ ወቅት በሶማሊያ የሚገኘው የአፍሪካ ኅብረት ሰላም አስከባሪ ኃይል አካል ሆነው ከአሸባሪው ቡድን ጋር እየተፋለሙ ይገኛሉ፡፡
አል-ሸባብ ኬንያ ውስጥ ጥቃት ሲፈፅም የሰሞኑ የመጀመሪያው አይደለም፡፡ ከ2007 ዓ.ም ጀምሮ ኬንያን በተደጋጋሚ ጥቃቶቹ ጎብኝቷታል፡፡ ቡድኑ በመስከረም ወር 2006 ናይሮቢ ውስጥ በሚገኘው በዌስትጌት የገበያ ማዕከል ላይ በፈጸመውና ከሦስት ቀናት በላይ በቆየው ጥቃት 67 ሰዎች ተገድለዋል፡፡ ጥቃቱም የኬንያ መንግሥትን የፀጥታ መዋቅሩ ደካማ ነው ተብሎ ከዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድ ከፍተኛ ወቀሳ እንዲገጥመው አድርጎ ነበር፡፡ በኅዳር ወር 2007 ዓ.ም ማንዴራ በተባለ አካባቢ አንድ አውቶብስ አግቶ 28 ሰዎችን ገድሏል፡፡ በሚያዚያ 2007 ዓ.ም ደግሞ ምስራቃዊ ኬንያ ውስጥ በሚገኘው ጋሪሳ ዩኒቨርሲቲ ላይ በፈፀመው ጥቃት 148 ሰዎች ሕይወታቸው አልፏል፡፡ ከሟቾቹም መካከል አብዛኞቹ ተማሪዎች እንደነበሩ ይታወሳል፡፡ ከዚህ ባሻገርም ቡድኑ በጥር ወር 2008 ዓ.ም በኬንያ ወታደሮች በሚመራ የአፍሪካ ኅብረት የሰላም አስከባሪ ጣቢያ ላይ በፈፀመው ጥቃት በርካታ የኬንያ ወታደሮች መገደላቸው የሚታወስ ነው፡፡
አል-ሸባብ ባለፉት አራት ዓመታት ጥር ወርን እየጠበቀ ሦስት የሽብር ጥቃቶችን በኬንያ ዜጎችና ወታደሮች ላይ ፈፅሟል፡፡ ከነዚህ ጥቃቶች መካከል ሁለቱ ሶማሊያ ውስጥ በሚገኘው የኬንያ ጦር ላይ የተሰነዘሩ ሲሆኑ አንዱ ደግሞ ሰሞኑን የተፈፀመው ጥቃት ነው፡፡
ፓትሪክ ጋታራ የተባሉ ጸሐፊ ኬንያ ድንበሯን ከአል-ሸባብ ሰርጎ ገቦች ለመከላከል በማሰብ ወታደሮቿን ወደሶማሊያ መላኳ ኬንያውያን የአል-ሸባብ የበቀል በትር ሰለባ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል ይላሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የኬንያ የጸጥታ ኃይሎች የአል-ሸባብን ጥቃት ማስቆም ባለመቻላቸው ለደህንነታቸው ዋስትና እንዳጡም ይገልፃሉ፡፡ የፀጥታ ኃይሎች ለሰሞኑ ጥቃት የሰጡት ምላሽ በመስከረም ወር 2006 ዓ.ም በዌስትጌት የገበያ ማዕከል ከነበረው የተሻለ ቢሆንም አሁንም በአገሪቱ የጸጥታ ኃይል መዋቅርና በፀረ-ሽብር ስትራቴጂ ላይ የሚነሱ በርካታ ጥያቄዎች እንዳሉ ያስረዳሉ፡፡ እርሳቸው እንደሚሉት፣ የጸጥታ ኃይሎች የሽብር ጥቃቶች ከተፈጸሙ በኋላ ጥቃቶቹ የተመከቱባቸው መንገዶች ላይ ምንም ዓይነት ግምገማ አያካሂዱም፡፡ ለአብነት ያህልም አንድ የአገሪቱ ፖሊስ ባልደረባ ከዌስትጌት ጥቃት በኋላ ፖሊስ ጥቃቱን እንዴት እንደተቆጣጠረው የሚገመግም ውይይት ባለመካሄዱ ካለፉት ጥቃቶች መማር እንዳልተቻለ ለ‹‹ዴይሊ ኔሽን (Daily Nation)›› ጋዜጣ የሰጡትን ማብራሪያ በማሳያነት ይጠቅሳሉ፡፡
‹‹በቀጣዮቹ ሳምንታት ኬንያውያን ስለአገራቸው የፀጥታ ኃይል መዋቅርና በሶማሊያ ስለሚገኘው የኬንያ ጦር ጉዳይ በተመለከተ የፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ መንግሥትን መጠየቃቸው አይቀርም›› የሚሉት ጋታራ፣ የአገሪቱ መንግሥት ጠንካራ እርምጃ መውሰድ ካልቻለ ኬንያውያን የአል-ሸባብ ቂም መወጫ መሆናቸው የሚያበቃበት ቀን ሩቅ እንደሚሆን ይናገራሉ፡፡
የሰሞኑን ጥቃት ተከትሎም በኬንያ የፀጥታ ኃይሎች ላይ የሚሰነዘሩ ወቀሳዎች በድጋሜ መነሳታቸውን ቀጥለዋል፡፡ መሐል ናይሮቢ ውስጥ በጠራራ ጸሐይ ተደጋጋሚ ጥቃቶች የመፈፀማቸው ምስጢር ብዙዎችን እያነጋገረ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የተቃዋሚ መሪ ራይላ ኦዲንጋ እና አንዳንድ የአገሪቱ ምክር ቤት አባላት ደጋግመው ሲጠይቁት የነበረው በሶማሊያ ያለው የኬንያ ጦር ይውጣ ጥያቄ ወደ ንግግር መድረኩ ተመልሶ መጥቷል፡፡ በሚያዚያ ወር 2008 ዓ.ም የተሰበሰበ የሕዝብ አስተያየት እንደሚያሳየው አብላጫ ኬንያውያን ጦሩ ከሶማሊያ እንዲወጣ ፍላጎት አላቸው፡፡ ይሁን እንጂ ፕሬዝዳንት ኬንያታ ግን ሶማሊያ ውስጥ የሚገኘው የኬንያ ጦር ወደ አገሩ የሚመለሰው ሶማሊያ ውስጥ አስተማማኝ ሰላምና መረጋጋት ሲሰፍን እንደሆነ በተደጋጋሚ ሲናገሩ ቆይተዋል፡፡
በሙሉ ስሙ ‹‹ሃረካት አል-ሸባብ አልሙጃሂዲን (Harakat al-Shabaab al-Mujahideen)›› በመባል የሚጠራውና የአልቃይዳ የምስራቅ አፍሪካ ክንፍ እንደሆነ የሚነገርለት አል-ሸባብ፣ ከሰባት ሺ እስከ ዘጠኝ ሺ የሚገመቱ ተዋጊዎች ያሉት ሲሆን፤ ሶማሊያን ጨምሮ በየመን፣ በታንዛኒያ፣ በኬንያና በሞዛምቢክ እንደሚንቀሳቀስ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ቡድኑ በአሜሪካ ጦር የአየር ድብደባና በአፍሪካ ኅብረት ሰላም አስከባሪ ኃይል ጥቃት በርካታ ይዞታዎቹን ቢነጠቅም አሁንም በርካታ የሶማሊያ ገጠራማ ቦታዎችን ተቆጣጥሮ ይገኛል፡፡
አዲስ ዘመን ጥር 10/2011
አንተነህ ቸሬ