አብዛኛው ህዝብ ከእጅ ወደ አፍ በሆነ የህይወት እርከን ውስጥ ይገኛል። የኑሮን ክብደት መቋቋም አቅቶት የሚንገዳገደውም ጥቂት የሚባል አይደለም። ዘመን መልካም እድል የፈጠረላቸው ኑሮን እንዳሻቸው የሚመሩ፣ ሙቅ ማኘክ የሚቀራቸው በአንድ በኩል ፣ ጥቂት ናቸው እንጂ ችግርን ለአንዴም ቢሆን አይተውት የማያውቁ ቤቶችና ቤተሰቦች በሌላ በኩል ይገኛሉ።
የዚያ መንደር ነዋሪዎች በጠንካራ ማህበራዊ ግንኙነታቸውና መረዳዳታቸው ይታወቃሉ። እንደ ቀደሙት ትውልዶች ሁሉ ሰርግና ምላሽን፣ ለቅሶና ተስካርን ግለሰባዊ ሳይሆን ማህበራዊ አድርገው ይኖራሉ። በጋራ እየሰሩ በህብረት ቆመው እየተቋደሱ ያከናውኑታል። የሚያስቀና አንድነትና ጥሩ ቤተሰባዊ ትስስር የአካባቢው ነዋሪዎች መለያ ነው።
በእዚሁ መንደር ልጅ መውለድ የአንድ ሰው ቢሆንም፣ ማሳደጉ ግን የሁሉም የአካባቢው ሰዎች ኃላፊነት ሆኖ ኖሯል። እኔ ምን አገባኝ በሰው ልጅ ብሎ ነገር የለም። ወላጅ ሆኖ ተንከባክቦና ሲያጠፋም ገስፆ በፍቅር ማሳደግ የአካባቢው ወግና ልማድ ነው።
በአንጻሩ የዚሁ መንደር ነዋሪዎች ሆነው በማህበራዊ ኑሮው ላይ የማይሳተፉ ማህበራዊ ግንኙነት ምን እንደሆነ ያላዩም ይገኛሉ። ልጆቻቸውን በአንድ ግቢ ውስጥ ወስነው ወጣ ብሎ ከሌሎች ልጆች ጋር መጫወትን እንዳያዩ አርገው ዘግተው ያሳደጉም አሉ።
የአቶ በላቸው ግቢ ይህን ከመሰሉት ግቢዎች መካከል ይጠቀሳል። የባለ ፀጋው የአቶ በላቸው ዋናው በር ከወትሮ በተለየ በሰፊው ተከፍቷል። ከውስጥ የተለያዩ ጣዕመ ዜማዎች ይሰማሉ። ”ተጫወቱ ኦሆ ተጫወቱ ገና ነው ሰዓቱ..” የሰርግ ዜማ። የግቢው በር በተለያዩ ማስጌጫዎችና አበቦች ተንቆጥቁጦ እንኳን ደስ ያላችሁ! እንኳን ለዚህ አበቃችሁ! መልካም ጋብቻ! የሚሉ ፅሁፎች ተለጥፈውበታል።
ከግቢው በር ወደ ውስጥ ገባ ብሎ በተንጣለለው ሌላ ግቢ ላይ ነጭ ድንኳን ተጥሏል፤ ድንኳኑ በተዋቡ ወንበሮችና በባለ ቀለም ማስጌጫዎች ተውቧል። ከድንኳኑ ፊት ለፊት ከፍ ተደርጎ መድረክ ታንጸዋል። መድረኩ በተለያዩ ባለቀለም መብራቶችና የሚያብረቀርቁ ማስዋቢያዎች ጠርዝ ጠርዙ ተጊጧል። የሚያማመሩት የሚዜ ወንበሮች በግራና በቀኝ ተሰልፈው መሀል ላይ ያሉትን የሙሽሮቹን ወንበሮች ይበልጥ የተዋቡ እንዲሆኑ አድርገውታል።
ከግቢው አንደኛው ጥግ በርካታ ሴቶችና ወንዶች እንግዶችን ለመቀበል በሚያማምሩ አልባሳት ተውበው ይጠባበቃሉ። እጅግ የተዋበ የባለ ፀጋ ግቢ ነው። እንደ ሌላው ቤት ድግስ አለ ተብሎ ወጥ አልተሰራም፣እንግዶች ሲለሚመጡ ተብሎ በሬ አልተጣለም። እዚያ ቤት ላይ የሚሸትና የሚቁላላ ወጥ ከቶም የለም። እዚያ ግቢ ላይ የሚላጥና የሚከተፍ ሽንኩርት፣ የሚጋገር እንጀራም የለም። ሁሉም ከውጪ በተለየ ትዕዛዝ ተሰናድቷል።
አቶ በላቸው የመጀመሪያ ልጃቸውን ከሰዓታት በኋላ ሊድሩ ሽር ጉድ እያሉ ናቸው። ሱፋቸውን ለብሰው በቄንጥ አንዴ ወደ ሰርጉ አዳራሽ ይገባሉ፤ ሌላ ጊዜ ከውጭ በልዩ ትዕዛዝ ተሰርቶ የመጣውን ምግብ ይቃኛሉ፤ ከአስተናጋጆች ጋር ይነጋገራሉ።
በሩ ላይ የደንብ ልብስ የለበሰ ጥበቃ ቁሟል። ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በሙሉ ልብስ እና ከረቫት አምረው፣ የሀገር ባህል አልባሳትን ተጎናፅፈው ይገባሉ። በቄንጠኛ አለባበስ አምረው በውብ መኪኖቻቸው ወደ ግቢው ቀረብ እያሉ ወርደው ተያይዘው ወደ ውስጥ የሚገቡም አሉ።
አቶ በላቸውም ለሁሉም ሞቅ ያለ አቀባበል እያደረጉ ናቸው፤ በተለይ ጥንድ ጥንድ ሆነው የሚመጡትን እጅ እየነሱ ይቀበሏቸዋል።
በሰርግ ስነ ስርዓት ላይ በአብዛኛው የሚገኙት በተለያየ ቦታ የሚኖሩ የአቶ በላቸው ወዳጅ ዘመዶች ናቸው። ከሚኖሩበት አካባቢ ማህበረሰብ ጋር ብዙም ግንኙነት የሌላቸው አቶ በላቸው ልጃቸውን ለመዳር ሲያስቡ ለእኔ ምቀኛ ናቸው ብለው የሚያስቡዋቸውን በአቅራቢያቸው ያሉ ጎረቤቶቻቸው ለማስተባበር ያቀረቡትን ጥያቄ አልተቀበሉትም።
ሁሉም ነገር ገንዘብ ካለ ይቻላል የሚሉት አቶ በላቸው፣ አጎራባቾቻቸውን ማቅረብ አይደለም በደንብም አያውቋቸውም። እዚያ መንደር ላይ ለረጅም ዓመታት ቢቆዩም ማህበራዊ ግንኙነታቸው ግን ልል ነው። ሰዎችን ማቅረብ፣ ከጎረቤቶቻቸው ጋር መልካም የተባለ ግንኙነቶችን መፍጠር የሚለውን አስበውት አያውቁም። እንዲያውም የእርሳቸው ጠላቶች የተሻለ ህይወት መኖራቸውን የማይፈልጉ ይመስላቸዋል። በተደጋጋሚ ሊቀርቡዋቸው የሞከሩ ጎረቤቶቻቸውን ከመወዳጀት ይልቅ ማራቅን ይመርጣሉ።
አቶ በልሁ አይቼው የአቶ በላቸው ጎረቤት ናቸው። ሶስት ጎረምሳ ልጆች አሉዋቸው። በአካባቢው በመልካም ባህሪያቸው የተወደዱ ናቸው፤ ለሰዎች በጎ በመዋል ይታወቃሉ። እርግጥ የተመቻቸ ህይወት፣ የተደላደለ ኑሮ የላቸውም።
አቶ በላቸው ከአካባቢው ሰዎች ይበልጥ የሚያውቋቸው ከቤታቸው ፊት ለፊት ያሉትን አቶ በልሁን ብቻ ነው። በአካል አግኝተው “እሁድ እንድትገኝ” ሲሉ ጥሪ ያቀረቡላቸውም ለእሳቸው ብቻ ነው። አቶ በልሁም በክብር ግብዣውን ተቀብለዋል።
አቶ በልሁ ከቀናት በፊት ጎረቤቶቻቸውን በማስተባበር በባህልና በወጉ መሰረት ስራ ለማገዝ ሞክረው ነበር። ጎረቤቶቻቸውም በተናጠል ስራ ካለ እናግዝ ብለው ጠይቀዋቸዋል። አቶ በላቸው ግን የጎረቤቶቻቸውን ጥያቄ አልወደዱትም። ድግሱ ዝግጅት ላይ እንሳተፍ ማለታቸውንም አልወደዱላቸውም ። የልጃቸውን ሰርግ ሊያበላሹ የመጡ ያህል በመቁጠር ለጥያቄያቸው ትኩረት በመንፈግ ፊት ነስተዋቸዋል። ጎረቤቶችም የአቶ በላቸው ሁኔታ አናዷቸው ጉድ ብለው ወደ ቤታቸው ተመልሰዋል።
አቶ በላቸው ጎረቤቶቻቸውን ለዝግጅቱ ባይፈልጓቸውም ድግሳቸው ላይ ግን ሁሉም የአካባቢው ሰው እንዲገኝ ጥሪ አድርገዋል። ጥሪ ያደረጉት አንድም የልጃቸው ሰርግ አጃቢው እንዲበዛ አስበው አንጂ ጉርብትናቸውን ለማጠንከር ማህበራዊ ግንኙነታቸውን ለማደርጀት ብለው አይደለም።
ከሰዓት ቆይታ በኋላ ግቢው እየሞቀና እየደመቀ ሄደ። ለሰርጉ የተጠራው ሰው ሁሉ መምጣትና አዳራሹ መሙላት ጀመረ። የሙሽሮች መምጫ ሰዓት ከመድረሱ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት የበዓሉ ታዳሚዎች ቦታ ቦታቸውን ይዘው መጠባበቅ ጀመሩ።
በህዝቡ መሀል ጎምለል ጎምለል እያሉ ታዳሚውን የሚያዩት አቶ በላቸው በድግሳቸው ላይ ከተጠሩት ውስጥ እጅግ በጣም ጥቂት ጎረቤቶቻቸው ብቻ መገኘታቸውን ተመለከቱ። “እንዴት ቢንቁኝ ነው ጎረቤቶቼ ጠርቻቸው ያልመጡት ሲሉ ራሳቸውን ጠየቁ። በአካል ተገኝተው የጠሯቸው አቶ በልሁ አለመኖራቸውን ሲመለከቱም ይበልጥ ተናደዱ። ክፉ ነገር ታሰባቸው። “አላልኩም፤ ድሮም ጎረቤት ምቀኛ ነው…ና ብዬ የጠራሁት እኔው ነኝ፤ እንዴት በደስታዬ ቀን ይቀራል። ” ሲሉ በንዴት መጦፍ ውስጥ ገቡ። ክብራቸው የጎደለ የተናቁ መሰላቸው።
ሙሽሮች ተስተናግደው ሰርገኛው ተሸኝቶ እጅግ በደመቀ መልኩ የሰርጉ ዝግጅት እስኪጠናቀቅ የጎረቤቶቻቸው አለመገኘት አቶ በላቸውን አብከነከናቸው፤ ቂም ቋጥረውብኛል ሲሉ ማሰብ ጀመሩ። በተለይ የአቶ በልሁ አለመገኘት አበሳጫቸው።
እንግዳ ተሸኝቶ ነገሮች ሲረጋጉ አንድ ድምፅ ከጎረቤት ጎልቶ መሰማት ጀመረ። የለቅሶ ድምፅ ፤ ምን እንደሆነ ለማጣራት አቶ በላቸው ከፎቅ ላይ ወጥተው ሲመለከቱ የለቅሶው ድምፅ አቶ በልሁ ግቢ መሆኑን ተመለከቱ።
ምንነቱን ለማጣራት ታች ወረዱና ወደ ግቢያቸው አጥር ጠጋ ብለው ጥበቃቸውን ጠሩ። “አንተ ና ወዲህ..ምንድነው እዚያኛው ግቢ የሚነፋረቁት ሲሉ ጠየቁት። ደስታችንን በወጉ ሳናጣጥም ለማበላሸት ነው ይህን የሚያደርጉት፤ምንድነው የሚያለቅሱብን? ሲሉ ተናገሩ።
ጥበቃውም ፈጠን ብሎ እያለቀሰ “ እንደዚያ አይደለም አለቃ፤ እዚያ ቤት ለቅሶ ገጥሟቸው ነው። የአቶ በልሁ ባለቤት ሞተው ነው… ትናንት ማታ ነው የሞቱት አሉ ሲል ገለጸላቸው። የዚህን ሰርግ ድባብና የሰርገኛውን ደስታ ላለመንጠቅ በሚል ድምፅ ሳያወጡ እያለቀሱ ነው የቆዩት። ” በማለት አብራራላቸው።
“ለሰርግ የተጠራውም ጎረቤት እዚያ ተሰብስቦ ነው የዋለው። በፊት ለፉት በሩን የዘጉትም እዚህ ያለው ስነስርዓት አንዳይታወክ አስበው ነው ጌታው። ” ብሎ ቀና ሲል አቶ በላቸው ያለወትሯቸው ፊታቸው በሀዘን ሲሞላ ተመለከተ። ተፈፀመ።
ተገኝ ብሩ
አዲስ ዘመን ነሃሴ 21/2013