
እየተጠናቀቀ ባለው ግንቦት ወር አያሌ ሊታወሱ የሚገባቸው ታሪኮች ተከስተዋል፡፡ የተወሰኑትንም በዚህ የሳምንቱ በታሪክ አምዳችን ይዘን በመቅረብ ታሪካቸውን ልናጋራችሁ ሞክረናል፡፡ ለዛሬ ደግሞ ከታሪካዊ ክስተቶች መካከል አንዱ ወደ ሆነውና በ18ተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ወደ ተፈጸመው ልንመልሳችሁ ወደናል።
በዘመኑ በኢትዮጵያ ውስጥ ትልቅ ስፍራ ይዛ የምትወሳውን እቴጌ ምንትዋብና የኢትዮጵያ ታሪክ ትውስታዎችን እንቃኛለን። መልካም ምልሰት።
እቴጌ ምንትዋብ
እቴጌ ምንትዋብ በዙፋን ስሟ ብርሃን ሞገስ በ1698 ዓ.ም. ከአባቷ ደጅ አዝማች መንበር እና እናቷ ልዕልት እንኮይ በቋራ፣ ጎንደር ነው የተወለደችው፡፡ እናቷ ልዕልት እንኮይ ከዓፄ ሚናስ ዘር እንደምትወለድ ይጠቀሳል።
ምንትዋብ በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያ ላይ ብዙ አሻራ ትታ ያለፈች ንቁ፣ ሃይለኛና ተራማጅ መሪ ነበረች። ከባለቤቷ ዓፄ በካፋ ዘመን ጀምሮ እስከ ልጇ ዳግማዊ ዓፄ ኢያሱ እና የልጅ ልጇ ዓፄ እዮዋስ ዘመን ድረስ ለ40 አመታት የአገሪቱ እኩል መሪ ነበረች ።
በዚህች መሪ ዘመን በኢትዮጵያ ውስጥ ትልቅ የህንጻዎች ግንባታና የቤተክርስቲያን የስነ ጽሁፍ ስራ እንዲሁም የስነ ጥበብ እድገት ታይቷል። የፋሲል ግቢን የመጨረሻ ግንብ ያስገነባችው ምንትዋብ ነበረች። ከልጆቿ የእድሜ አናሳነትና እራሷም በሰራቻቸው አንዳንድ ስህተቶች ምክንያት በስልጣን በነበረችበት ዘመን የነበረው እድገትና ሰላም እርሷ ስታልፍ አብሮ አልፏል። አገሪቱም ወደ ዘመነ መሳፍንት የተሻገረችው ልክ እርሷ እንዳለፈች ነው።
እቴጌ ምንትዋብ ከዐፄ በካፋ ጋር የተቀራረበችው በተለየ አጋጣሚ ነበር። ዐፄ በካፋ በህዝብ ዘንድ ክብርን ካስገኘለት ስራው አንዱ ብዙ ጊዜውን በመሰዋት፣ ራሱን ደብቆ በግዛቱ ሁሉ እየተዘዋወረ የተሰራውን ስህተት ማቃናቱ ነበር። በዚህ ሁኔታ አንድ ቀን ተደብቆ ከጣና ሃይቅ በስተ ምዕራብ ሲጓዝ ቋራ ላይ ወባ ታመመና ከአንድ ገበሬ ቤት አረፈ። በካፋ ታሞ ያረፈበት ቤት ባለቤት ልጅ ነበረች። ምንትዋብ ታማሚውን ንጉሥ ተንከባክባ ለጤንነት ስላበቃችው ጳጉሜ 5፣ 1716 (እ.ኤ.አ) ላይ ወደ ጎንደር ከተማ እንዳስመጣትና እንዳገባት የስኮትላንዱ ተጓዥ ሐኪም ይጋቤ ሲተርክ ይገልጻል። የስኮትላንዱ ተጓዥ ሐኪም “ወጣቷ ምንትዋብ ከመጠን በላይ ቆንጆ፣ ተግባቢና ልዝብ” ነበረች ሲል ይገልጻል፡፡
እቴጌ ምንትዋብ በ1717 ዳግማዊ አጼ ኢያሱን ወለደች። ከዚህ በኋላ ለ2 አመት ጎንደር ከተማ ተቀምጣ በመካከሉ በ1718 ወደ ወልቃይት እንድትሄድ ተደረገ። ምንም እንኳ ከሁለት ወር በኋላ ብትመለስም ልጇ ግን ወደ ሰሜን ሽሬ፣ ትግሬ ተልኮ በዚያ እስከ 1730 መኖር ቀጠለ።
አጼ በካፋ በ1722 ዓ.ም. ሲሞት የከተማው ህዝብ ሞቱን ሊቀበል አልቻለም። ለዚህ ምክንያቱ ከአሁን በፊት ንጉሱ ሳይሞት የሞተ በማስመሰል ህዝቡ ላይ ሽብር በመፍጠሩ ነበር። ምንትዋብም ባሏ ሲሞት የህዝቡን ጥርጣሬ በመጠቀም ውስጥ በማስገባትና ከቋራ አምስት ወንድሞቿ መጥተው የቤተመንግስት ስልጣን እስኪጨብጡና እስኪያረጋጉ ድረስ የንጉሱን ሞት ደብቃ ቆየች። ከወንድሞቿ መምጣት በኋላ እርሷና ዘመዶቿ ሆነው የ7 አመት ልጇን ኢያሱን ለማንገስ ቻሉ።
ከ2 ወር በኋላ ታህሳስ 15 ቀን 1722 ላይ የልጇን ህጻን መሆን በማስታከክ ራሷ ላይ ዘውድ በመጫን በንግሥት ሥልጣን እንደራሴነቷን አሳወጀች። ለሚቀጥሉት 40 አመታት እርሷና ወንድሟ ወልደ ልዑል ከንጉሥ ልጇና ልጅ ልጇ ጋር እኩል ተሰሚነት ኑሯቸው አገሪቱን ለማስተዳደር በቁ፡፡ በልጇና በልጅ ልጇ ዘመናት ለ40 ዓመት ስትነግስ ያከናወናቻቸው ስራዎች ብዙ ነበሩ።
እቴጌ ምንትዋብ በባህሪዋ ተራማጅና ንቁ ነበረች። በቤተክርስቲያን ተነስቶ የነበረውን የቅባት እና ተዋህዶ ክርክር ለማስታረቅ ያደረገችው ጥረት ተሳክቷል። ስለሆነም ከሞላ ጎደል በአስተዳደሯ ወቅት ሃይማኖታዊ ሰላም ነግሶ ነበር። ከሌሎች መንፈሳዊ ስራዎቿ ውስጥ ብዙ አብያተ-ክርስቲያናትንና ግንቦችን በማነጽ እንዲሁም በግሏ እየተከታተለች ድርሰቶችን በማስደረስ ስሟ ይጠቀሳል።
በተለያዩ ምክንያቶች ራሷን ከጎንደር ከተማ ለማራቅ ጥረት አድርጋለች። የዚህ ጥረት ማሳያዎች ከጎንደር ከተማ 3 ኪሎሜትር ራቅ ብሎ በሚገኘው ደብረ ፀሐይ (ቁስቋም) ያሰራቻቸው ህንጻዎች ናቸው። የስኮትላንድ ተጓዥ ጄምስ ብሩስ (ሃኪም ይጋቤ) በኒህ ህንጻዎች አንድ ክፍል ተሰጥቶት ይኖር ነበር፡፡ ስለቁስቋም ሲጽፍም 3 ፎቅ የሆነ ቤተመንግስት፣ ክብ የሆነ ቤተክርስቲያንና ብዙ የተለያዩ የሰራተኞችና ዘበኞች ቤቶች እንዲሁም ግብዣ ቤት በአንድ ማይል ርቀት ዙርያ በታጠረ ግቢ ይኖር እንደነበር አስፍሯል።
እነዚህን ቤተመንግስቶችና ቤተክርስቲያኖች ከ1723 ጀምራ በማሰራት በ1732 ነበር ያስመረቀቻቸው። በግቢው ውስጥ የሚገኘው ቤተ ክርስቲያን፣ ደብረ ፀሐይ ማርያም ይባላል። በጄምስ ብሩስ ግምት፣ ደብሩ በኢትዮጵያ ከሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ሃብታም የነበረና ብዙ ምርጥ ምስሎችና በወርቅና በብር የተሰሩ የቤተክርስቲያን መገልገያ ዕቃዎች የተሞላ ነበር። የተገነባውም በአናጢዎች መሪ በጅሮንድ ኢሳያስ እና አዛዥ ማሞ፣ አዛዥ ህርያቆሳና አዛዥ ናቡተ መሪነት ነበር። ቤተክርስቲያኑ በቀይ ሃር አሸብርቆ በዙሪያው 380 መስታወቶች ተተክለውት ብርቅርቅታው ጎንደር ከተማ ድረስ ይታይ ነበር። ቤተክርስቲያኑና ሌሎች በግቢው የነበሩ ህንጻዎች በሱዳን ወራሪ መሃዲስቶች በ1880 ተቃጠሉ። አሁን በጊቢው የሚገኘው ቤተክርስቲያን በዚህ ፍርስራሽ ላይ የተሰራ ነው።
ምንትዋብ እጅግ መንፈሳዊ ነበረች። ለዚህ ስትል ብዙ መንፈሳዊ ስራዎችን በገንዘብ ትደጉም ነበር። ብዙ መጻህፍት በዚህ ዘመን ተጽፈዋል፣ ከአረብኛም ተተርጉመው ወደ ብዙ አብያተ ክርስቲያናት የተሰራጩት መጻህፍት ብዛት ስፍር ቁጥር የለውም።
ለስነጥበብ ከነበራት ትኩረትና ከምታደርገው ድጎማ የተነሳ በዚሁ ዘመን በድንገት የተፈጠረ ልዩ አይነት የሥነ-ስዕል ስራ ተጀመረ። ይህ እንግዲህ በውጭ ሃገር የኪነ ጥበብ አጥኝዎች ዘንድ ሁለተኛው የጎንደር የስነስዕል ስልት የሚባለው ነው።
በአዲሱ ስልት ሥነ ሰዕል የቀጥተኛ መስመሮች ጥንቅር መሆኑ ቀርቶ በጎባጣ መስመሮች ጥንቅር የሚሰራና በህብረ ቀለማት የደመቀ ሆነ። እውነተኛ ሰዎችን የሚመስሉ ምስሎችም መታየት ጀመሩ። በዚህ ሁኔታ በጣና ሃይቅ ባሰራችው ናርጋ ስላሴ ቤተክርስቲያን እና በቁስቋሙ ደብረፀሐይ ማርያም ግድግዳዎች ላይ አይን የሚስቡ ምስሎች ተሰርተው ነበር። ሆኖም ብዙዎቹ በመሃዲስት ሱዳኖች ሲወድሙ ንግስቲቱ በራሷ ክትትል ያጻፈችው መጽሐፈ ራዕይ የተሰኘው በምስል ያሸበረቀ መጽሓፍ አሁን እንግሊዝ አገር ይገኛል፡፡ መጽሀፉ የአዲሱ የሥነ ሥዕል ስርዓት ቅርስ ከጥፋት ድኖ አሁን ቅርሱን መዝግቦ ይገኛል።
አጼ በካፋ ከሞቱ በኋላ ከተወሰኑ ወንዶች ጋር ለአጫጭር ጊዜያት ቅርርብ ነበራት ተብላ ትታማ ነበር። በመጨረሻ፣ ምንም እንኳ ግራዝማች እያሱን ብታገባም የአማቷ ልጅ ከመሆኑም በላይ ከእርሷ በእድሜ ስለሚያንስ “ምልምል እያሱ” በሚል የሽሙጥ ስም ይታወቅ ነበር። ከዚህ ምልምል እያሱ 3 ሴት ልጆችን አፍርታለች፤ እነርሱም ልዕልት አስቴር፣ ልዕልት ወለተ እስራኤልና ልዕልት አልጣሽ ይባሉ ነበር።
በኢትዮጵያ ታሪክ፣ በተደጋጋሚ እንደሚታየው፣ የህጻናት ስልጣን ላይ መውጣት አገሪቱን ከጥንት ጀምሮ ለውድቀት የዳረገ ነበር። የዳግማዊ አጼ ኢያሱና የልጁ የኢዮዋስ በህጻንነታቸው መንገስ ከዚሁ እውነታ የተለየ አልነበረም።
አጼ በካፋ ሲሞት ልጁ ኢያሱ መንገሱ ህጋዊ ቢሆንም ፣ህጻን ስለነበር ሃይል ለማግኘት የግዴታ ከሌላ ቦታ የፖለቲካ መሰረት ማግኘት ነበረበት። ስለሆነም እናቱ እቴጌ ምንትዋብ የምትተማመንባቸው የቋራ ዘመዶቿን በቤተ መንግስት ሾመች። ለምሳሌ፡ ወንድሟ ወልደ ልዑልን በራስ ማዕረግ ሾመች። ይህን በማድረጓም ቀደምት በጎንደር ከተማ ስልጣን የነበራቸው ባላባቶች በጣም ጠሏት።
ስለሆነም ከ1735-1736 እርሷንና ልጇን ከስልጣን ለማስወገድ ባላባቱ ሞከረው አመጹ ስለከሸፈ ይብሱኑ የቋራ ዘመዶቿን በከፍተኛ ስልጣንና በሰራዊቱ ላይ ሾመች ። ስልጣኗ እንዳይናጋ፣ የባላባቱን ኃይል በየጁዎች ሃይል ለማጣፋት በማሰብ ልጇ አጼ ኢያሱን ለየጁ ባላባት ልጅ የሆነችውን ውቢት (ክርስትና ከተነሳች በኋላወለተ ቤርሳቤሕ) ዳረች።
በጋብቻው ግን ያልተደሰቱ ነበሩ፡፡ ንጉሱ ክርስቲያን ያልሆነች የየጁ ሴት አገባ ተብሎ ይታማ ስለነበር ጋብቻው በከተማው እርሱን ያስጠላና ድብቅ እንጂ በግልጽ የሚካሄድ አልነበረም። በመካከሉ ቤርሳቤሕ ቀስ በቀስ የየጁ ዘመዶቿን ልክ ምንትዋብ የቋራ ዘመዶቿን በቤተመንግስት እንደሰገሰገች ታደርግ ነበር።
በዚህ ሁኔታ በየጁዎችና በቋራዎች የለሆሳስ ፉክክር ተጀመረ። ዳግማዊ አጼ ኢያሱ በ1747 ሲሞትና ከቤርሳቤሕ የወለደው ልጁ እዮዋስ ሲነግስ ምንትዋብ መልሳ እንደራሴነቷን አጸናች። ቤርሳቤሕ በበኩሏ ልክ ምንትዋብ የኢያሱ ሞግዚት እቴጌ እንደነበረች፣ እርሷ በተራዋ ለእዮዋስ እንደራሴነት (እቴጌነት) ይገባኛል በማለቷ በሁለቱ መካከል ጥል ተነሳ። በዚህ ወቅት አጼ እዮዋስ አያቱን ምንትዋብን ከመደገፍ ይልቅ የቤርሳቤህና የየጁዎች ወገን ሆነ። ውዝግቡ በ1759ዓ.ም. ወደ የርስ በርስ ጦርነት አመራ።
በዚህ ጦርነት፣ የየጁም ሆነ የቋራ ክፍሎች ሃይላቸው ስለተዳከመ፣ ከትግሬ ገዢ ራስ ሥዑል ሚካኤል እገዛ ፈለጉ። ሥዑል ሚካኤል መጀመሪያ የንጉሱና የየጁዎች ደጋፊ ቢሆንም፣ በምንትዋብ የዲፖሎማሲ ስራ ኋላ የእርሷ አጋር በመሆን አቋሙን ቀየረ። በስተመጨረሻ 1769 ላይ ሥዑል ሚካኤል፣ አጼ እዮዋስ የጁዎችን በጦርነት ደግፏል በሚል ክስ እንዲገደል አደረገ።
የንጉሱ መገደል በአገሪቱ ሲሰራበት የነበረውን ትውፊት የቀየረ እንግዳ ነገር ነበር። እንግዲህ እስከ ብዙ ዘመን ድረስ የነበረውን የንጉስ ክብር የነካ ስለነበር የሚፈራ አንድ ሃይል በመታጣቱ አገሪቱ ወደ ዘመነ መሳፍንት – ሁሉ በሁሉ ጦርነት ገባች። ምንትዋብ፣ ምንም እንኳ የየጁዎች ዋና ተቃዋሚ ብትሆንም፣ የልጅ ልጇን መገደልና የሥዑል ሚካኤልን መግነን በመጥላት 1762 ላይ ወደ ጎጃም ሸሽታ ከሄደች በኋላ 1763 ተመልሳ ከጎንደር 3 ኪሎ ሜትር ሰሜን-ምዕራብ በሚገኘው ቁስቋም ባሰራችው ቤተ መንግስት ኑሮ ጀመረች። ታላቋ ንግስት ምንትዋብ ግንቦት 26 በ1785 ዓ/ም አረፈች።
ምንጭ- “በእምነት ታደለ-ሸገር ብሎግ” James Bruce, Travels to Discover the Source of the Nile “ጉዞ የአባይ ወንዝ መነሻ የሆነውን ስፍራ ለማግኘት” 3rd ed, vol II, Edinburgh, 1813
ዳግም ከበደ
አዲስ ዘመን ግንቦት 29/2013