መሀሪ በየነ
ለኢትዮጵያዊ ማንነት መበረዝ መንስኤ በዋናነት የሚጠቀሰው መስፋፋትና የምዕራቡ ዓለም ስነልቦና በሳይንስና ቴክኖሎጂ አማካኝነት ተፅዕኖ እያሳደረ መገኘቱ መሆኑን የስነ ልቦና ባለሙያዎች ያስረዳሉ።
በአሁኑ ዘመን ዓለም ወደ አንድ መንደርነት እየጠበበች ነው። ይህም ለሁለንተናዊ ስልጣኔ ሲባል አዎንታዊ ምላሽ ቢኖረውም ለብዙ ሺህ ዓመታት ጎልብቶ የቆየው የኢትዮጵያውያን የማንነት ስነ-ልቦና በዘመን አመጣሽ ቴክኖሎጂዎችና ልክ በሌለው የባህል ልውውጥ ሳቢያ ማንነታችን ጥያቄ ውስጥ እንዲገባ ምክንያት እየሆነ መጥቷል።
የሳይኮሎጂ ባለሙያ የሆኑት አቶ ነጋሸ አበበ እንደሚሉት በኢትዮጵያውያን ስነ ልቦና ውስጥ የማንነት መገለጫዎች ከሆኑት መካከል ኩራትና ክብር መሰረታዊውን ስፍራ ይይዛሉ። በታሪክ፣ በቅርስ፣ በመልክአ ምድር፣ በእምነትና በመሳሰሉት ባህላዊና ታሪካዊ ዕሴቶች ላይ በብዙ ኢትዮጵያውያን ዘንድ የሚታየው ኩራትና የሚሰጠው ክብር ቀላል አይደለም።
ስለክብር ስናወራ በተለምዶ “የአቶ እከሌ ልጅ” መባል ትልቅ ቦታ አለው። ክብርን መስጠትም ሆነ መንፈግ፣ በርስ በርስ ግንኙነታችን ውስጥ ቁልፍ ስፍራ አለው። አንድን ሰው “ሰው አክባሪ ነው” ማለት፣ የምስጉንነት መገለጫ ሲሆን፣ “ክብረ ቢስና ክብረ ነክ” የሚሉት አገላለፆች ደግሞ ለአንድ ሰው የሚሰጠውን የክብር ስፍራ ዝቅ የሚያደርግ መሆኑን ይጠቁማሉ።
አበው ሲተርቱ “ከፍትፍቱ ፊቱ” ማለታቸው ከምግብ ይልቅ ክብር ስፍራ እንዳለው የሚያሳይ ሲሆን ከጮማና ጠጅ ግብዣው በላይ በክብር መቀበልና ማስተናገድ የተሻለ መሆኑን ይጠቁማል።
“አንገት ከሚሰበር ባይበላስ ቢቀር” ሌላው ክብርንና ኩራትን መጠበቅ ለኢትዮጵያውያን አስፈላጊ የሆነ የማንነታችን መገለጫ ነው። “አሰደብከኝ” ሲሉ አንድ አባት፣ ክብራቸው መነካቱን መግለፃቸውና ለክብር የሚሰጡት ቦታ ትልቅ መሆኑን ማስረዳታቸው ነው።
የክብር ስፍራ የምንለው ነገር አለ። “አኮራሽኝ/አኮራኸኝ” የሚሉት አባባሎች መደሰትን መግለጫ የተለመዱ ቃላት ናቸው። ጠቅለል ባለመልኩ፣ ኢትዮጵያውያን ለክብራቸው የሚጨነቁት፣ ኩራትን የሚያወድሱት በማንነታቸው የማይደራደር ስነልቦና ስላላቸው መሆኑን መናገር ይቻላል።
እንደ አቶ ነጋሽ ገለፃ ከሆነ መንፈሳዊነት ሌላኛው የኢትዮጵያውያን መገለጫ ነው። የዓለም ሁለቱ ታላላቅ እምነቶች፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ከብዙ አገራት ቀድመው የገቡ ናቸው።
በክርስትና ዕምነት ኢትዮጵያ በቅዱሳን መጽሐፍት ከመጠቀስ ባለፈ በእስልምና ሃይማኖትም አያሌ ሚሊዮን አማኞችን በማፍራትም ረገድ በቀዳሚነት ከሚመደቡ አገራት ረድፍ ነች።
ፒው የተባለ ዓለም አቀፍ የጥናትና ምርምር ተቋም፣ ከ99 በመቶ በላይ ኢትዮጵያውያን በፈጣሪ ህልውና እና ሃይማኖት በሕይወታቸው ውስጥ ቁልፍ ቦታ ያለው ነገር እንደሆነ በፅኑ እንደሚያምኑ ይናገራል።
በተጨማሪም ፈጣሪን መፍራት የአንድን ኢትዮጵያዊ አስተሳሰብ፣ እርምጃና ጥቅል የሕይወት መልክ ይገልፃል፤ ይወሰናልም። ነገስታትም የፅድቅና ኩነኔ እሳቤዎችን ይጋራሉ። ዳግማዊ አፄ ምኒልክ፣ ዓድዋ ላይ ፋሽሽቱ የጣልያን ጦርን ድል ካደረጉ በኋላ በፃፉት አንድ ደብዳቤ ላይ፣ “በጥጋባቸው መጥተው ወረሩን፣ በእግዜር ድጋፍ ድል አደረኳቸው፤ እኔ ግን የዚህን ሁሉ ክርስቲያን ሞት አይቼ የምደሰት አይደለሁም” ብለው ነበር።
በታላቁ መጽሐፍ መግደል ኩነኔ መሆኑን ያስረዳል፤ ነገር ግን ስለክብር የኢትዮጵያውያንን ስነልቦና ያላወቁት ጣሊያኖች “ኢትዮጵያውያኖች አማኞች ናቸው፣ ጦርነት አያነሱም” በማለት ጦርነት በመክፈታቸው ተሸንፈው ተመልሰዋል።
እኚህ ንጉስና ተከታዮቻቸው የገደሉት ታዲያ ባህር ተሻግሮ በመምጣት የወረራቸውን ጠላት ቢሆንም፣ በሟቾች አስከሬን ላይ ግን አልዘፈኑም ነበር። ሁሉም የፈጣሪ ሥራ ነው ብለው ስለሚያምኑ ነበር።
በሌላ በኩል በትዳር፣ በልጅ አስተዳደግ፣ በጉርብትና፣እና ስለ መንግሥት አነሳስ ወዘተ መንፈሳዊነት ኢትዮጵያ ውስጥ በፅኑ ይንፀባረቃል። ኢትዮጵያውያን ማግኘትና ማጣት፣ ደስታና ኀዘን፣ ድልና ሽንፈት፣ ጤናና ሀብት፣ ሰላምና ጦርነት ወዘተ የፈጣሪ ስጦታዎች እንደሆኑ ይታመናል።
በተጨማሪም የስነልቦና ባለሙያው ያነሱት በጋራ ሕይወትን መምራትም ዋነኛው መገለጫ እንደሆነ ነው። “ድር ቢያብር አንበሳ ያስር” የሚለው የአበው ብሂል፣ የትብብርን ጠቃሚነትና በጋራ ሕይወትን የመምራትን ጥልቅ ፋይዳ አጉልተው ያሳያሉ። አርሶ አደሮች በደቦ አብሮ ማረስ፣ ማጨድ፣ መሰብሰብና መውቃት ልማዳቸው ነው። ደግሶ ማብላት ደስ የሚያሰኝ ተግባር ነው። “ጠሪ አክባሪ ነው” ይባላል። “እንዴት ሳይጠራኝ” ተብሎ፣ አንድ ኢትዮጵያዊ ደጋሽ ወዳጅ ዘመዱን ይቀየማል።
“ለአንድ ብርቱ ሁለት መድኃኒቱ” ፣ “ልጅ ሀብት ነው”፣ “ተማክረው ምን ያሉት አይሸትም” ወዘተ የመሳሰሉ አባባሎቻችን ስንመለከት፣ በትብብር እና በጋራ መኖር የአንድ ኢትዮጵያዊ ማንነት እና ስነ ልቦና መገለጫ እንደሆኑ እንረዳለን።
በር ዘግቶ ለብቻ መብላት ነውር ነው። ዛሬም ድረስ ሬስቶራንት ውስጥ ያዘዝነው ምግብ ሲመጣ፣ “እንብላ/ብሉ” መባባልን አልተውንም። አሁንም “በሞቴ” ብለን እንጎራረሳለን። አስራ ስምንት ዓመት ስለሞላህ፣ ከቤት ውጣ የሚል ባህል ለኢትዮጵያውያን እንግዳ ነገር ነው። ደስታንም ችግርንም ለወዳጅ ዘመድ ማካፈል እንዲሁም ደስታና ኀዘንን በጋራ ማሳለፍ የተለመደ ነው።
በኢትዮጵያውያን ባህል ሁሉን ነገር ለራስ መያዝ አይበረታታም። አንድ ሰው ድብቅ ነው፤ ልቡ አይገኝም ወዘተ ሲባል እየተወቀሰ እንጂ እየተመሰገነ አይደለም። የእኛ ባህል ጀብደኝነትን፤ ድል አድራጊነትን፣ የበላይነትን፣ አሸናፊነትን ያበረታታል። ለዚህ ማሳያ የሚሆኑን በርካታ አባባሎች አሉን፤ “ወንድ ልጅ ተወልዶ ካልሆነ አንደ አባቱ” እና “አንበሳ ገዳይ” የሚሉት የተለመዱ ፉከራዎች ናቸው።
በተለይ በኢትዮጵያዊ ስነ ልቦና አተያይ አንድ ሰው እጁን ከሚሰጥ ራሱን የሚያጠፋ የጀግና ምልክት ነው።
ፈሪ ሰው የመዘባበቻና የመቀላለጃ ተምሳሌት ነው። ፈሪን ሚስቱም እናቱም አይኮሩበትም። ለስም፣ ክብር፣ እምነትና ሀገር መሞት በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ጎልተው የሚታዩ የኢትዮጵያውን ጀብደኛ ማንነት የሚያሳዩ ታሪኮች እልፍ ናቸው። አንበሳ የሚለው መጠሪያ ከአውቶብስ እስከ ባንክ፣ ከሻይ ቅጠሉ እስከ ስንቱ ነገር ድረስ ለመጠሪያነት መጠቀማችን የዚሁ ስነ ልቦናችን ማሳያ መሆኑን አቶ ነጋሽ ያብራራሉ።
ለታላላቆች ክብር መስጠት ሌላኛው የኢትዮጵያውያን ስነልቦና መገለጫ ሲሆን ሽበት ኢትዮጵያ ውስጥ ያስከብራል። በእድሜ መግፋት የማስተዋልና የጥበበኝነት ምልክት ነው። እናትና አባትን እንዲሁም ታላላቆችን ማክበር ያስከብራል።
በንፅፅር ስናየው፣ በውጭው ዓለም እርጅና መገለልን፣ ከሥራና ማኅበራዊ ህይወት መራቅን ያስከትላል። ኢትዮጵያ ውስጥ ግን በእድሜ ታላላቆቻችን አስታራቂዎች፣ ሸምጋዮችና መካሪዎች ናቸው። ከአበው ስር ቁጭ ብሎ መማርን እናበረታታለን።
ለኢትዮጵያዊ ማንነት መበረዝ መንስኤ አስመልክተው እንደተናገሩት የምዕራቡ ዓለም እሳቤ በኢትዮጵያውያን ማንነት ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ እያሳደረ ይገኛል። ዘመኑ የሳይንስና ቴክኖሎጂ በመሆኑ በተለምዶ እንደሚባለው ዓለም ወደ አንድ መንደርነት እየጠበበች ነው። ይህ መቀራረብ የባህል መወራረስን አምጥቷል።
በጎ ባህልን መውረስ እና ክፉውን መተው መልካም ሆኖ ሳለ፣ በጎ ያልሆኑ እና የእኛም ትውፊት ያልሆኑ ባህሎችን ግን እየወረስን መምጣታችን ማንነታችን መበረዙን ያመላክታል። ለአብነት ያህል ግለኝነት የምዕራቡ ባህል ነው። እኔነት ከእኛ ሲቀድም እያስተዋልን ነው።
ምክንያቱ እና ምንጩ ደግሞ የምዕራቡ ዓለም ስነልቦናን እንዳለ መውሰድ እንደሆነ ግልፅ ነው። የራሳችንን ጥለን የሌላውን የማንጠልጠል ዝንባሌያችን ከፍ ብሏል። ይኼ የውጭው ስነልቦና ተፅዕኖም የራሳችንን ባህልና ስነልቦና አራክሶ የማየት ችግር ያመጣው ውጤት ነው። ይኼ የእኛም የሌላውም ፈተና ነው።
አዲስ ዘመን የካቲት 16/2013