ምኩራብ አቃጥሏል የተባለው ተጠርጣሪ በፖሊስ ተገደለ

በሰሜናዊ ፈረንሳይ ሩየን ከተማ የሚገኝ ምኩራብ በማቃጠል የተጠረጠረው ግለሰብ በፖሊስ ጥይት መገደሉን የሀገሪቱ ባለስልጣናት አስታወቁ። ግለሰቡ ቢላዋ እና ብረታማ መሳሪያ ይዞ እንደነበር የተገለጸ ሲሆን፤ ፖሊሶችን በማስፈራራቱ በጥይት መመታቱን የሩየን አቃቤ ሕግ ተናግረዋል።

የሩየን ከንቲባ ኒኮላስ ማየር ሮሲግኖል በበኩላቸው፤ በምኩራቡ ላይ የተፈጸመው ጥቃት የአይሁድ ማህበረሰብን ብቻ ሳይሆን “መላውን የከተማዋ ነዋሪ ድንጋጤ ውስጥ የከተተ ክስተት ነው” ብለዋል። የፈረንሳይ ሚዲያዎች ተጠርጣሪው አልጀሪያዊ ዜግነት ያለው እንደሆነ እና ፈረንሳይን ለቆ እንዲወጣ ውሳኔ ተላልፎበት በዚህ ላይ ይግባኝ ብሎ እየተጠባበቀ እንደነበር ዘግበዋል።

ከምኩራቡ ጢስ ሲወጣ በመታየቱ ፖሊስ ማለዳ 12፡45 ተጠርቷል። ጥቃት ፈጻሚው በትልቅ የቆሻሻ ማጠራቀሚያ ላይ ወጥቶ በመስኮት በኩል ከቤንዚን የተሠራ ቦምብ ከወረወረ በኋላ በምኩራቡ ላይ እሳት ተነስቷል። ተጠርጣሪው በደህንነት ካሜራዎች ላይ ከታየ በኋላ ሁለት ፖሊሶች በፍጥነት ወደ ስፍራው መድረሳቸው ተነግሯል። ፖሊሶቹ ሲደርሱ ግለሰቡ በምኩራቡ ጣሪያ ላይ እንደነበር አቃቤ ሕግ ገልጿል።

እንደ አቃቤ ሕጉ ከሆነ ተጠርጣሪው ፖሊሶቹን 25 ሴንቲ ሜትር ባለው ስለት ካስፈራራቸው በኋላ ወደ መሬት ወርዷል። “አንደኛው ፖሊስ በተጠርጣሪው ላይ አምስት ጊዜ የተኮሰበት ሲሆን፤ አራቱ ጥይቶች አግኝቶት ሕይወቱ አልፏል” ሲሉ ሁኔታውን በደህንነት ካሜራዎች መመልከታቸውን ዋቢ በማድረግ የሩየን አቃቤ ሕግ ፍሬደሪክ ቴይሌት ተናግረዋል።

በስፍራው የደረሱ የእሳት አደጋ ሠራተኞች በከተማዋ ታሪካዊ ማዕከል ውስጥ በሚገኘው ምኩራብ የተነሳውን እሳት በቁጥጥር ስር ማዋላቸው ተገልጿል። ከተገደለው ተጠርጣሪ በስተቀር ሌላ ተጎጂ ያለ እንደማይመስልም ከንቲባው አስረድተዋል።“እሳቱ በምኩራቡ ላይ ያደረሰው ጉዳት ከፍተኛ እንደሆነም ተነግሯል።

“በጣም የሚያሳዝን ነገር ነው። ከፍተኛ ጥፋት ነው የደረሰው” ሲሉ 150 ቤተሰቦችን ያቀፈው የሩየን አይሁዶች ማህበረሰብ ኃላፊ ናታቻ ተናግረዋል። የምኩራቡ ግድግዳዎቹ እና ዕቃዎቹ በእሳቱ ቢጠቁሩም ቅዱሳን መጻሕፍቱ ላይ ምንም ጉዳት አልደረሰም ተብሏል ሲል ቢቢሲ ዘግቧል።

አዲስ ዘመን ግንቦት 11 ቀን 2016 ዓ.ም

Recommended For You