ኤችአይቪን የሚከላከለው መድኃኒት ውጤታማ መሆኑ በጥናት ተረጋገጠ

ዌልስ ውስጥ በሙከራ ላይ የነበረውና በሰውነት ውስጥ የኤችኤይቪ ቫይረስ ሥርጭትን የሚገታው መድኃኒት ውጤታማ መሆኑ በጥናት ተረጋገጠ። የመድኃኒቱ ውጤታማነት የተረጋገጠው በመላው እንግሊዝ ከተውጣጡ እና በጥናቱ በተካተቱ ከ24 ሺህ በላይ የመድኃኒቱ ተጠቃሚዎች ላይ ምርመራ ከተካሄደ በኋላ ነው።

በእንግሊዝ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ፒአርኢፒ የተሰኘውን ይህን መድኃኒት ከሥነ ተዋልዶ ጤና ክሊኒኮች እየወሰዱ ይገኛሉ። ከቼልሲ እና ዌስትሚኒስትር ሆስፒታል ጋር በመሆን የመድኃኒቱን ውጤታማነት ለማረጋገጥ የተደረገውን ሙከራ የመራው የዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) የጤና ደኅንነት ኤጀንሲ፣ ጥናቱ በዓይነቱ ከዚህ ቀደም ከተሠሩ ጥናቶች ሰፊ መሆኑን ገልጿል።

ጥናቱ ከአውሮፓውያኑ ጥቅምት 2017 እስከ ሐምሌ 2020 ባሉት ጊዜያት እንግሊዝ ውስጥ በሚገኙ 157 የሥነ ተዋልዶ ጤና ተቋማት ላይ ተካሂዷል። ይህ ጥናት ‘ፕሪ ኤክስፖዠር ፕሮፍላክሲስ (ፒአርኢፒ)’ የተባለው መድኃኒት ጥቅም ላይ እንዲውል ማረጋገጫ የሰጠ ሲሆን መድኃኒቱ በኤችአይቪ የመያዝ ዕድልን በ86 በመቶ ይቀንሳል።

በክሊኒክ የተደረጉ ሙከራዎች እንዳመለከቱትም መድኃኒቱ 99 በመቶ ውጤታማ ነው። የዩኬ ጤና ደኅንነት ኤጀንሲ የመድኃኒቱ ውጤታማ መሆን የሀገሪቷ መንግሥት በ2030 የኤችአይቪ ሥርጭትን ዜሮ ለማድረስ ያስቀመጠውን ግብ ለማሳካት ይረዳል ብሏል። በጥናቱ ላይ የተሳተፉት የሥነ ተዋልዶ ጤና እና ኤችአይቪ አማካሪ ጆን ሳንደርስ እንዳሉት ሙከራው መድኃኒቱ ኤችአይቪን ለመከላከል ውጤታማ መሆኑን ይበልጥ ያሳየ ነው።

ይህም ቀደም ብለው ከተሠሩ ጥናቶች በበለጠ መድኃኒቱ በሽታውን የመከላከል አቅሙን ለመጀመሪያ ጊዜ አሳይቷል ብለዋል። ትሬንስ ሂጊንስ ኤችአይቪ የተባለው ግብረሰናይ ድርጅትም ጥናቱ መውጣቱን በበጎ ተቀብሎ፤ ነገር ግን ተደራሽነትን ለማስፋት፣ ስለመድኃኒቱ ግንዛቤ ለመስጠት ብዙ ሊሠራ እንደሚገባ ጠቁሟል።

የድርጅቱ የፖሊሲ ጉዳዮች ኃላፊ ደቢ ላይኮክ መድኃኒቱ በመድኃኒት ቤቶች እና በበይነ መረብ (ኦንላይን) ተደራሽ እንዲሆንም ጠይቀዋል። ዶ/ር ሳንደርሰን እንዳሉት ምንም እንኳ ምርምሩ የመድኃኒቱን ውጤታማነት ከማረጋገጡ ባሻገር ጥናቱ እንዴት ጥቅም ላይ እንደሚውል የሚያስረዱ ሌሎች ጠቃሚ መረጃዎችን ይፋ አድርጓል።

«መጀመሪያ ምን ያህል ሰዎች መድኃኒቱን እንደሚፈልጉ እንዲሁም ለምን ያህል ጊዜ መድኃኒቱን ሲወስዱ እንደቆዩ አናውቅም ነበር። አሁን ላይ ግን መድኃኒቱ ለማን መታዘዝ እንዳለበት ተረድተናል። በመሆኑም ብዙ ሰዎችን ለመድረስ ከክሊኒኮች ጋር መሥራት እንችላለን» ብለዋል ሳንደርሰን።

ፒአርኢፒ ቀደም ብሎ የነበሩትን ቴኖፎቪር ዲሶፕሮክሲል እና ኢምትሪሳይታቢን የተባሉ የኤችአይቪ መድኃኒቶችን የያዘ ሲሆን፣ የኤችአይቪ ቫይረስ ወደ ሰውነት እንዳይገባ እና በሰውነት ውስጥ ከገባም በኋላ ራሱን እንዳያባዛ ያደርጋል።

መድኃኒቱ በክኒን መልክ በቀን አንዴ መወሰድ አሊያም ከወሲብ ግንኙነት ቀደም ብሎ መወሰድ ይችላል። ይህንን መድኃኒት እንደ አውሮፓውያኑ በ2020 በእንግሊዝ በስፋት እንዲሰራጭ የተደረገው ቀደም ብሎ በተሠሩ ጥናቶች ውጤት ላይ በመመሥረት ነበር። አሁን ላይ የጥናቱ ውጤት በላንሴት ኤችአይቪ ላይ የታተመው ሰፋ ያለ ናሙና ስለተወሰደ እና ጥናቱን ሌሎች ተመራማሪዎች ሰፊ ጊዜ ሰጥተው ስለተመለከቱት ነው ተብሏል።

በጋዜጣው ሪፖርተር

አዲስ ዘመን ህዳር 21/2016

Recommended For You