ሙዚቃዎቹ የብዙዎች የፍቅር ታሪክ ውስጥ ቦታ አላቸው። ድምጹ ነጎድጓዳዊ ነው። ድምጻዊ ብቻ ሳይሆን የሙዚቃ መሳሪያ ተጫዋችም ነው። ራሱ ኪቦርድ እየተጫወተ ከመዝፈኑ ባለፈም የሌሎችንም ሙዚቃዎች ሰርቷል። ላለፉት 32 አመታት ኑሮውን በአገረ አሜሪካ ቢያደርግም ዛሬም ድረስ በብዙዎች ልብ ውስጥ የታተሙ በወጣት ድምጻውያንም በብዛት የሚቀነቀኑ ሙዚቃዎች ባለቤቱ ተሾመ አሰግድ የዛሬው ገፃችን ትኩረት ነው።
የተወለደው በእለተ እንቁጣጣሽ መስከረም 1 ቀን 1945 ዓ.ም በያኔው ወለጋ ጠቅላይ ግዛት ቄለም አውራጃ ደምቢ ዶሎ ከተማ ውስጥ ነው። ስድስት ወንድ እና ስምንት ሴት በተወለደበት ቤተሰብ ውስጥ ተሾመ ለአቶ አሰግድ ይመር አራተኛው ልጅ ነው። ያሳደጉት አክስቱ ወ/ሮ አማከለች በአካባቢያቸው የሚታወቁ ሴት ናቸው። ተሾመ ገና የ5 ወር ህጻን እያለ ነው የአይን ብርሃኑን ያጣው። ነገር ግን ምናልባትም በዚያ ወቅት ሳይሆን አይቀርም ጥበብ ወደ ተሾመ የመጣችው። ከጥበብም ሙዚቃ።
ተሾመ ገና ከልጅነቱ ሙዚቃ እንደሚወድ ይናገራል። በተለይም የክብር ዶክተር አርቲስት ጥላሁን ገሰሰ ድምጽ በተሾመ ልብ ውስጥ ታትሞ ቀርቷል። የሌላኛው አንጋፋ ድምጻዊ ፍሬው ሀይሉ አይናማዬ ነሽ አይናማዬ የተሰኘ ሙዚቃንም በጣም እንደሚወደው እና ከአፉ እንደማይጠፋ ይናገራል። በአካባቢያቸው የማይጠፉት ባለ መሰንቆ የኦሮምኛ አዝማሪዎችም የተሾመን ጆሮ ስለውታል። እናም እሱም እድሉን ባገኘ ቁጥር ያንጎራጉራል። ወ/ሮ አማከል ደግሞ ቤት ስራ ላይ ሲሆኑ ሬዲዮ ከፍተው ለተሾመ የሚወደውን ሙዚቃ የማዳመጥ እድሉን ያመቻቹለታል።
የ6 አመት ልጅ ሳለ አንድ ቀን ሰርግ ላይ ከበሮ እየተመታለት ሲዘፍን በወቅቱ በወለጋ አካባቢ ሚሽን የነበራቸው ኦሮምኛ ተናጋሪው ካናዳዊው የፕረስባይቴሪያን ሚሽን አገልጋይ ካናዳዊው ሚስተር ረስል ይሰሙታል። ቀልባቸው ይወደዋል። ጠጋ ብለው ትምህርት ቤት መሄድ ትፈልጋለህ አሉት። ተሾመ ትምህርት ቤት ምን እንደሆነ ባያውቅም አዎ አለ። ይዘውት መኪናቸው ውስጥ ገቡ። ወ/ሮ አማከለች ተጠሩ። ልጅሽን ላስተምረው ልወስደው ነው አሏቸው። እሺ አሉ። ሚስተር ረስል ለተሾመ አዲስ ቁምጣ፤ ሸራ ጫማ እና ጥብቆ ሰጡት። ከልጆቹ ጋር እንግሊዝኛ ቋንቋን በቤቱ ሌላውን ትምህርት በሚሽኑ እያስተማረ ያሳድገው ጀመር። አዲስ ሕይወት ተጀመረ። ከትምህርቱ ጎን ለጎን ግን አዲስ አጋጣሚም ተፈጠረ። የሚስተር ረስል ባለቤት ኦርጋን ይጫወታሉ። በቤታቸው በእግር እየተረገጠ የሚጫወቱት አርሞኒየም የተባለ መሳሪያ አላቸው። ይህ ሙዚቃን ለሚወደው ተሾመ ፍጹም አስደሳች ሆነለት። ቀስ በቀስ እሱም መጫወትን መልመድ ያዘ።
ከእለታት አንድ ቀን ሚስተር ረስል ተሾመን ወደሚያስተምሩበት አሜሪካን ሚሽን አንድ ትልቅ እንግዳ መጣ። ለእንግዳው አቀባበል አበባ እንዲያበረክት የተመረጠው ደግሞ በእድሜ ትንሹ ተሾመ ነበር።አበባውን አበረከተ።እንግዳው ትንሹን ተሾመ አፋን ኦሮሞ ቤክታ ብለው ጠየቁት።ኦሮምኛ እንደሚችል በኦሮምኛ ነገራቸው። እኛ ማን ነን አሉት። የኢትዮጵያ ብርሃን ጃንሆይ ነዎት አላቸው። ምን ቢደረግለት እንደሚወድ ጠየቁት። ልጅ ነውና አዲስ ሸራ ጫማ እንዲገዙለት እንደሚፈልግ ነገራቸው። መሻቱ ተፈጸመለት። ጃንሆይ ወደ ሚስተር ረስል ዞሩ። ሚስተር ረስልም ትምህርት ቤቱ ከበጀት አንጻር ያለበትን ችግር አስረዱ። በትምህርት ቤቱ ከሚማሩ አይነ ስውራን ተማሪዎች ስምንቱ ወደ ሌላ ቦታ ሄደው እንዲማሩ ተወሰነ። አራቱ ወደ ባኮ አራቱ ወደ ሰበታ። ወደ ባኮ ከተዘዋወሩት አራት ተማሪዎች መሀከል አንዱ ተሾመ ሆነ።
ባኮ ለጥቂት አመታት ከቆየ በኋላ 1959 ሰበታ መርሀ እውራን ተቀላለቀለ። ወደ ሰበታ መምጣቱ ለተሾመ የሙዚቃ ሕይወት መሻሻል አስተዋጽኦ አደረገ። ትምህርት ቤቱ ብዙ የሙዚቃ መምህራን ነበሩት። የሙዚቃ ባንድም ነበረው። እንደ ጓደኛም እንደ አርአያም የሚያየውን አብዱቄ ከፈኔንም ተዋወቀ። ከባንዱ ጋር ሙዚቃውን መጫወት ቀጠለ። በወቅቱ ያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤትን ለመቀላቀል ቢሞክርም ትምህርት ቤቱ አይነስውራንን ማስተማሪያ መላው ስለሌለው አልተቀበላቸውም ነበር። ቢሆንም ታዋቂው የሙዚቃ ቀማሪ አሸናፊ ከበደ በግላቸው እነ ተሾመን በሳምንት ሁለት ቀን እየወሰዱ ትምህርት ያስተምሯቸው ነበር። እነ ሲራክ ታደሰን 4ኛ ክፍል ጦርም እንዲሁ እነ ተሾመን ያግዙ ነበር። በየሁለት ሳምንቱ ወደ ሰበታ ጎራ የሚሉት አንድ ሁለት ጊዜ ሽልማት ያበረከቱለት ሲሆን ሙዚቃው ላይ እንዲበረታም ገፋፍተውታል።
ከሰበታ በኋላ ለሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ወደ ኮከበ ጽባህ ተቀላቀለ። እዚያ ደግሞ ጓደኛው አብዱቄ የወንዶች የሙዚቃ ቡድን አቋቋመ። ቀስተ ደመና የሚባል 7 አይነ ስውራን አንድ ላይ ሆነው ያቋቋሙት ባንድም ነበር። ይህ ባንድ ባቲ እና ትዝታ የተሰኘ አልበም የሰራ ሲሆን እዚህ ውስጥ ካሉት ሙዚቃዎች መሀከል አንዱ በክብር ዶክተር ጥላሁን ገሰሰ የተዘፈነው ይህች አጋጣሚ ሙዚቃ አንዱ ነው። ሙዚቃው ተሾመ ሊጫወተው ተብሎ የተዘጋጀ ሙዚቃ የነበረ ቢሆንም አሳታሚው ከተሾመ ይልቅ ለጥላሁን የተሻለ ይሆናል ተብሎ በመታመኑ ጥላሁን እንዲዘፍነው ተደርጓል። የሙዚቃውን ገቢ ጥላሁን ለኢትዮጵያ አይነ ስውራን ማህበር የሙዚቃ ቡድን ለግሷል።
የስርአት ለውጥ መጣ እና ጃንሆይ ወርደው ደርግ ስልጣኑን ያዘ። የእናት አገር ጥሪ መጣ እና እነ ተሾመም በሙዚቃቸው አገራዊ ግዴታቸውን ተወጡ። ደርግ ከምስራቅ ጀርመን ጋር ወዳጅ ነበርና የትምህርት እደል ተገኘ። የኢትዮጵያ አይነ ስውራን ማህበር የመጣውን የትምህርት እደል ለተሾመ ሰጠ። ወደ ምስራቅ ጀርመን ሄዱ የፒያኖ አጠቃቀም እና ጥገና ትምህርት ተማረ። ከምስራቅ ጀርመን ሲመለስ ሙዚቃን መጫወቱን ቀጠለ። ቪላቨርዴ የሚባል ቤት ከኩኩ ሰብስቤ ጋር ሙዚቃ መጫወት ቀጠለ። ከዚያም ዋቢ ሸበሌ እና ሂልተን ሆቴል ላይ ከኢትዮ ስታር ባንድ ጋር መጫወት ቀጠለ።
ቀጣዩ የተሾመ የሕይወት አቅጣጫ ከአገር የሚያስወጣ ሆነ። ወደ ጎረቤት አገር ጂቡቲ ተጓዘ። እዚያ ለ5 አመት ቆየ። እዚያ እያለ ነው ተወዳጅ የሆኑትን ስራዎቹን መስራት የጀመረው። ከሰራቸው ስራዎች አብዛኞቹ ሙዚቃዎች ዛሬም ድረስ በሕዝብ ጆሮ ላይ የታተሙ ናቸው። በተለይም የኔ አካል የኔ ነሽ እያደር እንደ አዲስ እየተደመጠ ያለ ሙዚቃው ነው።
የኔ አካል የኔው ነሽ
ምን አወርስሻለሁ
አንጀትና ልቤን
ያው ትቼልሻለሁ
ይህ ሙዚቃ ዛሬም አዲሱ ትውልድ እንደ አዲስ ይሰማዋል ብቻ ሳይሆን በተለያዩ ድምጻውያን ተደግሞ ተዘፍኗል ፤ በሙዚቃ ተሰጥኦ ውድድሮች ላይ ብዙ ወጣቶች ባለ ተሰጥኦ መሆናቸው የሚያሳዩበት አልበም ነው። ሌላኛው እሱም ከፍተኛ ዋጋ የሚሰጠው እንዲያው ዘራፌዋም ተወዳጅ ስራው ነው። ደግሜ ስሰማው እንዴት እንደዚህ አድርጌ ዘፈንኩበት ብዬ የምደነቅበት ሙዚቃ ነው ይላል። ሕዝብ በጣም የሚወድለት ሌላኛው ስራው ደግሞ የኩባያ ወተት ነው። ከሮሃ ባንድ ጋር በአምባሰል ሙዚቃ ቤት የተዘጋጀው ይህ ሙዚቃው በወቅቱም ዛሬም ተወዳጅ ሙዚቃ ነው ብቻ ሳይሆን የተሾመ መታወቂያውም ነው ማለት ይችላል።
የኩባያ ወተት
የለውም አረፋ
በሽታዬን የሚያውቅ
አስታማሚ ጠፋ
ያንን ጋራ የተሰኘው ሙዚቃውም እንዲሁ ተወዳጅ ሙዚቃው ነው።
ያንን ጋራ አቋርጠሽ ሁሌ ማልምሽ
ያንን ጋራ አቋርጠሽ በአካል የማይሽ
የአገሬ ልጅ እንደምንድን ነሽ
ካላጣሽው አካል ፤ ሞት አደላድሎን እና በእጆቼ እየዳሰስ ኩም በኤልያስ ጉሮሮ ሲደመጡ አዲስ ቀለም ያገኙ የሌሎች ዝነኛ ድምጻውያን ውብ ሙዚቃዎች ናቸው። ኤልያስ ከበርካታ አንጋፋ ድምጻውያን ጋር በጋራ በመሆን 2 አልበም ሰርቷል። አንደኛው አልበም ከበዛወርቅ አስፋው፤ ኤልያስ ተባበል እና ማርታ አሻጋሪ ጋር በመሆን የሰራው ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ከራሄል ዮሀንስ፤ አሰፉ ደባልቄ እና ኬኔዲ መንገሻ ጋር በመሆን የሰራው ነው። በተለይ ከራሄል ጋር የዘፈነው ገላዬ ናና እና በአምባው ላይ በጣም ተወዳጅ ሙዚቃዎች ናቸው።
ኤልያስ በግሉ ሶስት በጋራ ሁለት አልበሞችን ያወጣ ሲሆን ለሌሎችም ድምጻውያን ሙዚቃ ሰርቷል። ከኢትዮ ስታር ባንድ ጋር በመሆን በጋራ ያቀናበረው የቴዎድሮስ ታደሰ አልበም ሉባንጃዬ ለዚህ ተጠቃሽ ነው። የአልበሙ መጠሪያ የሆነው ሉባንጃዬ እና ቀን ሳይመሽ ሳይጨልም በጊዜ የተሾመ ስራዎች ናቸው። ከኦርኬስትራ ኢትዮጵያ ጋር በመሆን ያቀናበራቸው አልማዝን አይቼ እና ያለቀሰም ሲስቅ የሳቀም ያለቅሳልም እንዲሁ ተወዳጅ ስራዎቹ ናቸው። ተሾመ ድምጻዊ ብቻ አይደለም። ማሲንቆ አኮርዲዮን እና ኪቦርድን ጨምሮ ብዙ ስራዎችን ሰርቷል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የተሾመ ስራዎች ዛሬም ድረስ ተወዳጅ የመሆናቸውን ያህል የኮፒራይት ጥሰት ሰለባ ናቸው። ብዙዎች የሚያውቁት በድምጻዊ ጎሳዬ ቀለሙ (ጃኪ ጎሳዬ) የተዘፈነው የተሾመ ተወዳጅ ስራ የኔ አካል አንዱ ሲሆን ድምጻዊው ተሾመን ይቅርታ ጠይቆ ችግሩ ተፈቷል። ከዚህ ሙዚቃው በተጨማሪ ሌሎቹም ስራዎቹ እንዲሁ በድጋሚ የተዘፈኑ ሲሆን ተሾመ በዚህ ዙሪያ በተደጋጋሚ በሚያሰማው ቅሬታ ወጣት ድምጻውያን ከመዝፈናቸው በፊት የሙዚቃውን ባለቤቶች ፈቃድ መጠየቅ አለባቸው ብሏል። ከዚህ ቀደም እሱም የሌሎችን መዝፈኑን ነገር ግን ይህን ሲያደርግ ባለቤቶቹን እንዳስፈቀደ የሚናገረው አንጋፋው ድምጻዊ በኮፒ ራይት መብት ዙሪያ መሰራት እንዳለበት በአጽንኦት ተናግሯል።
ተሾመ በአሁኑ ወቅት በአሜሪካ አገር የሚኖር ሲሆን በአንድ ወቅት በሰጠው ቃለመጠይቅ ናዮሚ ተሾመ የምትባል በሙያዋ የህክምና ዶክተር የሆነች እና አዲስ አበባ የምትኖር ልጅ እንዳለችው ተናግሯል።
(አቤል ገ/ኪዳን)
አዲስ ዘመን እሁድ ሚያዝያ 2 ቀን 2014 ዓ.ም