ሎሬት ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ገብረእግዚአብሄር ባለፈው ሳምንት በ83 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ የሚለው መርዶ የበርካታ ኢትዮጵያውያንን ልብ ያለ ልዩነት የሰበረ ከመሆኑ ባሻገር በማህበራዊም ሆነ በመደበኛው ሚዲያ ሰፊ ሽፋን ማግኘቱ አገር ትልቅ ባለውለታዋን ለማጣቷ ህያው ምስክር ነው። ታዋቂው የብዝሃ ሕይወት ሳይንስቲስት ሎሬት ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ገብረእግዚአብሄር ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው እንደተሰማ መላው ኢትዮጵያዊ ከሊቅ እስከ ደቂቅ ሀዘኑን ገልጿል። ሎሬት ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ባደረባቸው ሕመም በአገር ውስጥ በሕክምና ሲረዱ ቆይተው በ83 ዓመታቸው ባለፈው ሰኞ መጋቢት 11/2015 ለማክሰኞ አጥቢያ 9፡00 ላይ በሞት መለየታቸውን ቤተኛው ደራሲ እና ጋዜጠኛ ዘነበ ወላ አስታውቋል።
ዶክተር ተወልደ ብርሃን በአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ አገልግሎት የተከበረ ሥም ያላቸው ሲሆን፤ በዘርፉ ላደረጉት ምርምር እና በጉዳዩ ዙሪያ ከፍተኛ ግንዛቤ እንዲፈጠር ላደረጉት ጥረት በፈረንጆቹ 2000 (Right Livelihood Award) ሽልማትን አግኝተዋል። በተጨማሪም፣ በፈረንጆቹ 2006 ዓመት የተባበሩት መንግሥታት በአካባቢ ጥበቃ ዙሪያ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላደረጉ ሰዎች የሚሰጠውን Champions of the Earth ሽልማት አግኝተዋል። ከተማሩበት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ደግሞ በ1997 የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ተቀብለዋል። ሎሬት ዶ/ር ተወልደ ብርሃን የሦስት ሴቶች ልጆች አባት ሲሆኑ ከ60 በላይ ሌሎች ልጆችን ያሳደጉ ልበ ቀና ሰው እንደነበሩ ይነገርላቸዋል። ታዋቂው የአካባቢ ጉዳይ ሳይንስቲስት ዶክተር ተወልደ ብርሃን ገብረእግዚአብሄር የደራሲ ስብሐት ገብረእግዚአብሔር ታናሽ ወንድም መሆናቸው ይታወሳል ይለናል ሰሞኑን በስፋት በማህበራዊ ሚዲያ ሲዘዋወር የተመለከትሁት መርዶ።
መኃልየ መኃልይ ዘሰሎም ከሁሉም የሚበልጥ የሰለሞን መዝሙር ማለት ነው። የሁለት ፍቅረኛዎች ንግግር ተደርጎም ይወሰዳል። የፍቅረኞች ንግግር በግጥም ነውና ምት፣ ዜማ አለው። ሰለሞን ስለ ሙሽራውና ሙሽሪት፣ ስለፈጣሪና ስለ ቤተ ክርስቲያን የዘመራቸውን 1ሺህ 5 መዝሙሮችን ይመለከታል። ሙሽራው ልዑል እግዚአብሔርን ሲወክል ሙሽራይቱ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት። መኃልይ እንደ ለዘብና ወረብ አይነት በፍጥነት የሚዘመር ጥዑም መዝሙር ነው። መዝሙሮቹ በተለያየ ስልት ዜማ ቢደጋገሙም ያው ስለፈጣሪና ቤተ ክርስቲያን ክብር፣ ቅድስና የሚመስክሩ ናቸው። ይህ መጣጥፍ ስለ ዶ/ር ተወልደብርሃን ገብረ እግዚአብሔር፤ የሚዘክር፣ የሚያወድስና የሚያከበር ሆኖ ስለአገኘሁት” መኃልዬ መኃልዬ ዘ “እናት ምድር ባለውለታ”ማለትን መርጫለሁ።
ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ገብረ እግዚአብሔር የካቲት 11 ቀን 1936 ዓ.ም ትግራይ ተወልደው የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በተወለዱበት አካባቢ፣ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ደግሞ በጄነራል ዊንጌት ትምህርት ቤት ተከታትለዋል። እንዲሁም ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ገብተው በባይሎጂ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በከፍተኛ ማዕረግ የወርቅ ሜዳሊያ በማጥለቅ አጠናቀዋል። በመቀጠል ወደ እንግሊዝ ሄደው ከዌልስ ዩኒቨርሲቲ በዶክትሬት ዲግሪ ተመርቀዋል።
ከዚያም በ1961 ዓ.ም ወደ አገራቸው ተመልሰው በዩኒቨርሲቲ መምህርነትና በሳይንስ ፋኪልቲ ዲንነት፣ ሰርተዋል። ወደ አስመራ ዩኒቨርሲቲ ተልከው በፕሬዚዳንትነት ለስምንት ዓመታት በከፍተኛ ኃላፊነት መርተዋል። ከ1983 ዓ.ም የመንግስት ለውጥ በኋላም የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ስትራቴጂ ሴክሬታሪያት ዳይሬክተር ቀጥሎም የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው ለአገር የሚጠቅሙ በርካታ ተግባራትን አከናውነዋል።
ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ገብረእግዚአብሔር በሥነ ሕይወትና በአካባቢ ጥበቃ ላይ ከ30 በላይ ጥናቶችን በማሳተም፣ የአካባቢ ጥበቃ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ የሥነ ሕይወት ሀብታችንን የሚገልጹ መጽሐፎችን በማሳተምና በመሳሰሉት ለአገርና ህዝብ የሚጠቅሙ ተግባራትን አከናውነዋል። ከዚህ አልፈው በአፍሪካ ኅብረት ውስጥ ማኅበረሰብ፣ ገበሬዎችና ከብት አርቢዎች የሥነ ሕይወት ሀብት ተጠቃሚነታቸውን የሚያረጋግጥ ሕግ በተጨማሪም የአፍሪካን የባዮ ቴክኖሎጂ ሴፍቲ ሕግ በማርቀቅ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርገዋል።
በዓለም አቀፍ ደረጃም አገራችንንና አፍሪካን በመወከል በብዝኃ ሕይወትና በአካባቢ ጥበቃ ላይ በተመረኮዙ የተለያዩ ድርጅቶች ላይ በግንባር ቀደምትነት ተሳትፈዋል። በተለይ ጂ 77 ተብለው ለሚታወቁ አገሮች ዋንኛ ተከራካሪ ሆነው በመሪነት በተጫወቱት ሚና በሥነ ሕይወት ደኅንነትና ብዝኃ ሕይወት ጥበቃ እንዲከበር፣ ታዳጊ አገሮች አገር በቀልና የማህበረሰብ መብቶች እንዲከበሩ ሽንጣቸውን ገትረው ተከራክረዋል። በታሪክ የተመዘገቡ ውጤቶችንም አስመዝግበዋል።
ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ገ/እግዚአብሔር በአገራችን የአካባቢ ሥነ ሕይወትና ብዝኃ ሕይወት ጥበቃ ጉዳይ ሲነሳ ከማንም በላይ በታላቅ ክብር ስማቸው የሚነሳ የተከበሩ ሳይንቲስት ናቸው። በዓለም አቀፍ ደረጃም በብዙ የምርምርና የትምህርት ተቋማት፣ ዓለም አቀፍ ድርጅቶችና ታዋቂ ሰዎች ዘንድ የከበረ ስም አትርፈዋል። በተሰማሩበት መስክ የአገርንና የህዝብን ጥቅም በማስቀደም በተለይም የአርሶ አደሮችና የአርብቶ አደሮች ጥቅም እንዲጠበቅ በቁርጠኝነት ጠንክረው ሰርተዋል።
በተዳቀሉ እህሎች በእርዳታ ሰበብ ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡና ትውልድ እንዳይበላሽ በዓለም አቀፍ መድረኮች ጭምር ተከራክረዋል። በአጭር መግለጫ ተገልጾ በማያበቃው ሥራቸው በዓለም አቀፍ ደረጃ የተለያዩ የክብር ሽልማቶችን አግኝተዋል። ከዚህም ውስጥ እኤአ በ2006 ዓ.ም የተባበሩት መንግስታት ከፍተኛ የአካባቢ ጥበቃ ሽልማት “የምድር ሻምፒዮን”ተብለው ተሸልመዋል። ከላይ በተጠቀሱትና በሌሎችም ለአገርና ለህዝብ በሚጠቅሙ የላቁ ተግባሮቻቸው የተነሣ መንግሥታዊ ኃላፊነትን በመወጣት ዘርፍ የ2008 ዓ.ም የበጎ ሰው ሽልማት አሸናፊ መሆናቸው አይዘነጋም።
ዶክተር ተወልደ ብርሀን ገብረእግዚአብሔር የብዝሀ ሕይወት ጉዳይ የሚገዳቸው፤ በዓለም አቀፍ መድረኮች በማደግ ላይ የሚገኙ 134 አገራትን ወክለው የተደራደሩ ሳይንቲስት ነበሩ። ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ዶክተር ተወልደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እና አስመራ ዩኒቨርሲቲን ጨምሮ በተለያዩ ተቋማት በሙያቸው አገልግለዋል። የአካባቢ ጥበቃ ህይወት ሳይንቲስት የነበሩት በርካታ ዓለም አቀፍና የአገር ውስጥ ሽልማቶችን ባለቤት ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ገብረ እግዚአብሔር ለአገራችንም ሆነ ለዓለም አርሶ አደሮችን መብት ያስከበሩ የዘረ መል ማሻሻያ በተደረገባቸው ወይም የGMO ምግቦች ያላቸውን ተጽዕኖ አስመልክተው ውጤት ያለው ድርድር ያደረጉ ሳይንቲስት ነበሩ። በሥነ-ምህዳር ሳይንስ አያሌ ምሁራን ለዓለም ያፈሩ እንዲሁም በርካታ መጽሃፍትን በመጻፍ፣ የአካባቢ ጥበቃ ስትራቴጂዎችን በመቅረጽ ለአገር ያበረከቱ ሳይንቲስት ነበሩ።
የ83 ዓመት የእድሜ ባለፀጋ የነበሩትን ሳይንቲስት ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ገብረ እግዚአብሔር ከአራት አስርት ዓመታት በላይ እንደሚያውቋቸው ለዶቼ ቬሌ የተናገሩት ፕሮፌሰር እንዳሻው በቀለ ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ተቋምን ብቻ ሳይሆን አብረው ሰው የመሰረቱና ያፈሩ ትልቅ ሰው ናቸው ሲሉ በአገራችን ይሁን በአህጉር ደረጃ ትልቅ አስተዋጽኦ ያደረጉ ናቸው ብለዋል። ካበረከቱት ስራዎች መሀከል ጥቂቶቹን አካፍለውናል።
«ባደጉት አገሮች መሀከል ያለውን የብዙሃ ህይወት አጠቃቀም እና የመካፈል ወይንም አብሮ ቀጣይነት እድገት ላይ ለመስራት ትልቅ አስተዋጽኦ ያደረገ ነው።» አያይዘውም «የአፍሪቃ አገሮች አስተባብሮ የተሟገተ ተሟግቶም ያሸነፈ በመጨረሻም አፍሪቃ የራስዋን እንብዛ ህይወት እንድትጠብቅ ያደረገ ሰው ነው» በአገራችንም ቢሆን ይላሉ ፕሮፌሰር እንዳሻው «በኢትዮጵያ አካባቢ ጥበቃ ላይ ብዙ ህጎች እንዲወጡ በአየር ለውጥ ኢትዮጵያ ታወቂ ሆና አቅሟ እንዲጎለብት ያደረገ ትልቅ ሰው ነበር » ብለዋል።
የአካባቢ ጥበቃ ባለሙያው ዶክተር ተወልደ ብርሃንን ስራዎች «የምድራችን ጀግና» በሚል በመጽሀፍ ያሳተመው ደራሲ ዘነበ ወላ ዶክተር ተወልደ ብርሃን በብዙሃን ህይወት ሀብት ላይ አፍሪካን ወክለው በዓለም መድረክ ላይ ይቀርቡ ነበር ሲል ለዶቼ ቬሌ ተናግሯል፤ የሚያውቁትም ይሁን የማያውቁት ሰው ሲስቅ ማየት ከምንም ነገር በላይ ያስደስታቸዋል ያለው ደራሲ ዘነበ፤ የብዙዎች አባት ነበሩ ሲሉ ስለአገራቸው የነበራቸውን ስሜት በዚ መልክ አጋርተውናል።
«ከምንም ነገር በላይ የሚያሳስበው የኢትዮጵያ አንድነት ነው» በጣም ብዙ ስራዎች ሰርተዋል ከነዚህ መሀከል ይላሉ ደራሲው «ኢትዮጵያ ከማዳበሪያ ገበያ ነጻ የሆነች አገር ለመፍጠር ያለፉትን 30 ዓመታት ጥረት አድርገዋል። ሌላው የማህበረሰብ መብት ና የዓለም አርሶ አደሮች መብት ላይ ነው በብዙሀን ህይወት ላይ የባለቤትነት መብት ማውጣት ጀምረው ነበር ሌላው ሰው የፈጠረው ቁሶች ላይ ማውጣት ይቻላል በህያውያን ላይ ግን ማውጣት ገበሬውን እንደሚጎዳው ስለሚያውቅ ባደረገው ከባድ ክርክር ለውጤት አብቅቷል » ብለዋል።
ያስገኙትን ውጤት ሲናገሩ « በዓለም ላይ ከ1 ነጥብ 4 ቢሊዮን በላይ አርሶ አደሮችን የዘር መብት ባለቤትነታቸውን አረጋግጠዋል» ብለዋል። ደራሲ ዘነበ ወላ ለበርካቶች አባት እና መጠለያ የነበሩት ዶክተር ተወልደ ብርሃንን የሕይወት ጉዞ ዙሪያ ዳጎስ ያለ መጽሐፍ አሳትመዋል ብለዋል።
ዶክተር ተወልደ ብርሃን የዩናይትድ ኪንግደም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን ጨምሮ በተለያዩ መድረኮች በመገኘት አካባቢ ጥበቃና ሥነ ህይወት የተመለከተ ንግግሮችን አድርገዋል በርካታ ስራዎችንም ለዓለም አበርክተዋል ያሉት ፕሮፌሰር እንዳሻው በቀለ፤ ዶክተር ተወልደ ብርሃን ሳይንሱን በአገራችን ለማበልጸግ ትልቅ ስራ ሰርተዋል ይላሉ። «ሳይንሱን ለማበልጸግ ትልቅ ስራ ነው የሰራው። ትልቅ ሰው ነው። ብዙ የሰራ ሰው ነው በፍሎራው በኢኮሎጂው፤ በቬጂቴሽን ለምሳሌ በደርግ ግዜ በጋምቤላ እና ዴዴሳ ኢኮሎጂው ቬጂቴሽን አሰርቷል ግን እሱ እንደሰራው አድርገን አይደለም የምንመለከተው ወይም ምናገናዝበው ሌላው በባዮ ቴክኖሎጂ ላይ በደንብ እውቀቱ ኖሮት ብዙ ስራዎችን እንዲሰራ ያደረገ ነው ለአገሩ በርካታ ስራዎችን ያበረከቱ ሰው ነው»
ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ከአካባቢ ጥበቃና ብዝሃ ህይወት ጋር የሚያያዝ ከ30 በላይ ጥናቶችን አሳትመዋል። በተመሳሳይ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ መጽሐፍትንም ጽፈዋል እንዲሁም በርካታ ዓለም አቀፍና የአገር ውስጥ ሽልማቶችን አግኝተዋል።
እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር 2000 ላይ ስዊዲን ስቶኮልም በአካባቢ ጥበቃ በነበራቸው አስተዋጽኦ አማራጭ (Alternative) የኖቤል ሽልማት የወሰዱ ሲሆን በ2006 ሲንጋፖር ላይ (champion of the earth) የሚል ሽልማትን ከመንግሥታቱ ድርጅት ተበርክቶላቸዋል።
በዶ/ር ተወልደብርሃን ሕይወት ማለፍ ሐዘኑን ለአሜሪካ ድምጽ የገለፀው የግለታሪካቸው ጸሐፊ ዘነበ ወላ፤ “በአገሩ፣ በወገኑ እና በራሱ ማኅበረሰብ ጥሩ አስተዋፅኦ ካደረጉ እና ተጠቃሽ ከሆኑ ኢትዮጵያውያን አንዱ ነው። ዓለም ለወደፊት ስለ አካባቢ ጥበቃ አሳቢዎቿ በምትፅፍበት ጊዜ ከአውራዎቹ አንዱ ዶ/ር ተወልደ ይሆናል። ” ብሏል።
በማስከተልም፤“ዶ/ር ተወልደ አንተን የሚተካ ሰው ፈጥረሃል ወይ ብዬ ስጠይቀው፣ እኔ መተካት አለብኝ ብዬ የማስብ ሰው አይደለሁም፣ ማስተማር እኮ ራስህን መተካት ነው” ብሎኛል። የዶ/ር ተወልደብርሀን ሀሳብ ተሰሚነት አግኝቶ ቢተገበር ኖሮ፣ ዛሬ ኢትዮጵያ ለማዳበሪያ ግዢ በቢሊዮን የሚገመት ወጪ አታወጣም ነበር። ” ብሎናል።
ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ገብረ እግዚአብሄር ከእናታቸው ከወ/ሮ ማእዛ ተወልደ መድኅን እና ከአባታቸው ከመምሬ ገብረ እግዚአብሄር ገብረ ዮሐንስ በሰሜን ኢትዮጵያ ትግራይ ክልል በአድዋ ከተማ አቅራቢያ በምትገኝ ይርባገረድ በተባለች አካባቢ የካቲት 12 ቀን፤ 1932 ዓ.ም ተወልደው በ83 ዓመታቸው መጋቢት 11 ሰኞ ለማክሰኞ አጥቢያ 2015 ዓ.ም አረፉ። የቀብር ስርአታቸው በአዲስ አበባ ከተማ የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ቤተ ክርስቲያን ባለፈው እሮብ ተፈጽሟል። ዶክተር ተወልደ የሦስት ሴት ልጆች አባት ነበሩ ።
ዓለማቀፉ የሰላም፣ የእርቅ ፣ የሽምግልናና የግልግል ረቡኒ/ መምህር / ፕሮፌሰር ሕዝቅያስ አሰፋ ዘላቂ ሰላም እውን እንዲሆን ሰው በመጀመሪያ ከፈጣሪ ጋር ከዚያ ከራሱ ጋር በማስከተል ከተፈጥሮ ጋር ሰላም፣ እርቅ ማውረድ አለበት ይላሉ ። ከተፈጥሮ ጋር ሰላም ለመፍጠር የሰው ልጅ ተፈጥሮን እንዳይኑ ብሌን መንከባከብ ይጠበቅበታል። ዶ/ር ተወልደብርሀን የሰውን ልጅ ከተፈጥሮ ጋር የሚያሸማግሉ፣ የሚያስታርቁ አባት ነበሩ።
ምንም እንኳ ስማቸው የኖቤል የሰላም ተሸላሚ እንደነበሩት ኬኒያዊቷ የአካባቢ ጥበቃ ተሟጋች ዋንጋሪ ማታይ ወይም የእናት ምድር ጠበቃ ስለሆነችውና ከልጅ እስከ አዋቂ ፣ ከሊቅ እስከ ደቂቅ ፣ ከአገር መሪ እስከ ተራው ዜጋ ፣ ከትምህርት ቤት የአካባቢ ጥበቃ ክበብ እስከ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በአጠቃላይ ከአፅናፍ እስከ አፅናፍ ስለ የአየር ንብረት ለውጥ ዓለማቀፍ ንቅናቄን እንደ አቀጣጠለችው፤ የኖቤል የሰላም አሸናፊ እጩ፤ የተወዳጁ TIME መፅሔት የ2019 ዓ.ም የዓመቱ ሰው ተብላ እንደተመረጠችው ስዊድናዊት ብላቴና ግሬታ ተንበርግ ባይዘመርላቸውም እናት ተፈጥሮ ግን ውለታቸውን መቼም ቢሆን አትዘነጋውም።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን መጋቢት 17 ቀን 2015 ዓ.ም