በቅርቡ በተካሄደው የኳታር ዓለም ዋንጫ ድንቅ አቋም ከነበራቸውና ለዋንጫም ይጠበቁ ከነበሩ ቡድኖች መካከል አንዱ የክሮሺያ ብሔራዊ ቡድን መሆኑ የሚታወስ ነው። በወቅቱ ክሮሺያ ቡድኗ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ ውድድሩን ሲፈጽም፤ ወደ ግማሽ ማጣሪያ ያለፈው በእግር ኳስ ታሪክ የደመቀና ግዙፍ ታሪክ ያላትን ብራዚልን በመለያ ምት ከውድድር ውጪ በማድረግም ጭምር ነበር። እግር ኳስ እጅግ እንዲወደድ ካደረጉት ምክንያቶች መካከል ይህ አንዱ ነው።
በብርቅዬው ዋልያ የተሰየመው የኢትዮጵያ ብሔራዊ እግር ኳስ ቡድን በአህጉረ አፍሪካ ታላቅ በሚባለው የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ለመካፈል የማጣሪያ ውድድሩን በማከናወን ላይ ይገኛል። ከውድድሩ ጥንስስ አንስቶ አህጉር አቀፉን የእግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን በማቅናት ከፍተኛ ሚና የነበራት ኢትዮጵያ ከመድረኩ ከራቀች ከዓመታት በኋላ መመለስ መቻሏ እግር ኳስ ወዳዱን የኢትዮጵያ ሕዝብ ማስደሰቱ አይካድም።
ዘንድሮም ዳግም በመድረኩ ተወዳዳሪ ለመሆን የማጣሪያ ጉዞውን በማላዊ ሽንፈት የጀመረች ቢሆንም ሽንፈቱን በቀናት ልዩነት ቀልብሳ ትልቅ ግምት የተሰጣት ግብጽ ላይ የሁለት ለምንም ጣፋጭ ድል ማጣጣሟ አይዘነጋም። ሶስተኛ የማጣሪያ ጨዋታዋን ደግሞ ዛሬ የጊኒ አቻዋን በገለልተኛ ሜዳ ሞሮኮ ላይ ትገጥማለች። ጊኒ ልክ እንደ ፈርኦኖቹ ሁሉ ትልቅ ግምት የተሰጣት አገር ብትሆንም እግር ኳስ ነውና የቀደመ ታሪክ ሳይሆን ጠንካራ የቡድን ስራ የዋሊያዎቹን ዓላማ ያሳካል የሚል ተስፋም በብዙዎች ዘንድ አድሯል።
በእርግጥ ኢትዮጵያ በስፖርቱ የሚጠቀስ ጠንካራ ስም የላትም፤ ነገር ግን እግር ኳስ እንደ ሀገር እጅግ ተወዳጅና ደጋፊውም ያለውን ሁሉ የሰጠው ስፖርት ነውና ዋልያዎቹ ትልቅ የሞራል ስንቅ ሁሌም አብሯቸው አለ።
አሁን ላይ ኢትዮጵያዊ ስሜትን ከሚያነቃቁ፣ አንድነታችንንም ከሚመልሱ ጉዳዮች መካከል አንዱ እግር ኳስ ነው። ለዚህም ከሁለት ዓመታት አስቀድሞ ካሜሮን አዘጋጅ በነበረችበት የአፍሪካ ዋንጫ የማለፋችን ብስራት ሲሰማ ያሳደረብንን አገራዊ ስሜት ማስታወስ በቂ ነው። በመሆኑም እንደቀደመው ጊዜ በረጅም ሳይሆን በአጭር ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፏችንን ለማረጋገጥ ለዚህ ማጣሪያ ውድድር ትኩረት መስጠት አለብን። የኢትዮጵያን ስኬታማ የእግር ኳስ ታሪክ ዛሬ ያውም አሁን ባለንበት ሁኔታ መጻፍ መጀመር እንችላለን።
ክሮሺያ ነጻነቷን ባወጀች ማግስት ነበር ብሔራዊ ቡድኗ እውቅና ያገኝላት ዘንድ ፌዴሬሽን አዋቅራ የአህጉርና ዓለም አቀፉን እግር ኳስ ለሚመሩት አካላት ጥያቄዋን ያቀረበችው። ከሶስት ዓመት በኋላም እአአ 1996 የአውሮፓ ዋንጫ የዋንጫ ተፋላሚ በመሆን ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ አጠናቀቀች። ከሁለት ዓመት በኋላ ደግሞ ፈረንሳይ ባዘጋጀችው የዓለም ዋንጫ የመጀመሪያውን ተሳትፎ በማድረግ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ በማጠናቀቅ የውድድሩ ክስተት ለመሆን በቃች። በመሃል ጥቂት ብትዳከምም በ2018 የሩሲያ የዓለም ዋንጫ በድጋሚ ክስተት የሆነ ቡድኗን ይዛ በመቅረብ፤ በፈረንሳይ ተሸንፋ ለጥቂት ዋንጫው አመለጣት። በኳታርም ከአስፈሪ ቡድኖች መካከል አንዱ ነበር። እኛም ከዚህ መማር አለብን።
በማጣሪያው ሁለተኛ ጨዋታ ኢትዮጵያ በሰባት የአፍሪካ ዋንጫዎች የተንቆጠቆጠችውንና ከአህጉሩ ጠንካራ የእግር ኳስ ቡድኖች መካከል አንዷ ከሆነችው ከግብጽ በተገናኘችበት ወቅት፤ የተመዘገበው ውጤት የፈጠረው መነቃቃት የሚታወስ ነው። ይህ የሆነው ቡድኑ ባደረገው ርብርብ እንደመሆኑ፤ አሁንም ስህተቶቹን በማረም መጫወት ይጠበቅበታል። ጥሩ እግር ኳስን ከመጫወት አቅም ባለፈ አሁን ላይ ለሽንፈትና ውጤት ማጣት በስፋት የሚነሳው የሜዳ ጉዳይም በዚህ ማጣሪያ እንከን ሊሆን አይገባም። በእርግጥ በራስ ሜዳ፣ በሚያውቁት የአየር ሁኔታ ውስጥ በደጋፊ ታጅቦ መጫወት በራስ የመተማመን ስሜትን ይፈጥራል። ከእነዚህ ሁኔታዎች ርቆ መጫወትም የራሱ ተጽእኖ እንዳለው የማይካድ ሃቅ ነው።
አሰልጣኝ ውበቱ አባተ ዋሊያዎቹን ወደ መምራት ከመጡበት ጊዜ አንስቶ ሀገራቸው ላይ ያደረጓቸው ዓለም አቀፍ ጨዋታዎች አራት ብቻ ናቸው። የተቀሩትን ጨዋታዎች በሙሉ ከኢትዮጵያ ውጭ በውሰት ሜዳዎች ላይ አከናውነዋል። ይህ ምናልባትም አስቸጋሪ ሁኔታ ሊመስል ይችላል፤ ይሁንና ዋሊያዎቹ በዚህ መልኩ እየተጫወቱ ከስምንት ዓመታት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ እንዲሁም ከስድስት ዓመታት በኋላ ወደ ቻን (ምስራቅና መካከለኛው አፍሪካ ዋንጫ) ማለፍ ችለዋል። በመሆኑም ቡድኑ ችግሮቹን ብቻም ሳይሆን መልካም ሁኔታዎችንም በመጠቀም አንጻራዊ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን ነው። አሁንም እንደ አዲስ የሜዳ ችግርን እና ከደጋፊ መራቅን እንደ ምክንያት ከማስቀመጥ ይልቅ በምን መልኩ ውጤት ሊመዘገብ ይችላል የሚለውን እያሰቡ መጓዝ ውጤታማ ሊያደርግ ይችላል።
ከሶስት አስርት ዓመታት ያልበለጠ እድሜ ያላት ትንሿ ሀገር ክሮሺያ ከዩጎዝላቪያ ተነጥላ ነጻነቷን ለማወጅ ከአራት ዓመት በላይ ጦርነት ውስጥ ቆይታለች፤ ዜጎቿም ተሰደው ነበር። ይሁንና ያለፉትን መጥፎ ጊዜያት በማሰብ ሳይሆን ሀገርን የሚያኮሩ የእግር ኳስ ተጫዋቾችን በማፍራት ላይ ማተኮሯ ትልቅ የእግር ኳስ አገር አድርጓታል። ክሮሺያዊው የስፖርት ጋዜጠኛ ስርዳን ፋቢጃንክ ‹‹እግር ኳስን ያገኘነው በደም ነው። ምንም እንኳን ትንሽ ሀገር ብንሆንም ሁሌም የእግር ኳስ ቡድናችን ካለበት ልቆ እንዲገኝ ጥረት እናደርጋለን። ብሔራዊ ጀግኖቻችን የሆኑት ተጫዋችም ያላቸውን ኃይል አሟጠው ነው የሚጫወቱት›› ሲል በአንድ ወቅት ተናግሮ ነበር።
በእርግጥም አንድ ቡድን ጠንካራ አሊያም ስኬታማ ነው ሊያሰኙት ከሚችሉት ነገሮች መካከል አንዱ ራስን ከሁኔታዎች ጋር አስማምቶ መገኘቱ ነው። የቡድኑ አባላት እንደ ክሮሺያዊያን ለየትኛውም ጨዋታ ትኩረት በመስጠትና ኢትዮጵያን ብቻ በማሰብ የአሸናፊነት ስነልቦናን ተላብሶ መሰለፍ ያስፈልጋል። ምድቡን እየመራ የሚገኘው ቡድኑ በቀጣይ የሚኖሩት ጨዋታዎች እየጠነከሩበት እንደሚሄዱ ግልጽ በመሆኑ ከወዲሁ ነጥቡን በማስጠበቅ ለአምስተኛና ስድስተኛ ጨዋታዎች ምቹ መደላድልን መፍጠር አስፈላጊ ነው።
በበርካታ ቡድኖች መልበሻ ቤት የሚስተዋለው አላስፈላጊ ሁኔታ በክሮሺያ ብሔራዊ ቡድን ቦታ እንደሌለው ጋዜጠኛው ፋቢጃንክ ይገልጻል። አንድም ሰው ከቡድኑ በላይ ሊሆን እንደማይችልና ሁሉም በስርዓት እንደሚከናወንም ይጠቁማል። ሀገርን በሚመለከት ጉዳይ የትኞቹም ግላዊ ሁኔታዎች ቦታ የላቸውም። ከቻን ውድድር አንስቶ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጫዋችና አሰልጣኙ መካከል የተስተዋለው ሁኔታም መፈታት የሚገባው ነው።
ብሔራዊ ቡድን ከሀገር መከላከያ ሊለይ የሚችለው በሚውሉበት አውድ እንጂ ግልጋሎታቸው የሀገርን ስም ማስጠራት እስከሆነ ድረስ ማንኛውም ተጫዋች የቀረበለትን ጥሪ አክብሮ በተጠንቀቅ ሊቆም ይገባዋል። በአንጻሩ ኢትዮጵያን የሚያህል ሀገር ተሸክሞ የሚጫወትን ቡድን የሚመሩት አሰልጣኝ ስርዓት እንዲከበር ማድረጋቸው የሚያስመሰግናቸው ተግባር ሆኖ ሳለ ሆደ ሰፊ መሆንም ይጠበቅባቸዋል። አንድነትና ትልቅ አገራዊ ስሜት መፍጠር ከቻሉም በየትኛውም ቡድን በእግር ኳሳዊ ምክንያት ተበልጠው እንኳን ስኬታማ ሊሆኑ የሚችሉበት እድል ይኖራል። ለዚህም ሁሉም ኢትዮጵያዊ ከዋልያዎቹ ጎን ቆሞ በሞራል ሊደግፍ ይገባል።
ብርሃን ፈይሳ
አዲስ ዘመን መጋቢት 15/2015