(የመጨረሻ ክፍል)
እንደማንኛውም ግዙፍና አጓጊ ፕሮጀክት የጄምስ ዌብ የህዋ ቴሌስኮፕም በብዙ ውጣ ውረዶችና ፈተናዎች አልፏል ትለናለች ናዲያ፤ የተያዘለት በጀት በ20 እጥፍ ማደጉ፣ በስምንት ዓመት ይጠናቀቃል ሲባል 30 ዓመት መውሰዱ፤ ከመነሻ ሀሳቡ፣ ዕቅዱ፣ ዲዛይኑ፣ ግንባታውና እስከመጠቀበት ጊዜ ድረስ እውን ይሆን በሚል በጥርጣሬ ያዩት የነበሩ፤ ተቋማት፣ ፖለቲከኞች፣ ሊቃውንት፣ ወዘተረፈ ቁጥርም ቀላል አልነበረም። የሀብል ቴሌስኮፕም ተመሳሳይ እጣ ገጥሞት ነበር ስትል ታስታውሰናለች ጸሐፊዋ።
በዌብ ቴሌስኮፕ ንድፍ የተሳተፈው ጆን ኦሚያራ፤ ሲያጉረመርሙ የነበሩ ሁሉ የዌብን የመጀመሪያ የህዋ ምስል ሲያዩ ይረሱታል እንዳለው፤ ዛሬ ሕዝበ አዳም ሲያዘንበው የነበረውን ያን ሁሉ ትችት እረስቶ ቃላት እስኪያጥረው አድናቂ ሆኖ አርፎታል። አጽናፈ ዓለም እጅጉን ረቂቅ፣ ጥልቅ፣ መጀመርያ እና መጨረሻ የሌለው አልፋ እና ዖሜጋ ነው። የምድርን ግዝፈት፣ የተፈጥሮ ረቂቅነት፤ እየኖርንባት፣ እያየናት፣ እየጨበጥናት፣ እያሸተትናት እና እየቀመስናት በእርግጥ ገና በቅጡ አላወቅናትም ይለናል የጀርመኑ ሬዲዮ ዶቸ ቬሌ ደግሞ።
ይህ በእንዲህ እያለ ታዲያ እንዴት ተደርጎ ከእኛ በብርሃን ዓመታት ርቀው የሚገኙ ዓለማትን መመርመርስ ይቻለናል፤ ለዚያውም መቶ ሚሊዮን ዓመታትን ወደ ኋላ ተመልሶ ፍጥረተ ዓለምን ለማወቅ በውኑ ይቻላልን ? የሚሉ ጥያቄዎች ከዚህም ከዚያም እየተነሱ ነው። ጋዜጠኛ እና የስነፈለግ ተመራማሪ የሆነችው ኤልሳቤት ቤርሶን በበኩሏ በጀምስ ዌብ ላይ ያላትን ምልከታ ስትናገር፤ በእድሜዬ የሰው ልጅ በጠፈር ምርምር ረገድ ያሳየውን እመርታ ማየት ችያለሁ። ቴሌስኮፑ እየላካቸው ያሉ ምስሎችም ለዚህ ምስክሮች ናቸው። ሰዎች በዙርያቸው ባለው ሕዋ ውስጥ ምን እየተካሄደ እንዳለ የማወቅ ጉጉታቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ባለበት ሰዓት ቴሌስኮፑ መምጠቁ ጥሩ አጋጣሚ ነው ትላለች።
በ18 ጠንካራ እና ግዙፍ ወርቃማ መስታወቶች የተሠራችው እና እንደ ጎርጎርሳዊው አቆጣጠር፤ ከ1961 እስከ 1968 የአፖሎ 11ን የህዋ ጉዞ ተልዕኮ በመራው ጀምስ ኤድዊን ዌብ ስም የተሰየመው ቴሌስኮፑ፤ በአንድ ነጸብራቀ ምስል ተቀባይ መሳርያ አማካኝነት እጅጉን ርቆ ምናልባትም እስካሁን ከተደረሰባቸው መረጃዎች፤ አንድ እርምጃ የተራመደ መደምደሚያ ላይ ሊያደርሱ የሚችሉ መረጃዎችን ይሰበስባል ተብሎ ተስፋ ተጥሎበታል።
ጀምስ ዌብ በህዋ ውስጥ የሚደርስበትን ሙቀት ቅዝቃዜ፤ ግጭት ተቋቁሞ ሚሊዮን ኪሎ ሜትሮችን አቆራርጦ ስፍራውን ይዟል። የወዲያኛውን ዓለም አቅርበው ለማየት የቋመጡ የሰው ልጅ ዓይኖች በቴሌስኮፑ ዓይኖች ላይ ተስፋቸውን ጥለዋል። በአጽናፈ ሰማያት መሐል ባለችው ትንሿ መሬት ላይ ብቻችንን ነን ወይስ እኛ የማናውቃቸው ሰማየ ሰማያትን ተሻግረው ሌሎች ይኖሩ ይሆን ? የሚለውንና ከፍ ብሎ የተጠቀሱ ጥያቄዎችን ይዞ ጉዞውን ያጠናነቀው ቴሌስኮፕ ምላሽ ይኑረው አይኑረው ወደፊት የሚታይ ነው።
ቀናት ፣ ወራት ምናልባትም ዓመታት ልንጠብቅ ግድ ሊለን ይችል ይሆናል። ደግሞስ ማን ያውቃል፤ ይሄ ትውልድ የጠየቀው ጥያቄ መልስ ሳያገኝ ትውልድ ሄዶ ትውልድ ሊመጣ ይችላል ይለናል ዶቸ ቬሌ። ግዙፉ ቴሌስኮፕ በጠፈር ላይ ያሉ ከዋክብትን ይቃኛል። ይመረምራል። የማይታወቁ ፕላኔቶች ያስሳል። ከምድራችን ውጭ በሌላ ፕላኔት ህይወት ያለው ነገር መኖሩን ወይም ለሰው ልጅ መኖሪያ ሊሆን የሚችል ሌላ ፕላኔት እንዳለ ይፈትሻል ይለናል የእንግሊዙ ዜና ማሰራጫ ቢቢሲ።
በአይነቱ የመጀመሪያ የሆነው የዌብ ቴሌስኮፕ በአጽናፈ ዓለም እስከ ዛሬ ያልታዩ አዳዲስ ጋላክሲዎችንና ፕላኔቶችን ያገኛል ተብሎ ይታመናል። ይህ ጹሑፍ እየተጠናቀረ ባለበት እንኳ በረዷማ የሆነ ጭጋግ እና ካርበን ዳይኦክሳይድ መገኘቱ እየተነገረ ነው። አጽናፈ ዓለም በታላቅ ፍንዳታ/ቢግ ባንግ/ ነው የተፈጠረው የሚለውን ሳይንሳዊ ንድፈ ሀሳብ የሚያጠነክር ወይም የሚቃረን ፍንጭ ይሰጣል የሚል እምነትም ተይዟል።
የጄምስ ዌብ ቴሌስኮፕ ከትሮፒካል ሬይን ፎረስት ተነስቶ አጽናፈ ዓለም ተፈጥሮበታል ተብሎ በሳይንቲስቶች የሚታመንበትንና፤ የሁሉ ነገር መጀመሪያ የሆነውን ቢግ ባንግ በቅርብ መመርመር ወደ ሚያስችልበት የህዋ አካል መጥቋል ይላል ቢቢሲ። የጄምስ ዌብ የጠፈር ቴሌስኮፕ ዋና ዋና ዓላማዎች ፤ የመጀመሪያው ከቢግ ባንግ በኋላ በአጽናፈ ዓለም/ዩኒቨርስ/ ውስጥ የተፈጠሩትን፤ የመጀመሪያዎቹን ከዋክብትና ጋላክሲዎች ይመረምራል። ሁለተኛው የጋላክሲዎችን አፈጣጠር እና ዝግመተ ለውጥ ማጥናት እና፤ የፕላኔቶችን ስርዓቶች እና የህይወት አመጣጥን ማጥናት ሶስተኛው ይገኝበታል።
ቴሌስኮፑ እስካሁን ከተገኙ እጅግ በጣም ርቀው የሚገኙትን ሁለቱን ጋላክሲዎች ከማስመልከቱ ባሻገር፤ የጄምስ ዌብ የጠፈር ቴሌስኮፕ ከቢግ ባንግ በኋላ ከተፈጠሩት የመጀመሪያዎቹ ጋላክሲዎች አንዱን አሳይቷል። ቴሌስኮፕ በ32 ሚሊዮን የብርሃን ዓመታት ርቀት ላይ“የ ghost ጋላክሲን”ምስል ከማንሳቱ ባሻገር አዳዲስ ግኝቶችን ይፋ እያደረገ ነው ይለናል የእንግሊዙ የዜና ማሰራጫ ቢቢሲ።
በነካ እጃችን አጠቃላይ የሰውን ልጅ አኗኗር ፍጹም ሊቀይር ስለተዘጋጀው እና ሌላው የ21ኛው መክዘ ክስተት ስለሆነው በ2030 እኤአ ለዓለም ኢኮኖሚ 15 ትሪሊየን ዶላር ይጨምራል ተብሎ ስለሚጠበቀው የሰው-ሰራሽ ክህሎት ወይም አስተውሎት በዚያ ሰሞን ለንባብ የበቃው የTIME መጽሔት የሰው ልጅ ላለፉት 300,000 ዓመታት ኑሮውን ያቀለሉ ፈጠራዎችን ሲያከናውን የመጣ ቢሆንም ሰው ሰራሽ አስተውሎት ግን ወደ አዲስ ምዕራፍ እያሸጋገረው ነው ይለናል። ስዕል መሳል፣ ለኢሜላችን መልስ መስጠት፣ የታክስ ክፍያዎቻችንን፣ የጤና የምክር አገልግሎት፣ እንደ ተማሪ ፈተና ይቀመጣል፣ መጣጥፍ ይጽፋል፣ ወዘተረፈ አይነት አገልግሎቶችን እየሰጠ ይገኛል።
አርቲፊሻል ኢንተለጀንት (AI) ፦ ከሰው ልጅ አስተሳሰብ ባህሪዎች ጋር ተመሳሳይ የስራ አይነቶችን መፈፀም ችሎታ ያለው ውቅርን የሚያመለክት በውስጡ ሰፊ ሀሳብ ያለበት ሀረግ ነው ። ከጥንት ጊዜያት ጀምሮ የሰው ልጆች አንዳንድ እንደነዚ አይነት ክህሎት የማበልፀግ ፍላጎት ነበራቸው። የዘመናዊ ሳይንስ ማደግ ጋር ተከትሎ፤ የ AI ፍለጋው በሁለት ዋና ዋና አቅጣጫዎችን ወስደውታል: ሥነ ልቦናዊ ጥናት (psychological) እና ፊዚዮሎጂ (physiological) ጥናት በሰው አስተሳሰብ ተፈጥሮ፣ እና እንዲሁም ከጊዜ ወደ ጊዜ ይበልጥ የተራቀቁ የኮምፒዩተር ሥርዓቶች የቴክኖሎጂ እድገት ተፈጠረ። በሌላ አገላለፅ የ AI ቃል ትክክለኛውን የሰው አስተሳሰብ እውቀት አኳያ የራቀ ቢሆንም እንኳን ቀጥተኛ ከሆኑት ፕሮግራሚንግ የበለጠ ውስብስብ ተግባሮችን መፈፀም የሚችሉ የኮምፒውተር ስርዓቶች እና ፕሮግራሞች ላይ ተግባራዊ የሚሆን ነው።
በዚህ መስክ በጣም አስፈላጊው የምርምር ዘርፎች ውስጥ የመረጃ ማቀነባበር ሂደት፣ የንድፍ ቅደም-ተከተሎችን መረዳት፣ የኮምፒውተሮች ጌም-መጫወቻ (game-playing) እና ተግባራዊ መስኮች እንደ የሕክምና ምርመራ የመሳሰሉት ናቸው። በመረጃ ማቀነባበር አሰራር ሂደት አሁን ያለው ጥናት ኮምፒውተር አንድን የተጻፈ ወይም የንግግር መረጃን እንዲረዳ እና አጭር ማጠቃለያዎችን እንዲያደርግ፣ የተወሰኑ ጥያቄዎችን እንዲመልስ ወይም የዚህን መረጃ የተወሰኑ ስፍራዎች ውስጥ ለሚፈልጉ ተጠቃሚዎች መረጃን በሚያሰራጭ ፕሮግራሞች ላይ ያቀርባል።
ለእንደዚህ ያሉ ፕሮግራሞች እጅግ ወሳኝ የሆነው የስርዓቱ አቅም ሰዋሰዋዊ አረፍተ ነገሮች እንዲፈጠሩ እና በቃላት፣ ሀሳቦች እና ከሌሎች ሀሳቦች መካከል ትስስሮችን ለመመስረት ነው። ጥናቶች እንደሚያመለክቱት የቋንቋ ሎጂካዊ አወቃቀር ለፕሮግራሙ የተሰጠው —የቃላት አገባብ—በዓረፍተ-ነገሩ ውስጥ፣ የትርጉም ችግር፣ ወይም የስነ-ፍቺ ጥናቶች (Semantics)፣ በእውነተኛው AI አቅጣጫ ውስጥ፣ በጥልቀቱ እርቀው የተቀመጡ ናቸው።
በሕክምናው ውስጥ፣ የበሽታ ምልክቶች፣ የህክምና ታሪክ፣ እና የታካሚውን ላቦራቶሪ ምርመራ ውጤቶች የሚተነትኑ፣ እና ከዚያም ለሐኪሙ የምርመራ ውጤትን የሚያመላክቱ ወይም ሀሳብ የሚያቀርቡ ፕሮግራሞች ተዘጋጅተዋል። የምርመራው ፕሮግራም እንደ ልዩ ባለሙያተኛ የሰው ልጅ የሆነበት መስኮች ውስጥ ልዩ ልዩ ስራዎችን ለማከናወን የተነደፉ ኤክስፐርት ስርዓቶች (Expert Systems) ተብሎ ለሚጠሩት ምሳሌ ናቸው።
የኤክስፐርት ስርዓቶች ኮምፒውተሮችን ከቀጥተኛ የፕሮግራሚንግ ስርዓት ባሻገር ባለ ደረጃ ላይ ይወስዱታል፣ ከመረጃዎች በመነሳት የሚወሰን ህገ-
መሰረት (rule-based inference) ተብለው የሚጠራ ቴክኒክ ላይ መሰረት ያደረገ፣ ዴታን ለማቀነባበር የሚጠቅሙ ቀድሞ የተመሰረቱ የህግ ስርዓቶች ናቸው። እጅግ የተራቀቁ ቢሆኑም፣ ስርዓቶች አሁንም የእውነተኛውን የማሰብ ችሎታ ውስብስብ እውቀት ላይ ገና አልቀረቡበትም።
በርካታ የሳይንስ ሊቃውንት እውነተኛ AI ን ሊፈጠሩ እንደሚችሉ ጥርጣሬ አላቸው። የሰው ልጅ አእምሮ አሰራር ላይ ያለው ግንዛቤ አሁንም ገና አነስተኛ ነው፣ እና የኮምፒውተር ንድፍ የማይታወቁ እና ውስብስብ ሂደቶችን በተመሳሳይ ሁኔታ አመሳስሎ ለመተግበር ምን አልባት የአቅም ገደቦች አሉበት። የእውነተኛ AI ግብ ላይ ለመድረስ የተለያዩ መንገዶች በጥቅም ላይ እየዋለ ነው። አንዱ አቀራረብ ትይዩ የአሰራር ሂደት-አገናኝ እና ባንድ ጊዜ ጥምር የኮምፒውተር ተግባሮች የሚለውን ጽንሰ-ሀሳብ ተግባራዊ ማድረግ ነው። ታሪካዊ ዳራውን በአለፍ ገደም እንመልከት።
ትውልደ እንግሊዛዊው አሜሪካዊ ፈላስፋ ቶማስ ፔይን በ18ኛው ክፍለ ዘመን እንደ ነብያት ቀድሞ ተገልጦለት ኖሮ፤ ” አዲሱን ዓለም ልናዋልድ እየተዘጋጀን ነው። ” ብሎ ነበር፤ ያለውም አልቀረም። አሜሪካ የአዳዲስ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ የፈጠራ ምድር በመሆን አዲሱን ዓለም፤ 3ኛውን የኢንዱስትሪ አብዮት ስትገላገል፣ ስትወልድ፤ በተቃራኒው አውሮፓ ግን እንደ ባዝራ መካን ከመሆኗ ባሻገር በጥልቅ እንቅልፍ ላይ ናት። ሲል ይሳለቃል ተነባቢው የየካቲት ወር መጨረሻ ዕትም The Economist መፅሔት፤ ይህ የአውሮፓ ድንዛዜ የሚገለፀውም በቴክኖሎጂ ዘርፍ ባስመዘገበችው ውጤት ነው።
ዛሬ በዓለማችን ቀዳሚ ከሆኑ 20 የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ኩባንያዎች 15ቱ በአሜሪካ መገኘታቸው በአውሮፓ ግን አንድ ብቻ መሆኑ ለዚህ ጥሩ ማሳያ ነው። የአሜሪካው ሲሊካን ቫሊ የዓለማችን ባለ ምጡቅ አእምሮ የፈጠራ ሰዎችና ባለሀብቶች ሁል ጊዜ የሚቃጠሩና የሚገናኙበት ነው። በሲሊካን ቫሊ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ዘርፍ በየ6 ደቂቃው አዲስ ነገር ይፈጠራል። በሰዓት ሲሰላ 10፣ በቀን ሲመታ 240፣ በዓመት 87ሺህ 600 አዳዲስ ፈጠራ ማለት ነው። (እዚህ ላይ ለአፍታ አገራችን የምትገኝበትን ተጨባጭ ሁኔታ በምናብ አብራችሁኝ አሰላስሉና በመንፈሳዊ ቅናት እንድትንጨረጨሩ በአክብሮት እጋብዛለሁ …!? ) ታዲያ … ! አሜሪካ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ምድረ ገነት ብትባል ይበዛባታል !? እረ ! በጭራሽ። በዓለማችን የመጀመሪያው የትሪሊዮን ዶላር ጥሪት አፕል መሆኑንም ይገነዘቧል።
ሆኖም አሜሪካ እነዚህ ኩባንያዎቿ የገመና* መብት the right of privacy እና የገበያ ውድድርን እንዲያከብሩም እየሰራች ነው። ፌስ ቡክ ገበያውን በበላይነት ስለተቆጣጠረ ወደ ትናንሽ ካምፓኒዎች መከፋፈል አለበት በማለት የምርጫ መቀስቀሻ እስከማድረግ ተደርሷል። የአውሮፓ ሕብረትም እጁን አጣጥፎ አልተቀመጠም። በ50ዎቹ IBM፣ በ80ዎቹ Micro Soft በምዕራባውያን ገበያን በበላይነት በመቆጣጠር monopoly እንደከሰሳቸው ሁሉ፤ ባሳለፍነው ወር ጉግልን የማስታወቂያ ነፃ የገበያ ውድድርን በማስተጓጎል የአውሮፓ ህብረት የ1 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ቅጣት አከናንቦታል። ሕብረቱ በዚህ አያበቃም። በቀጣይ የቅጅ መብትን Copy Right፣ ዜጎች የግል መረጃቸው ባለቤትና የጥቅም ተጋሪ እንዲሆኑም እየሰራ ነው።
ሻሎም !
አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን መጋቢት 12/2015