ዛሬ፣ አገር ማለት . . . ለማለት የመፈለጌን ምስጢር ላመስጥር። እነሆኝ ጀምሬያለሁ . . . አገር ማለት በደምና በአጥንት የሚያቆሟት፤ ዋጋ ከፍለው፣ አኑረው የሚኖሩባት ስለመሆኗ ከዓድዋ ጀግኖች የተማርኩት በመኖሩ ነው «አገር ማለት» ለማለት የፈለኩት። ስንት ወገን ወድቆ፣ ስንት ደም ፈሶ፣ ስንት አጥንት ተከስክሶ፤ በክብር፣ በኩራት እንድንቆም ያደረጉንን ጀግኖች መዘከሪያ ወርሃ የካቲት እንደሆነ ስሰማ አገር ማለት ለማለት ወደድኩ።
አገር ማለት ለእኔ የተወለድኩበት ቦታ አይደለም። ድሄ፣ ዳዴ ብዬ ያደኩበት አፈር፤ አገር ማለት ለእኔ እትብቴ የተቀበረበትም አይደለም። ገና ከእናቴ ማህፀን ስወጣ ከለቅሶ ጋር የተነፈስኩት አየር፤ አገር ማለት ለእኔ ሌሎቹ እንደሚሉት ነፍስና ስጋ ነው – ሰው የሚሉት ቃል በፍቅር በአብሮነት በትብብር የሚኖርበት። አገር ማለት ለእኔ ከሳር ከቅጠሉ፣ ከጋራ ሸንተረሩ . . . ከሁሉም ይልቃል። ሰው የመሆን ምስጢር፤ ሰው የመሆን ዋጋ ዓድዋ ላይ ተከፈሎ ውድ የሆነው ደም እንደ ውሃ ፈስሶ ሌሎችን ቀና አድርጓል።
አገር ማለት ለእኔ ታሪክ ነው። ትዝታ፣ ከምዕተ አመት በፊት የተሳለ ሥዕል፤ የተወራ ትውፊት፤ የተቀመጠ እውነት በዓድዋ ተራራ ላይ በጀግኖቹ ደጃፍ ጨርቄን ማቄን ሳይል ልጅና ምሽቱን አስከትሎ የሄደው ሰው ያኛው ነው አገሬ፤ ዘርና ብሔር ሳይቆጥር፤ የማነህ፣ ከየት ነህ ያልተባባለበት፤ ሙስሊም፣ ክርስቲያኑ የሰው መሆን ትርጉም በደማቅ ቀይ ቀለም፤ ሊያውም በደም ሥዕል በዓድዋ ሸራ ላይ ላይደበዝዝ ደምቆ የተሳለበት ነው – አገር ማለት ለእኔ።
ከእናቴ ማህጸን የወጣሁበት ቀን፤ የሰማኋቸው ድምፆች፤ የእልልታው ድምቀት እሱ ነው አገሬ፤ ከእማማ ጊደይ ፈንድሻ፤ ከእትዬ መሪም የወሎ ጢስ፤ ከአዴ ጫልቱ ቤት መጥቶ እናቴ አናት ላይ የተቀመጠው ትኩስ የተናጠው ቅቤ፤ ከጎረቤቶቻችን ጋር ገንፎ ሲቋደሱ የነበረበት አንድ ትልቅ መአድ፤ ሁሉም ከበው በደስታና እልልታ አብሮ የሚቋደሰው . . . አገር ማለት ለእኔ አብሮ የሚኖር ሰው ነው።
አገር ማለት ለእኔ ትምህርት ቤት ሲሄድ የፊደል ገበታ ላይ ያየኋት ካርታ ናት፤ አገር ማለት ለእኔ ወደ ጎን ወደ ታች በቀጥታው መስመር የተፃፈው ፊደል ሳየው የሚያየኝ፤ ሳይገባኝ የማየው፤ በየኔታ ቅኝት ሀ…ሁ…ሂ.. ብዬ የቆጠረኩበት ዛሬ ላይ ቆሜ የእኔነቴ አሻራ በሌሎች መነፅር ምን እንደሚመሰል ከመጽሐፍ የማይበት፤ አገር ማለት ለእኔ ከየቤቱ መጥቶ በአንድ የተጋመደው፣ የእነ እገሌና የእነ እገሊት ልጅ ሳይባል በአንድ ቋንቋ የሚያወራው፣ የየኔታን ደጃፍ የረገጠው የልጆች እግር ነው።
አገር ማለት ለእኔ ከጓዴ ጀሚ ጋር አብረን የፆምነው የረመዳን ፆም ነው። የእኔ አገር ማለት የስቅለት ሰሞን ስግደቱን ላግዝሽ የተባባልንበት፤ እኔ ቁርሴን ካልበላሁ እሷ የምትተውበት፤ አገር ማለት ለእኔ በስጋ እንዳንለያይ ብዙ በዓላትን በስልስና እንቁላል አብረን የምናከብርበት፤ የጓደኝነት ገመድ ያስተሳሰረንን፣ እኔና ጀሚላን ያየዘን ፍቅር የሚገለፅበት፤ የጠዋቱን ስግደት ልትሰግድ ስትነሳ እኔንም ቀስቅሳ «በይማሪያም ሂጅና ቶሎ ተመለሽ፤ ቁርስ እንዳይረፈድብን» የተባባልንበት፤ የዩኒቨርሲቲ ግቢ . . . ለእኔ አገሬ እሱ ነው – ትንሿን ኢትዮጵያ የማይበት።
አገር ማለት ለእኔ ቋንቋ ነው፤ በአፍ የማይሉት በእዝነ ህሊና ብቻ የሚደመጥ አማርኛ፣ ኦሮምኛ፣ አፋርኛ፣ ቅማንትኛ፤ ጉራጊኛ ወይ ትግርኛ፣ የሚል ስም የሌለው በፍቅር ቋንቋ ብቻ አንድ የመሆን ዋጋ፤ የአንድ መቀመጫ፣ የአንድ መኖሪያ፣ የአንዱ መቀበሪያ፤ በመኖሯ ብቻ ፍቅርንም ፀቡንም የምናደርግባት ናት፤ የሁሉ እናት ጀርባ ሁሉን አዝላ ያለች አገር ማለት ለእኔ ያቺ ነች።
አማራውና አፋሩ፣ ኦሮሞውና ሲዳማው፣ ቋንቋዬን ባይሰማ፣ ባይገባው ባህሌም ግን ለቅሶዬን ሳይቀር፤ ሰርጌንም፣ ኀዘንና ደስታዬንም የሚጋራኝ ሰው ነው የኔ አገር። ሰው የተከፈለበት፣ የደም፣ የአጥንት ክብር፣ የቀይ ቢጫ አረንጓዴው የቃል ኪዳን ህብር ሕዝቦችን ከሰንደቃቸው አስተሳስሮ ያቆየ ያኛው ነው የእኔ አገር።
አገር ቅኔ ነው – ለእኔ የሁለንተናን አመስጥሮ ገበና ከቶ የሚይዝ፤ አገር ማለት ለእኔ የእናት ጓዳ ነው – ሲከፋኝ የምሸሸግበት፣ ሲደላኝ ተኳኩዬ፣ አምሮብኝ የምወጣበት፤ አገር ለእኔ ድግስ ነው – ሁሉ አብሮ በልቶ፣ ጠጥቶ የሚደሰትበት፤ አገር ለኔ ውርስ ነው – ከአያት አባት የተወራረሰ፣ ለእኔና ለአንተ ምቹ መኖሪያ፣ አባት ሲያቀና
ቀዬና ቤቱን ሰርቶ ያስረከበበት።
ቤት መስሪያውም ምድር ጠላት ሲደፍራትም፣ ጦሩን ሰብቆ እየፎከረ፤ ብሔር፣ ዘር ሳይቆጥር ከሁሉም የኢትዮጵያ ልጆች የተዋጣው፣ በእምዬ ምኒልክ ጥሪ ጥቅምት እኩሌታ ላይ ወረኢሉ የመሸገው፤ ብሎም ወደ ጦር ሰፈሩ፣ ወደ ዓድዋ የተመመው፣ ለዛሬው ክብር እንድንበቃ ደም አጥንቱን የገበረው፣ አገር ማለት ሰው (እሱ) ነው፤ ለእኔ የደምና የአጥንት ስሪት የሆነው።
አገር ማለት ለእኔ ተፈጥሮ ከቸረው በረከት፣ የላቡን ፍሬ የሚበላ፤ አገር ማለት ወገን ነው – የእኔ የምለው መከታ። አገር ማለት ሰው ነው – አፈርን ገፍቶ ሲያበቃ በእጁ የያዘውን ፍሬ በእምነት ምድር ላይ የሚበትን ገበሬ፤ አገር ማለት ሰው ነው – በእምነት የተጣለው ፍሬ በቅሎ፣ ጎምርቶ ሲያሸት እሸት ቅመሱ ብሎ ሲያድል ያለስስት የሚኖረው ሰው፤ አገር ማለት ለእኔ ምርቱ የተሰበሰበ ዕለት በደቦ የሚያግዘው ጎረቤት ነው።
አገር ማለት ለእኔ ሰው በመሆንህ ብቻ አልቅሶ የሚቀብርህ፤ አገር ማለት ለእኔ ሦስት ቀናት ሙሉ የራሱን ቤት ትቶ ኀዘንህን እንድትረሳ ከጎን የሚቆምልህ፤ ጥቁር የሚለብስልህ፤ አገር ማለት ለእኔ የራበውን አጉራሽ የታረዘን አልባሽ ሰውና ሰው መሆን ብቻ የሚጠየቅበት፤ እሱ ነው አገሬ ቀባሪ ከፈጣሪ ተብሎ ሞት የማይፈራበት፤ አገር ማለት ለእኔ እጅ ለምፅዋት በተዘረጋበት ዕለት ያለምንም ስስት ኪስና ቦርሳውን የሚፈተሽባት፤ የእኔ አገር ይህ ነው። ከሰላምታ ጋራ ፈጣሪ ይመስገን ምላሽ የሆነበት፤ ለዛሬ መድረስን እንደ ታላቅ ስኬት የሚቆጠርበት፤ በምስጋና ብቻ ሕዝቡ በበረከት ኑሮን የሚኖርበት – ለእኔ አገር ያ ነው።
ልብ ስለአገር ብዙውን ያልማል፤ ቆም ብሎ ሲያስብ እውነቱ ግን ጠፍቷል፤ ሰው ባልተጠየቀበት ባልመረጠው ዘሩ ዛሬም ይጠላላል፤ ስለ አንድ አገር ቀርቶ በጎጥና ብሔር ይጎነታተላል፤ የዛሬ ቀንህ ላይ ለነገ የሚሆን ጉድጓድ ይቆፍራል፤ እንኳን አምኖ ሊቆም ለአንድነት ለክብሩ ጉርብትናም ጠልቷል። የታለች ያች አገር? በልቤ ውስጥ ነግሳ የታተመችው፤ የት አለች ያች አገር የደምና የአጥንት ዋጋ ያስከፈለችው? እኔን ግራ ገባኝ እናንተ መልሱ፣ አገሬ የት አለች ሰው የረከሰባት ዛሬ ላይ ሆናለች። አገር ሰው ከሆነ ሰው ለሆነው አገር ሰው ከተከፈለ የሰው ክብር ጠፍቶ ዝቅ ብሎ መታየት በዚህኛው ትውልድ ለምን ተፈጠረ? ብዬ አብቅቻለሁ።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን የካቲት 26 ቀን 2015 ዓ.ም