በሰላም ወጥቶ ለመግባት፣ ሠርቶ ለማትረፍ፣ ወልዶ ለመክበድ ለሁሉም ነገር ሰላም መሠረት ነው። የሰላም ዋጋ ቀድሞ የገባቸው የአገሬ ሰዎች ጠዋት ከእንቅልፋቸው ሲነሱም ሆነ ሲተኙ ለራሳቸውም ለአገራቸውም ሰላምን ይመኛሉ። መሽቶ በነጋ ቁጥር በሰላም ያዋለ ፈጣሪያቸውን አመስግነው ለቤተሰቦቻቸው፣ ለጎረቤቶቻቸው፣ ለቀያቸው፣ ለአገራቸው እንዲሁም በምድር ላይ ላሉ ፍጡራን በሙሉ ሰላም እንዲሰፍን መመኘት የዘወትር ተግባራቸው ነው።
ሰላም ለሰው ልጆች የመኖር ዋስትና እንደመሆኑ መጠን ሰላም እንዲሰፍን ከመመኘት በዘለለ የሰላም አየር እየተነፈሱ ለመኖር ሰላም በዓለም ዙሪያ እንዲሰፍን መትጋት በእጅጉ አስፈላጊ ነው። የሰላም ዋጋው ገብቷቸው ለሰላም ዘብ የቆሙ ሰዎች እንዳሉ ሁሉ፤ በተቃራኒው ደግሞ ሰላም የማደፍረስ አላማን አንግበው ቀን ከሌት የሚተጉ ኃይሎች እንዳሉ ይታወቃል።
እነዚህ ሰላም ጠል የሆኑ ኃይሎች ሁከትን እንጂ ሰላም ማጣጣም አይሹምና የዓለም ሕዝቦች በሰላም እንዳይኖሩ፣ ሰላምና መረጋጋት እንዳይሰፍን በማድረግ የእርስበእርስ ግጭቶች እንዲበራከቱ፣ ሽብርተኝነትና ወንጀል እንዲባባስና እንዲስፋፋ ያደርጋሉ። በዚህም የተነሳ በብዙ ሺዎች የሚቀጠሩ ሰዎች ሕይወት ለመጥፋት እና ለንብረት ውድመት እንዲሁም ለብዙ ሚሊዮኖች መፈናቀል፣ ስደትና ረሃብ ምክንያት እየሆኑ ይገኛሉ።
በአሁኑ ጊዜ በዓለም ላይ በርካታ አገራት በሰላም እጦት የተነሳ እየተናወጡ ዜጎቻቸው ለከፋ መከራና ለስቃይ እንዲሁም ለስደት እየተዳረጉ ይገኛሉ። ባስ ሲልም እንደ ሶሪያ እና የመን ያሉት አገራት ደግሞ ወደ ፍርስራሽነት የተቀየሩበትን ሁኔታ አይተናል። በቅርቡ በሶሪያና በዩክሬን መካከል እየተካሄደው ባለው ጦርነት ዩክሬን እየወደመች ወደ ፍርስራሽነት እየተቀየረች ዜጎቿ ለሞትና ለስደት ሲዳረጉ በቴሌቪዥን መስኮቶቻችን ፍዝዝ ብለን ተመልክተናል። የዓለም አገራትን ከመጥቀሱ በላይም የሰላም እጦት የእኛንም በር በማንኳኳቱ ለእርስ በእርስ ጦርነት በመዳረጋችን ጦርነቱ ያስከተለውን ኪሳራና ውድመት በዓይናችን ከማየት፤ በጆሮአችን ከመስማት አልቦዘንም።
ባለፉት ሦስት ዓመታት አገራችን በሁሉም አቅጣጫ በሰላም እጦት መረጋጋት ባለመኖሩ የተነሳ ስትናወጥ መቆየቷ የሚታወሰ ነው። በአገሪቱ በየአቅጣጫው የተከሰተው የሰላም እጦት ለሺዎች ሕይወት መጥፋትና ለንብረት ውድመት ምክንያት ሆኗል። በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን ለስደት ዳርጓል። ጦርነት ኪሳራ እንጂ ትርፍ የለሽ፤ ጦርነት አሸናፊና ተሸናፊ የሌለበት በመሆኑ ሁለቱንም ተፋላሚ ወገኖች ለማህበራዊ፣ ለኢኮኖሚያዊና ለፖለቲካዊ ቀውስ የሚዳርግ ነው።
የፖለቲካ ቁማርተኞች የሚለኩሱት እሳት የሚፈጃቸው ምንም የማያውቁትን ንጽሃን ዜጎችን ነው። ከዚህ አንጻር ጦርነት ለምንም የማይበጅ መሆኑን አውቆ ከቀደመ ጥፋት ለመማር ዝግጁ መሆን ሰላም እንዲሰፍን መሥራት ብልህነት ነው። በፌዴራል መንግሥትና በሕወሓት መካከል በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ የተካሄደው የሰላም ስምምነት ለሰላም ቅድሚያ የሰጠ፣ ከጦርነት ይልቅ ሰላም ማስፈን ላይ ትኩረት ያደረገ ነው።
ዜጎች ያለምንም ስጋት በሰላም ወጥተው በሰላም እንዲገቡ፤ ሠርተው ለለውጥ እንዲተጉ የማድረግ ኃላፊነትን የወሰደ ነው። ሆኖም ግን ሰላምን እንዲጸናና ቀጣይነት እንዲኖረው ሰላም ፈላጊ አካላት መካከል የተደረገው ስምምነት እንዲቀጥል በሁሉም በኩል ያላሰለሰ ጥረት ማድረግ ይጠይቃል።
ስምምነቱም ፍሬ አፍርቶ ዜጎች ከጦርነት ተላቅቀው የሰላም አየር መተንፈስ መቻል በራሱ ትልቅ ተስፋ የሚሰንቅ ቢሆንም ሰላም እና መረጋጋት ለማስፈን በብዙ ትግልና ጥረት ውስጥ ማለፍ የሚጠይቅ ነው። ዘላቂና ዋስትና ያለው ሰላምን ለማረጋገጥ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን አስተዋፆኦ መወጣት ይጠበቅባቸዋል።
በተመሳሳይ በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች ዳር እስከዳር ድረስ ሰላም ለማስፈን የተጀመሩ ሥራዎችን ቀጣይነት እንዲኖራቸው ማበረታታት ይገባል። አሁን ላይ በአገራችን በሁሉም አቅጣጫ ሰላምን ለማስፈን እንዲያስችል እየተወሰዱ ያሉ እርምጃዎች ለሰላም ትልቅ ዋጋ እንደተሰጠው ማሳያ ናቸው።
ለአብነት በአገር ውስጥ ባሉ አገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ብሔራዊ መግባባት እንዲኖር ለማድረግ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስራ አንድ አባላት ያሉትን የምክክር ኮሚሽን አቋቁሞ ወደ ሥራ መግባቱን መጥቀስ ይቻላል። አገራዊ ምክክሩ የተለያዩ አላማዎችን አንግበው በፖለቲካው መድረኩ ላይ ያሉ የፖለቲካ መሪዎችና ልሂቃን እንዲሁም ሕዝቡ ውስጥ ያሉ ጥያቄዎችና ሐሳቦችን መሠረት በማድረግ እንዲቀራረቡ ለማድረግ ያለመ ነው።
አገራዊ ምክክሩ ለአገራዊ አንድነት ገንቢ አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ በማድረግ ረገድ አወንታዊ ሚና እንዳለው ታምኖበታል። የምክክር ኮሚሽኑም የተሰጠውን ኃላፊነት በመወጣት ረገድ በርካታ ሥራዎች እየሠራ ይገኛል። ኮሚሽኑ ባለፈው ሳምንት እንዳስታወቀው በሁሉም ክልሎች፣ በድሬዳዋ እና በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደሮች የግብዓት ማሰባሰቢያ መድረኮችን ማዘጋጀቱንና በተለያዩ ክልሎች ሲካሄዱ የነበሩ የውይይት መድረኮች ለኮሚሽኑ ቀጣይ ሥራ እጅግ ጠቃሚ ግብዓቶች የተገኘባቸው እንደሆኑ መጠቆሙ የሚታወስ ነው።
ተፎካካሪዎቹን እና ገዢውን ፓርቲ ጨምሮ በምርጫ ቦርድ ከተመዘገቡት 53 የፖለቲካ ፓርቲዎች ውስጥ ከ40 በላይ የሚሆኑ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከኮሚሽኑ ጋር ለመስራት መስማማታቸው ኮሚሽኑ በአብዛኛው ሕዝብ ዘንድ ቅቡልነት እያገኘ መሆኑን ማሳያ ነው። ሁሉም አካላት ለምክክር መድረኩ በራቸውን ክፍት ማድረጋቸው በምክክሩ ተስፋ እንድንሰንቅና አመርቂ ውጤት እንድንጠበቅ የሚያደርግ ነው።
አሁን ላይ በአገራችን ሰላምን በማስፈን በሁሉም አቅጣጫዎች ጫፍ እስከ ጫፍ ዜጎች በሰላም የመኖር ዋስትና ተጠበቆ እንዲኖሩ በማድረግ ረገድ መሠራት ያለባቸው ሥራዎች በሚገባ እንዲሠሩ ያስፈልጋል። አንዱ በኩል ያለው ቀዳዳ ሲደፈን በሌላ በኩል ያለው የሚያፈተልክ ከሆነ ግን ነገሩ ሁሉ ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ ዓይነት ይሆናልና መጠንቀቅ ይገባል።
የሰላም ባለቤትም ጠባቂም ሕዝብ ነው። ሰላም የማስከበር ጉዳይ የጸጥታ መዋቅሩ ኃላፊነት እንደሆነ ተደርጎ የሚተው ከሆነ ግን የሚፈለገውን ሰላም ለማስፈን አይቻልም። የኅብረተሰብ ተሳትፎ ያልታከለበት ሰላም ማስፈን የሚታሰብ ጉዳይ አይደለምና መንግሥት ሕግን በማስከበር አገር በማረጋጋት ሰላም በማስፈን ረገድ ከሕዝቡ ጋር እጅና ጓንት ሆኖ መሥራት ይጠበቅበታል።
ሰላም ፈላጊው ዜጋ ደግሞ የሰላምን ጥቅም በሚገባ የሚረዳ በመሆኑ ለሰላም ዘብ መቆሙን ማሳየት ይኖርበታል። ነገ በከፍታ ማማ ላይ ልናያት የምንፈልጋት የኢትዮጵያ የወደፊት ዕጣ ፈንታ የሚወስነው ሰላሟ መጠበቅ፣ ሕዝቦቿ በሰላም እና በአንድነት እንዲኖሩ ማስቻል ነው። ለአገር ተረካቢው ትውልድ የምናስረክባት አገር ሰላሟ የጸና በአንድነት መሠረት ላይ የታነጸች እንድትሆን ሁላችንም የሚጠበቅብንን መወጣት ይገባናል።
ቸር እንሰንበት።
ትንሳኤ አበራ