የኢትዮጵያ ፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ከአስር ቀናት በፊት አንድ አስደንጋጭ የጥናት ውጤት ይፋ አድርጓል። ኢትዮጵያ ምግብ ውድ ከሆነባቸው የአፍሪካ አገራት ከቀዳሚዎቹ ተርታ መሰለፏንና ከዓለም 8ተኛ ደረጃ፤ ከዚምባቡዌ ቀጥላ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ከፍተኛ የዋጋ ግሽበት ያለባት አገር እንደሆነች አርድቶናል። አጠቃላይ የዋጋ ግሽበቱ 49.1 በመቶ ሲሆን የምግብ የዋጋ ንረት ከፍተኛውን ድርሻ ይዟል። ይህም ከክልል ክልል የተለያየ ሲሆን በአማራና ደቡብ ክልል ያለው የዋጋ ግሽበት ከአገራዊ ምጣኔው ከፍ ያለ ነው።
በተለይ ለምግብ የዋጋ ንረቱ የምርት መጠን ከፍላጎት ጋር አለመመጣጠን አንዱ ምክንያት ነው ብለዋል ጥናቱን ያቀረቡት ዶ/ር ታደሰ ኩማ። ገበሬው ከሚያመርተው ምርት ከራሱ ፍጆታ ተርፎት ለገበያ የሚያቀርበው በአማካይ ከ20 በመቶ አይበልጥም። ከሚመረተው በቆሎ 85 በመቶው ገበሬው ለእለት ፍጆታው ያውለዋል። በሌላ በኩል ከሚመረተው ጤፍ ለገበያ ቀርቦ ከተማው የሚሸምተው 30 በመቶውን ብቻ ነው።
በምግብ ራሳችንን አለመቻላችን የኑሮ ውድነቱን ያባባሰ ሌላ ምክንያት ነው። ለምሳሌ ኢትዮጵያ ከ97 በመቶ በላይ የዘይት ፍላጎቷን ከውጭ ገዝታ ነው የምታስገባው። ዋጋው የሚወሰነው በዓለምአቀፍ ገብያ ነው። ዋጋው እንደተሰቀለ የቀረው ከኮቪድ 19 ወረርሽኝ በኋላ፤ ከዩክሬንና ከራሽያ ጦርነት ወዲህ መሆኑን ያስታውሷል።
ከተቀረው ዓለም የአገራችንን የኑሮ ውድነት ለየት የሚያደርገው ማለትም ከፍላጎትና አቅርቦት አለመመጣጠን ባሻገር እሴት የማይጨምሩ ደላሎች በገበያ ሰንሰለቱ ከማሳ እስከ ገበያ መሰግሰጋቸው፤ መንግሥትም ተገቢውን ቁጥጥርና የእርምት እርምጃ አለመውሰድ የዋጋ ንረቱን አባብሶታል ይላል ጥናቱ። በዚህም ምክንያት ምርት አምራቹ ከሚሸጥበት 58 በመቶ ዋጋው ከፍ ብሎ ሸማቹ ጋር እንዲደርስ አድርጓል።
ይህ ማለት ዛሬ በአገራችን ከሚስተዋለው የዋጋ ግሽበት 60 በመቶ ያህሉ የተከሰተው በደላሎች አማካኝነት መሆኑን ጥናቱ ያመላክታል። በሕግና በሥርዓት ሊስተካከል በሚችል የግብይት ሰንሰለት ሸማቹ ምን ያህል ፍዳውን እያየ መሆኑንም ቁልጭ አድርጎ አሳይቶናል። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ከስንት ውትወታ በኋላ ሕገ ወጥ ደላላን ከግብይት ሰንሰለቱ የሚያስወጣ መመሪያ አዘጋጀሁ ቢለንም ሥራ ላይ ባለመዋሉ የአገሪቱ የግብይት ሰንሰለት የደላላ መፈንጫ እንደሆነ ቀጥሏል።
በዚያ ሰሞን በሲሚንቶ አሁን ደግሞ ስንዴ ላይ የሚስተዋለው ትንቅንቅ የግብይት ሰንሰለቱን ስብራት አደባባይ አውጥቶታል። በነገራችን ላይ የደላላ ተጽዕኖ ከገበያው አልፎ የኢኮኖሚውን፣ የፖለቲካውንና የማህበራዊ ጉዳዩን መሠረት እየነቀነቀው ከመሆኑ ባሻገር ስውር «አራተኛው መንግሥት» እስከመሆን ደርሷል ቢባል ማጋነን አይሆንም። ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ በዚሁ ጋዜጣ ደላላን ከአራተኛ መንግሥት በትይዩ ያቀረብሁበትን መሰናዘሪያ ልመለስበት ወደድሁ። ለመሆኑ አራተኛ መንግሥት ማለት ምን ማለት ነው?
«አራተኛው መንግሥት» (The Fourth Estate) የሚለው ስያሜ፣ ሀረግ ለመጀመሪያ ጊዜ ሥራ ላይ የዋለው የዛሬ 232 አመታት በአገረ እንግሊዝ ነው። አንዳንድ የታሪክ መዛግብት ደግሞ ከዚህ ግማሽ ክፍለ ዘመን ቀድሞ እንደነበረም ያወሳሉ፤ በዚያን ጊዜ ሦስቱ መንግሥታት በመባል ይታወቁ የነበሩት፤ 1ኛ . ቤተ ክርስቲያኗ 2ኛ. መሳፍንቱ 3ኛ . ተራው ሕዝብ ሲሆን፤ 4ኛ. ጋዜጠኞችና መገናኛ ብዙኀን ነበሩ።
አራተኛው መንግሥት የሚለውን አባባል ለመጀመሪያ ጊዜ የተጠቀሙት የታላቋ ብሪታኒያ የፓርላማ አባል ኤድሞንድ ቡርክ ሲሆኑ፤ አመቱም እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1787 እንደሆነ የታሪክ ድርሳናት ከትበው አቆይተውናል። ከዚህ ቀደም ባሉት አመታት ንግስቷ፣ የሕግ ባለሙያዎች lawyers እና ዝቅተኛው መደብ፣ ላቭ አደሩ proletariat እንደ አራተኛ መንግሥት ይቆጠሩ ነበር። ከጊዜ በኋላ ስያሜው ወደ ጋዜጠኞችና ሚዲያ ቋሚ መጠሪያነት ተሸጋግሯል።
በተመሳሳይ ሁኔታ በሒደት ሦስቱ መንግሥታት ቀደም ሲል ከነበራቸው ስያሜ ወደ ሕገ አውጭ፣ ሕግ ተርጓሚ እና ሕግ አስፈፃሚ መለወጣቸውን እነዚሁ ድርሳናት ያስረዳሉ። እነዚህ የመንግሥት አካላት መንግሥታቸውን የመቆጣጠሪያ ሚዛንና የመመዘኛ መድለው check & balance በመሆን ያገለግላሉ። ሚዲያው አራተኛው መንግሥት መባሉ በአንድ አገር ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳይ ምን ያህል ከፍ ያለ ቦታ፣ ሚና እንዳለው ያሳያል።
በምዕራባውያን በተለይ በእንግሊዝና በአሜሪካ ሚዲያው ከሦስቱ የመንግሥት አካላት ተርታ መሰለፍ ችሏል። በአህጉራችን በደቡብ አፍሪካ፣ በጋና፣ በናይጄሪያ፣ …፤ በተወሰነ ደረጃ በኬኒያ፣ በኮትዲቯር እና በሌሎች አገራት ሚዲያው የአራተኛው የመንግሥት አካልነት ሚናቸውን፣ ኃላፊነታቸውን ከእነ ውስንነተቻው እየተወጡ ነው። እንደ አለመታደል ሆኖ አገራችን የጎለበተ፣ ጥንታዊ የአገረ መንግሥት ልምምድ ቢኖራትም ሚዲያችን ግን አራተኛው የመንግሥት አካል ለመባል ገና ብዙ ብዙ ይቀረዋል።
ስለሆነም ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር በአንድ መድረክ የመገናኛ ብዙኃን በመንበሩ አለመገኘታቸውን ታዝበው ይመስል፤ በአንድ መድረክ በአገራችን የገነገነውን ሙስና አራተኛው መንግሥት በማለት እንደገለፁት ሁሉ፤ እኔም በአገራችን አሉታዊ ተፅዕኖው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየከፋ የመጣውን፤ በጊዜ ሀይ ካልተባለ ለአገራችን ህልውና አደጋ እየደቀነ ያለውን፤ የአገሪቱን ኢኮኖሚ ከጉልት እስከ ጅምላ ንግድ፤ በአጠቃላይ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ ሕይወታችንን እየናጠ ያለውን፤ አደገኛ እየሆነ የመጣውን፣ በሰዓት የተጠመደ ቦንብ time bomb ይገልፅልኛል ብዬ ስላመንሁ “ድለላ “ን ሳልወድ አምባሻ ሳልቆርስ «አራተኛው መንግስት» ብዬዋለሁ።
አዎ ! ከላይ ስለ ሀረጉ ስረወ ቃል etymology ሳትት ፅንሰ ሀሳቡ በቀደመው ዘመን ንግስቷን፣ የሕግ ባለሙያን፣ ሠራተኛውን ለመግለፅ ይውል እንደነበረው ሁሉ፤ እኔም ዛሬ ድለላ በአገራችን ከደቀነው ወቅታዊና ከቡድ ተፅዕኖ አኳያ አራተኛው የመንግሥት አካል ብለው ያንስበት ይሆን እንደሁ እንጂ አይበዛበትም።
እንዲያውም ከሕግ አውጭው፣ አስፈፃሚውና ተርጓሚው እንዲሁም ከሚዲያው በላይ በዕለት ተዕለት ሕይወታችን፣ ጓዳ ጎድጓዳችንን አንዳንድ ጊዜም አልጋ ተጋሪያችንን፣ አንሶላ ተጋፋፊያችንን እስከ መወሰን ከፍ ሲልም ውሃ አጣጫችንን እስከመምረጥ፣ …፤ ስለተሸጋገረ “ ድለላ !? “ 1ኛው የመንግሥት አካል ቢባል ያንሰው ይሆናል እንጂ አይበዛበትም።
አዎ ! ደላላ ስንበላ የሚበላ፣ ስንጠጣ የሚጠጣ፣ ስንለብስ የሚለብስ፣ ስንገዛ የሚገዛ፣ ስንሸጥ የሚሸጥ፣ ስንከራይ የሚከራይ ፣ …፤ ምን አለፋችሁ ስንሰራ ካለመሥራቱ፣ ስንራብ ካለመራቡ፣ ስንታረዝ ካለመታረዙ፣ በችጋር ስንገረፍ ካለመገረፉ፣ በኑሮ ወድነት ስንሰቃይ ካለመሰቃየቱ፣ በዋጋ ግሽበት ኪሳችን፣ ቦርሳችን ሲገለበጥ ካለመገልበጡ፣ …፤ በስተቀር የማይገባበት የሕይወታችን ቅንጣት፤ የማያንኳኳው በር የለም። ታዲያ አይደለም 4ኛው፣ 1ኛው መንግሥት ቢሆን ይበዛበታል!?
በእያንዳንዳችን ሕይወት አዛዥ ናዛዥ የሆነው «ድለላ» የቃሉ ትርጉም ምን ማለት ይሆን !? ምንም እንኳ በስነ ልሳን lingustic አስተምህሮ በስያሜውና በተሰያሚው መካከል የባህሪ ግንኙነት እንደሌለ ቢበየንም፤ የቃሉ ግብርና ምግባር ስለተማታብን፣ ስለተጣረሰብን ትርጉሙን እንመልከት።
የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማዕከል፤ በ1993 ዓ.ም የአዘጋጀው የአማርኛ መዝገበ ቃላት፤ « ደላላ» ን ፦ ‘ ገንዘብ እየተከፈለው ተፈላላጊዎችን ( ሻጭና ገዥን፣ አከራይና ተከራይን፣ …፤ ) አገናኘ፣ አስማማ። ‘ በማለት ይተረጉመዋል። በመደለል ሥራ ላይ የተሰማራ ሰው፤ አታላይ፣ በውሸት አግባብቶ ለማሳመን የሚሞክር፤ «ድላል» ን ደግሞ ለደላላ የሚከፈል ገንዘብ በማለት ይተረጉማል።
የደስታ ተክለወልድ ዘሀገረ ወግዳ በ1970 ዓ .ም የአማርኛ መዝገበ ቃላት ደግሞ፤ ደለለ ፦ አሞኘ፣ አታለለ፣ ሸነገለ፣ የማያደርገውን አደርጋለሁ አለ፤
ደላላ፦ አመልካች፣ ጠቋሚ ድላል ፦ ለጠቋሚ፣ ላስማሚ፣ የሚሰጥ ገንዘብ ሲል ይተረጉመዋል። ይሄኛው ትርጉም ከቀደመው ይልቅ የአገራችንን ደላላ ቁልጭ አድርጎ ይገልፀዋል። የእንግሊዝኛውን ትርጉም ‘ broker ‘ ስረወ ቃል ስንመለከት “ brocour “ ከሚለው የፈረሳይኛ ቃል የመጣ ሲሆን ከ14ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ የቋንቋው አካል መሆኑን ሜሪያም ዌቢስተር የእንግሊዝኛ መዝገበ ቃላት ያወሳና ትርጉሙም ፦bro·ker : a person who helps other people to reach agreements, to make deals, or to buy and sell property (such as stocks or houses) ነው ይለናል።
የአማርኛውም ሆነ የእንግሊዝኛው መሠረታዊ ትርጉም ተቀራራቢ ቢሆንም፤ «ድለላ» ሲነሳ አብሮ ማታለል፣ መሸንገል፣ ማሞኘት፣ በውሸት አግባብቶ ማሳመን፤ የሚሉ አሉታዊ አንድምታዎች ግዘፍ ከመንሳት አልፈው «ድለላ» በተነሳ ቁጥር ቀድመው ወደ አዕምሯችን የሚመጡት እነዚህ አሉታዊ ብያኔዎች ናቸው።
በአገራችን ያለውን አብዛኛውን ደላላም ይገልፁታል ተብሎ ይታመናል። ሆኖም እጅግ፣ እጅግ ያነሱ በጣት የሚቆጠሩ ቢሆኑም ታማኝ፣ ሀቀኛና መልካም ስነ ምግባር ያላቸው ደላሎች መኖራቸው ግን ሊዘነጋ አይገባም። ድለላን ከመንግሥት አካላት ተርታ ከማሰለፍ አልፌ እንደ 1ኛው መንግሥት የቆጠርሁበትን አብይት መግፍኤዎችንና መገለጫዎችን ላነሳሳ፤
1 . ኢኮኖሚያዊ ፦
ኢኮኖሚያችን ከሌሎች አገራት ለየት ያደርገዋል ብዬ ከማምንባቸው ግርምቶች ቀዳሚው፤ በአዳም ስሚዝ የኢኮኖሚክስ ሀ ሁ … ዝቅተኛ መስፈርት በሆኑት ፍላጎት demand እና አቅርቦት supply አለመዘወሩ ነው። ከጉልት እስከ ጅምላ ንግድ፣ ከጎጥ እስከ ፌዴራል፣ ከሽንኩርት ማሳ እስከ አትክልት ተራ፣ ከሚዛን ተራ እስከ እህል በረዳ፣ ከአንድ ክፍል ጭቃ ቤት እስከ ተንጣለለ ቪላና ፎቅ፣ ከአንድ ጥማድ መሬት እስከ ጋሻ መሬት፣ ከአራጣ ብድር እስከ ባንክ ብድር፣ …፤ ከታች እስከ ላይ በተሰገሰጉ ህልቁ መሳፍርት ደላሎች ሳምባ የሚተነፍስ ኢኮኖሚ መሆኑ ነው።
አንድ ወዳጄ በዚያ ሰሞን እንዳጫወተኝ ከሆነ የደላላ እጅ ሀይ ባይ በማጣቱ እረዝሞ እረዝሞ በአንድ ወቅት አገራችን በምትፈርማቸው ብድርና እርዳታ ሳይቀር ፈርቅ እስከመያዝ ደርሶ ነበር። እግራችን እስኪ ቀጥን ብንዞር የደላላ እጅ ያልገባበት የኢኮኖሚ ዘርፍ የለም። ከላይ ከትርጉሙ እንደተመለከትነው የድለላ ሥራ ሻጭና ገዥን ማገናኘት ለዚህም ድላል ( የአገልግሎት ክፍያ ) መቀበል ቢሆንም፤ የአገራችን ደላላ ግን በዓለም ታይቶም፣ ተሰምቶም በማያውቅ ሁኔታ ዋጋ ቆራጭ፣ ተማኝ፤ ገበያ መሪ እስከመሆን ደርሷል።
አሁን ያለው የእህል፣ የአትክልት፣ የሸቀጣ ሸቀጦች ዋጋ፤ የመኪና የንግድም ሆነ የኪራይ ቤት ክፍያ፣ የመሬት ዋጋ፣ …፤ የተቆረጠው፣ የተተመነው በገበያ ሳይሆን በደላላ ነው። በዚህም ገበያ አመጣሽ ሳይሆን፤ ደላላ ዘራሽ የኑሮ ውድነትና የዋጋ ግሽበት ጎንቁሏል። በዚህ የተነሳ ዜጋው በኑሮ ውድነት ፍዳውን እያየ ነው። የሸቀጡ፣ የምርቱ፣ የአገልግሎቱ አምራች፣ አቅራቢም የሚገባውን ጥቅም እያገኘ አይደለም። ከሸማቹም፣ ከሻጩም በሁለት ቢላዋ እየበላ ያለው ሕገ ወጥ ደላላው ነው።
ዛሬ በመላው አገራችን ያሉ አርሶ አደሮችም ሆኑ አርብቶ አደሮች በተደጋጋሚ የሚያነሱት ጥያቄ የገበያ ትስስር እንዲፈጠርላቸውና ለምርታቸው፣ ለገበያ ከሚቀርቡ እንስሳትም ሆነ ተዋጽኦ ተገቢውን የድካማቸውን ዋጋ እንዲያገኙ ሲወተውቱ፣ ሲማፀኑ በየሚዲያው ብንሰማም፣ ብንመለከትም መፍትሔ ባለማግኘታቸው ዋጋ የሚቆርጥላቸው ደላላው ነው። በምርቱ ተጠቃሚዎች እነሱ ሳይሆን ደላላው ነው።
አርሶ አደሩም ሆነ አርብቶ አደሩ የድካሙ፣ የላቡ ተጠቃሚ ካለመሆኑ ባሻገር፤ ደላላ አመጣሽ የሆነው የዋጋ ግሽበትና የኑሮ ውድነት የኢኮኖሚውን ወደለየለት ቀውስ እያንደረደረው ነው። ሕገ ወጥ ደላላው ያለ አዛዥ ናዛዥ ገበያውን በብቸኝነት መቆጣጠሩ፤ መንግሥት በነፃ ገበያ ስም መነሻ ዋጋ ተመን እና የትርፍ ሕዳግን profit margin አለመወሰኑ፤ ከሕገ ወጥ ደላላው ጋር እሳትና ጭድ ሆኑ የኑሮ ወድነቱን እያቀጣጠለ፤ በዜጋው ላይ ብሶትን፣ ምሬትን ተስፋ መቁረጥን እየከዘነ ይገኛል።
በዚሁ ከቀጠለ ወደለየለት ፖለቲካዊ ቀውስ የማያመራበት ምክንያት የለም። የኢትዮጵያ የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት በሰሞነኛ የጥናት ግኝቱ ያስጠነቀቀው ይሄንኑ ነው። በዓለማችን የነፃ ገበያ አባት የምንላቸው ምዕራባውያን ሳይቀሩ የትርፍ ሕዳግንም ሆነ የመነሻ ዋጋ ደረጃን እየወሰኑ፤ ገበያውን እየተቆጣጠሩ ባለበት፤ እኛ ለዛውም ያልሰጠነውን ኢኮኖሚ ስድ መልቀቃችን ዛሬ ለምንገኝበት ምሬት፣ እሮሮ ዳርጎናል።
2 . ማህበራዊ ፦
ባለፉት አመታት ምሳሌ፣ አርዓያ የሚሆን ቤተሰብ፣ ተቋም፣ መሪ በየደረጃው አለመፈጠሩ፤ የግብረ ገብ ትምህርት አለመሰጠቱ፤ ፈሪአ እግዚአብሔር (ፈጣሪ ) ያለው ትውልድ አለመታነፁ ዛሬ ለምንገኝበት የማህበራዊ ቀውስ አፋፍ አድርሶናል። ውሸት፣ ሌብነት፣ ዘረፋ፣ ማጭበርበር፣ መካድ፣ ጥሎ ማለፍ፣ …፤ ነውር መሆናቸው ቀርቶ የሚያሸልሙበት ጊዜ ላይ ደርሰናል። የዚህ ትውልድ፣ ማህበራዊ ቀውስ ውጤት የሆነው አብዛኛው ደላላም መዋሸትን፣ ማታለልን፣ በአቋራጭ መክበርን ሙያ እስከማድረግ ተግቷል። ገንዘብ እስካገኘ ድረስ ለዜጋው ለወገኑ ደንታ ቢስ ሆነ። እህት ወንድሞቹን በማይጨበጥ ተስፋ እየደለለ ለስደት፣ ለመከራ ዳረገ። በበርሀ፣ በባህር አለቁ።
በአረመኔዎች እጅ ወድቀው የአካላቸውን ክፍል አጡ። ሕገ ወጥ ድለላው በዚህ የሚያበቃ አይደለም። በአገራችን እየተስፋፋ በመጣው የወሲብ ንግድም ግንባር ቀደም ተዋናይ ነው። ለአቅመ ሔዋን ያልደረሱ ልጃ ገረድ ሕፃናትን ሳይቀር ለሕገ ወጥ የወሲብ ንግድ እስከማቅረብ፣ የዩኒቨርሲቲ ሴት ተማሪዎችን ለዚህ ሕገ ወጥ ተግባር እየመለመለ የፎቶ አልበም አዘጋጅቶ የሚያቀርብ አረመኔ ደላላ በየዩኒቨርሲቲዎቻችን በሮች ማግኘት እየተለመደ መምጣቱ የአደባባይ ምስጢር ነው።
ዛሬ ዛሬ ደግሞ አዲስ የድለላ ዘርፍ ማለትም ስለ የማህፀን ኪራይ surrogacy ደላሎች መስማት ከጀመርን ውለን አደርን፤ ልጅህን ለልጄ ማለት እየቀረ ተጋቢዎች ራሳቸው ወስነው ትዳር መመስረት እየተለመደ ቢመጣም፤ አሁን ሦስት ጉልቻ በደላላም ተጀምሯል። ምን አለፋችሁ ድለላ ያልገባበት የሕይወታችን ቅንጣት የለም። በእንቅርት ላይ እንዲሉ በተለያዩ ገፊ ምክንያቶች እየተሸረሸረ በመጣው ማህበራዊ ተራክቦ ላይ ስነ ምግባር የሌለው ሕገ ወጥ ደላላ በአናቱ ተጨምሮበት ቀውሱን እያባባሰው ነው።
3 . ፖለቲካዊ ፦
ሕገ ወጥ ደላላው በኢኮኖሚው የሚስተዋሉ መዋቅራዊ፣ ተቋማዊ ችግሮችን በማበባስ የሕዝቡን የዕለት ተዕለት ኑሮ ፈታኝ እያደረገው ይገኛል። በዓል በመጣ ቁጥር የሚስተዋሉ እጅግ የተጋነኑ የዋጋ ጭማሬዎችን እዚህ ላይ በአብነት ማንሳት ይቻላል። በቋሚነት የኑሮ ወድነቱን፣ የዋጋ ግሽበቱን በማባባስ ዜጋውን ለብሶት፣ ለምሬት እየዳረገ ነው።
እዚህም እዚያም ለሚስተዋሉ ግጭቶች በአንድም በሌላ በኩል የዋጋ ግሽበቱና የኑሮ ውድነቱ የፈጠረው ተስፋ መቁረጥ እንደ ክብሪት ሆኖ በማገልገል ላይ መሆኑን የተለያዩ አካላት እያነሱ መሆኑ፤ የሕገ ወጥ ደላላ እጅ ከኢኮኖሚው አልፎ በማህበራዊ መዋቅራችን ከፍ ሲልም ከሌሎች መግፍኤዎች ጋር ተዳብሎ አገራዊ ቀውስ በመለፈፍ፣ በመጥራት ላይ መሆኑን ተገንዝቦ ከዚህ በላይ ሳይረፍድ፣ ሳይቃጠል በቅጠል ሊባል ይገባል።
ሻሎም ! አሜን።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ጥር 28 ቀን 2015 ዓ.ም