ስለ ራስ ቴአትር ስታወራ ስሜታዊ ትሆናለች:: ቤቱን ትወደዋለች:: ከሕይወቷ አብዛኛውን ክፍል የሙያዋን ደግሞ ሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ ያሳለፈችበት ቤትም ነው:: ራስ ቴአትር የፍቅር ቤት ነው ብላ ነው ማውጋት የምትጀምረው:: ይህንንም ሁሉንም ቃለ መጠይቆቿን አይቶ ማረጋገጥ ይቻላል:: እድሜዋን በሙሉ ስለኖረችበት እና ስለምታፈቅረው ራስ ቴአትር አውርታ የማትጠግበውን ዝነኛዋ ተዋናይ ፤ ተወዛዋዥ እና ድምጻዊ ዘነቡ ገሰሰ የራስ ቴአትር አምባሳደር ብለን ሰይመን ወጋችንን እንጀምር::
አባቷ የሽሬ ተወላጁ አስር አለቃ ገሰሰ ነጋሽ ናቸው:: እናቷ ደግሞ የጎጃም ተወላጇ ወ/ሮ ስመኝ ሸለሙ:: እነዚህ ሁለት ሰዎች ጎንደር ጎርጎራ ላይ ተቀራረቡ:: ትዳር ተመሰረተ ፤ ልጆችም ተወለዱ:: ከተወለዱት ልጆች መካከል ደግሞ አንዷ ዘነቡ ነበረች::
የተወለደችው ሚያዝያ 27 ቀን 1956 ዓ.ም ነው:: ጎርጎራ ላይ እትብቷ የተቀበረው ዘነቡ ገና የ3 ወር ልጅ እያለች ነበር ወደ አዲስ አበባ በወላጆቿ እቅፍ የመጣችው:: ማረፊያዋም የጠቢባን መፍለቂያ የሆነችው ፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ ሆነ::
ልጅነቷ እንደማንኛውም ልጅ ነበር:: ነገር ግን ነጻነት እና ሥነ ሥርዓት ሚዛን ጠብቀው የሚሄዱበት ቤት ውስጥ ነው ያደገችው:: አባቷ ወታደር እንደመሆናቸው መጠን ቆፍጣና እና ሥርዓት ወዳድ ናቸው:: ያም ቢሆን በተፈጥሮዋ መልከ መልካም እና ፍልቅልቅ ለሆነችው ልጃቸው ራሷን የምትገልጽበትን ነጻነት አልነፈጉም::
ቤት ውስጥ ያለው ነጸነት ግን ደጅ አልነበረም:: ወቅቱ በደርግ እና በኢሕአፓ መካከል የከተማ ጦርነት የጦፈበት እና ወጣት በየጎዳናው ተገድሎ የሚታይበት ወቅት ነው:: ይህ ጦስ ቀስ ብሎ እነ ዘነቡ ቤትም ደረሰ:: አንዱ የዚህ የከተማ ሽብር ሰለባ ሆነ::
ይህ ኃዘን አፍላዋን ዘነቡን ክፉኛ አሳዘናት:: ስለዚህም ይህን ኃዘን ለመወጣት መንገዶችን መፈለግ ያዘች:: ሁነኛ መንገድ የሆነላት ደግሞ ሙዚቃ ማንጎራጎር ነበር:: የዳግማዊ ምኒሊክ ትምህርት ቤት ተማሪ የነበረችው ዘነቡ በተለይም የታጋይ ድምጽ ይጮሀል የሚለውን የትግል መዝሙር ትወደውና አብዝታም ትጫወተው ነበር::
አንድ ቀን በትምህርት ቤቷ ይህን ሙዚቃ መድረክ ላይ ስትጫወት አንድ ሰው ሰማት:: የሰማት ሰው ደግሞ ሻምበል ዮናስ የሚባል መልማይ ነበር:: ዘፋኝ መሆን ትፈልጊያለሽ ወይ ብሎ ዘነቡን ጠየቃት:: ሳታቅማማ አዎ አለች:: ለአባት እና እናቷ አንዲትም ቃል ሳትተነፍስ ጓዟን ጠቅልላ የሰሜን እዝ ሰሜን ነጸብራቅ ኦርኬስትራን ተቀላቀለች ፤ ጉዞዋም ወደ አስመራ ሆነ:: ለቤተሰቦቿ አስመራ ከደረሰች በኋላ ደወለች:: አባት አዘኑ::
መልከ መልካሟ ዘነቡ ድምጻዊ ሆና የጀመረችው የጥበብ ሕይወት ብዙ አልገፋም:: አንድ ቀን ከከረን ወደ አስመራ በመኪና ስትጓዝ ጉሮሮዋ ተዘጋ:: ጊዜያዊ መዘጋት ቢመስልም አልስተካከል አለ:: ይህን ተከትሎም ሙዚቃና ዘነቡ ተለያዩ::
ለሙዚቃ የተዘጋ ድምጽ ግን ለመድረክ ትወና እንዲሆን ሆኖ ተስተካከለ:: ዘነቡ ከድምጻዊነት ብትለያይም በውዝዋዜ እና ባላት መልካም ቁመና የተነሳ የማርሽ ባንዱ ዘንግ ወርዋሪ በመሆን ሥራዋን ቀጠለች::
እዚህም ላይ አዲስ ክስተት ተፈጠረ:: የ22 አመቷ ወጣት ዘነቡ ታደሰ የመጀመሪያ ልጇን ወለደች:: በወቅቱ ደግሞ የሠራዊቱ አባል ሆኖ ልጅ መውለድ አይቻልምና ሕግ በመጣሷ ከሥራዋ ታገደች:: ከብዙ ክርክር በኋላ ልጅ መውለድ ተፈቀደ:: ልጇን እያሳደግች እያለ በቀይ ኮከብ ዘመቻ አባቷ ከመሐል ሃገር ወደ ምጽዋ መጡ ፤ እሷም ሥራዎችን ለማቅረብ ከባንዷ ጋር ምጽዋ ተገኘች:: አባትና ልጅ ተገናኙ:: ግጥምጥሞሹ ፊልም ይመስል ነበር ትላለች::
አባት እሷን ካገኙ በኋላ ግን ሳይነግሯት ወደ አስመራ ጠፍተው ገሰገሱ:: ወደዚያ የሄዱት ለአንድ ዓላማ ብቻ ነበር:: የልጅ ልጃቸውን ለማየት:: የልጅ ልጃቸውን አይተው እና መርቀው ወደ ግንባር ተመለሱ:: ከ10 ቀን በኋላ በውጊያ ላይ ተሰው::
አስር አለቃ ገሰሰ ልጃቸው መደበኛ ሕይወት እንዲኖራት ይፈልጉ ነበር:: ስለዚህም ልጇን ይዛ ወደ አዲስ አበባ እንድትመለስ ይፈልጉ ነበር:: ዘነቡ ሁለተኛ ልጅ ስትወልድ ሰራዊቱ አሰናበታት:: ከ4 ዓመት ተኩል የሰሜን ቆይታ በኋላ ወደ አዲስ አበባ የተመለሰችው ዘነቡ በወታደር ቤት ኑሮ እና ልጅ በማሳደግ ተጎድታ ነበር::
ይህን ያየችው በሲኒማ ቤቶች አስተዳደር የራስ ሲኒማ ኃላፊዋ እመቤት ወልደ ገብርኤል አዘነች:: ራስ ቴአትር የሥራ ማስታወቂያ ሲያወጣም መጥታ እንድትወዳደር ዘነቡን ጠራቻት:: ነገር ግን ዘነቡ ብቸኛ ተወዳዳሪ አልነበረችም:: 600 ያህል ተፎካካሪዎች ነበሯት:: ፈታኙ ደግሞ ዝነኛው ተስፋዬ ለማ ነበር:: የተጎሳቆለችውን ዘነቡ በአይኑ ቢያይም በውድድሩ ግን ተሰጥኦዋ በልጦ ታየው::
ተወዳዳሪዎቿን በልጣ ማለፏ ሲነገርም ቆይ ዝም በሉ የሁለት ወር ደሞዝ ስትበላ መልኳም ይመለሳል አለ:: በ97 ብር ደሞዝ በ1976 ዓ.ም ራስ ቴአትርን ተቀላቀለች:: ድምጻዊነቱ ቀድሞ ቀርቷልና የተቀላቀለቸው በተወዛዋዥነት ነበር:: በወቅቱ ደግሞ ራስ ቴአትር የከዋክብቱ መናኸሪያ ነበረ፤ ሱራፌል አበበ ፤ አስቴር ከበደ ፤ ንዋይ ደበበ፤ ጸሐዬ ዮሐንስ ፤ አበበች ደራራ ፤ ኤልያስ ተባበል እና ሌሎችም የራስ ቴአትር ተቀጣሪዎች ነበሩ:: ዘነቡ ከነዚህ ከዋክብት መካከል አንዷነበረች::
1981 ላይ በዘነቡ ሕይወት ላይ ሌላ እጥፋት/ ተርን/ ተከሰተ:: ከድምጻዊነት ወደ ተወዛዋዥነት በድምጽ መዘጋት ምክንያት የዞረችው ዘነቡ አሁን ደግሞ ከውዝዋዜ ወደ ትወና ፊቷን ልታዞር ግድ ሆነ:: ምክንያቱ ደግሞ በወቅቱ ኮከብ የነበረችው እንዬ ታከለ እና ጓደኞቿ የወቅቱ መሪ የነበሩት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያምን ጠይቀው በወቅቱ በሃገር ባህል ውዝዋዜ ዝነኛ የነበረውን ራስ ቴአትርን እንዲቀላቀሉ መደረጉ ነው::
አዳዲሶቹ ተወዛዋዦች ሲመጡ የዘነቡ እና ውዝዋዜ ውዳጅነት ተጠናቀቀ:: ውዝዋዜ መድረኩን ለወጣቶቹ ለቅቃ የትወናውን መድረክ ተቀላቀለች:: በትወናው በርካታ የመድረክ ተውኔቶችን የሠራች ሲሆን ከነዚህም መሀከል ላጤ ፤የሰው ሰው፤ ዘር አዳኝ ፤ አሻራ ተጠቃሽ ናቸው:: ከትወናው በተጨማሪም ግን ዘነቡ የምትወደውን ራስ ቴአትር በሜክ አፕ አርቲስትነት ፤ አልባሳት እና ቁሳቁስ ኃላፊነት ፤ በአዳራሽ ኃላፊነት እና ሌሎችም ዘርፎች ሰርታለች::
ከመድረክ ተዋናይነት በኋላ ወደ ፊልም ሥራም የተቀላቀለችው ዘነቡ ታዋቂ የሆነችበትን ሹገር ማሚ ፊልም ጨምሮ አያስቅም ፤ አለሜ፤ ኤሽታኦል ፤ ያለ ሴት ፤ አስታራቂ ፤ መፈንቅለ ሴቶች እና ሌሎች በርካታ ፊልሞች ላይ ተውናለች:: በጉማ የሽልማት ሥነ ሥርዓት ላይ በምርጥ ረዳት ተዋናይት ዘርፍ በትህትና ፊልም አሸናፊም ሆናለች:: በማስታወቂያውም ታዋቂ የሆነው የቆርቆሮ ማስታወቂያ ጠብ ሲል ስደፍን የሠራች ሲሆን የሙዚቃ ቪዲዮዎችም ላይ ተሳታፊ ሆናለች::
የ2 ወንድ 2 ሴት ልጆች እናት እንዲሁም የ 2 የልጅ ልጆች አያት የሆነችው ዘነቡ በእድሜዋ መጨረሻ ላይ በጡት ካንሰር ተጠቅታ በሕክምና ላይ ነበረች:: በዚህ የተነሳም በመገናኛ ብዙኃን በተደጋጋሚ የቀረበች ሲሆን ባገኘችው አጋጣሚ ሁሉ ሴቶች በጡታቸው ዙሪያ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ስትመክር እና ሃገር ሰላም እንዲሆን ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ ስታሳስብ ኖራለች:: እሷ እንዲያ ትበል እንጂ በተለይ በዩቲዩብ እሷን አስመልክቶ የሚነዙት አሉባልታዎች ቀላል አልነበሩም:: በተደጋጋሚ ሞታለች እና ድናለች የሚሉ አላስፈላጊ አሉባልታዎች ዘነቡን እና መላ ቤተሰቧን ረፍት ሲነሱ ከርመዋል::
ከእለተ ዕረፍቷ በኋላ በምትወደው ራስ ቴአትር እሷን ለመዘከር በተዘጋጀ መርሐ ግብር ላይ ወዳጆቿ ስለ እሷ ብዙ የተናገሩ ሲሆን ከነዚህም መሐከል ራስ ቴአትር እንድትቀጠር ትልቁን ድርሻ የተወጣችው አርቲስት እመቤት ወልደ ገብርኤል በሲቃ የዘነቡን ልጆች በመንከባከብ ለሷ ያለንን ፍቅር እንግለጽ ስትል ጥሪ አቅርባለች::
ሌላኛው የጥብበ ሰው ረዳት ፕሮፌሰር ነብዩ ባዬ በበኩሉ የዘነቡን ሕይወት እና ባህሪ አወድሷል:: የዩኒቨርሰቲ የ4ኛ አመት ተማሪ እያለሁ ራስ ቴአትር ስመጣ ተቀብላ በፈገግታ ያስተናገደችኝ እና ባይተዋርነት እንዳይሰማኝ ያደረገችኝ እሷ ናት ብሏል ረዳት ፕሮፌሰር ነብዩ:: ለጥበብ ካላት ጽኑ ፍቅር የተነሳ ብዙ መስዋዕትነት በመክፈል ከቀደምት የሙያ አባቶቿ እነ ዮፍታሄ ንጉሴ ጋር እንደምትመሳሰል የተናገረው ረዳት ፕሮፌሰር ነብዩ ዘነቡ ብትቸገር እንኳን አማራሪ ሳትሆን አመስጋኝ እንደነበረች እንዲሁም የሁልጊዜ ሀሳቧ የምትወደው ራስ ቴአትር አድጎ ማየት እንደነበር ተናግሯል::
በእርግጥም ለጥበብ እና ለራስ ቴአትር ባላት ፍቅር ብቻ ሃገሯን ስታገለግል የኖረችው ዘነቡ ይህን ሁሉ ዘመን ስታገለግል ደሞዟ ሁለት ሺ አምስት መቶ ገደማ የነበረ ሲሆን ኑሮዋም የምቾት የሚባል አልነበረም::መኖሪያ ቤት እንኳን ለብዙ ጊዜ ያልነበራት ሲሆን በቅርቡ ኢንጂነር ታከለ ኡማ ከንቲባ በነበሩበት ወቅት በእጣ መኖሪያ እንዲደርሳቸው ከተደረጉ አርቲስቶች መሐከል አንዷ በመሆኗ ነበር የራሷ ቤት የኖራት:: እንዲያም ቢሆን ግን በብዙዎች ፊት ላይ ፈገግታን እየዘራች የመድረክ ድምቀት እና የታላቁ ራስ ቴአትር አምባሳደር እንደሆነች እስከህይወቷ መጨረሻ ዘልቃለች::
አቤል ገ/ ኪዳን
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 23 ቀን 2014 ዓ.ም