“ኢትዮጵያ ታምርት !”የሚለው መሪ ቃል ወይም ሞቶ አስኳል ወይም ሞተር ኢንዱስትሪው ነው። በአንድ ኢኮኖሚ ውስጥ ምርትን አገልግሎትን የማምረት ሒደት ኢንዱስትሪ ይሰኛል። በውስጡ ሰፊ ዘርፎችን ያካትታል። ማኑፋክቸሪንግ ፣ ኮንስትራክሽን ፣ ግብርና ፣ የማዕድን ፍለጋና ልማት ፣ መጓጓዣና መሠረታዊ አገልግሎቶች በዋናነት ይጠቀሳሉ። ለአንድ ሀገር ልማትና ዕድገት ኢንዱስትሪ ወሳኝ ዘርፍ ነው። ለዜጎች የስራ ዕድል ይፈጥራል። ለሀገር ሀብት ያካብታል። በአጠቃላይ ለሁለተናዊ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ቁልፍ ሚና ይጫወታል። ለዚህ ነው የዛሬ አመት የአምራች ኢንዱስትሪውን ችግሮች በቅርበት ለመፍታት እና የዘርፉን ምርትና የማምረት አቅም ለማሳደግ ዓላማ አድርጎ ኢትዮጵያ ታምርት የሚል ሀገራዊ ንቅናቄ የተጀመረው ፡፡
ባለፉት አመታት የአመራረት ዘዴና የምርት ውጤቱ በአዳዲስ ቴክኖሎጂና በሸማቾች ተለዋዋጭ ባህሪና ፍላጎት የተነሳ የኢንዱስትሪው ዘርፍ በማያቋርጥ የለውጥ ሒደት ላይ ይገኛል። የአውቶሜሽንና የዲጂታላይዜሽን መስፋፋት የኢንዱስትሪዎችን የማምረት ብቃትና ምርታማነትን በእጅጉ አሳድጎታል ። በአናቱ የበይነ መረብ ንግድ ወይም የe-commerce መስፋፋት የችርቻሮ ኢንዱስትሪውን ወደ አዲስ ምዕራፍ አሸጋገረው።ከቅርብ አመታት ወዲህ ደግሞ የ4ኛው ኢንዱስትሪ አብዮት ወይም የ”industry 4.0”አልያም የሰው ሰራሽ አስተውሎትና የሮቦቴክስ ወደ ኢንዱስትሪው መቀላቀል የዘርፉን መልከዓ እንደ አዲስ እየበየነው ይገኛል።
ዘርፉ በአኅጉራችንም ሆነ በሀገራችን ኋላ ቀርና ዘመኑን የማይዋጅ ነው ። እንደ ነዳጅ ፣ ጋዝ ፣ ማዕድንና የግብርና ውጤት ያሉ የተፈጥሮ ሀብቶችን ምንም አይነት እሴት ሳይጨምር ወደ ውጭ በመላክ ላይ የተንጠለጠለ ነበር ማለት ይቻላል። ከቅርብ አመታት ወዲህ ግን እሴት የተጨመረባቸውን በርካታ ምርቶችንና አገልግሎቶችን ወደ ውጭ መላክ ተጀምሯል። በአኅጉሩ ኢንዱስትሪ በተወሰኑ ዘርፎች ተስፋ የሚጣልባቸው ውጤቶች በመመዝገብ ላይ ቢሆንም ገና ያልተሻገራቸው በርካታ ተግዳሮቶች እንደ ሰሜን ተራሮች ጀብራ ከፊቱ እንደተገተሩ አሉ ። የመሠረተ ልማት ዕጥረት ፣ የፋይናንስ አቅርቦት ችግር ፣ የሰለጠነ የሰው ኃይል ዕጥረት ፣ ሙስና፣ የተንዛዛ ቢሮክራሲ ፣ የመልካም አስተዳደር ችግርና ሌሎች ። እነዚህ ተግዳሮቶች የአፍሪካንም ሆነ የሀገራችንን ኢንዱስትሪ ከምዕራባውያንና በመልማት ላይ ካሉ ሀገራት ጋር ተፎካካሪና ተወዳዳሪ እንዳይሆን ቀይደው ይዘውታል። እነዚህን ማነቆዎች ለመፍታት የፓሊሲ ማሻሻያና የመርሀ ግብር ለውጥ እያደረጉ ነው ።
የሀገራችንን ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያንና የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን በአብነት ማንሳት ይቻላል ። ከዚህ ጎን ለጎን መሠረተ ልማት ላይ ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ ኢንቨስት ማድረግ ፤ ለውጭ ባለሀብቶች ማበረታቻዎችን ማቅረብ ፤ የትምህርት ጥራትን ማሻሻልና ኢንዱስትሪው በተከፈተበት አካባቢ ያለን አምራች ኃይል ማሰልጠን ሰፋፊ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛል። የታዳሽ ኃይል መስፋፋት ፣ የመኑፋክቸሪንግ ዘርፉ መነቃቃትና የቴክኖሎጂ ኢንዱስትሪ ዕድገት ተስፋ የሚጣልባቸው ስኬቶች ተደርገው ሊወሰዱ ይችላሉ ። እነዚህ የኢንዱስትሪ ዘርፎች ሰፊ የስራ ዕድል የመፍጠር፣ ምርታማነትን የማሳደግና በአኅጉሩ የኢኮኖሚ ዕድገትን የማሳለጥ ሚና እንዳላቸውም ይታመናል ።
በተለይ ወደ ሀገራችን ስንመጣ በዜጎች የዕለት ተዕለት ኑሮ ላይ የሚፈለገውን ያህል ለውጥ እያመጣ ባይሆንም ላለፉት በርካታ አመታት ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት እየተመዘገ መሆኑ አይካድም ጥያቄው ዕድገቱ ፍትሐዊና አካታች ነው ፤ በዜጎች ገበታ ላይም ሆነ አኗኗሪ ላይ ለውጥ አምጥቷል ወይ የሚለው ነው ። የሀገሪቱ ጥቅል የሀገር ውስጥ ምርትም ሆነ የነፍስ ወከፍ ገቢው ቢያድግም፤ ኢኮኖሚው ላይ የገነገነው መዋቅራዊና ተቋማዊ ትብታብ ቱርፋቱ ለዜጎች እንዳይተርፍ አድርጓታል። የዋጋ ግሽበቱን ተከትሎ የተከሰተው የኑሮ ውድነት እና የተንሰራፋው ስራ አጥነት ጥላ እንደጣለበት ይገኛል። ሀገራችን ግዙፍና የተለያየ የግብርና ዘርፍ ቢኖራትም ፤ የውጭ ንግድ መር ማኑፋክቸሪንግ ላይም ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው።
በነገራችን ላይ ካለው እምቅ አቅም የተነሳ ቀደም ባሉት አመታት በኢንዱስትሪው ዘርፍ ላይ የተሰራው ስራ አዚህ ግባ የሚባል አይደለም። አሁንም ሀገሪቱ ካላት የሰው ኃይል ፣ ግብዓትና ገብያ አንጻር ሲታይ ዝቅተኛ ነው። መንግስት ይሄን በመረዳት ከፍ ብሎ ለመግለጽ እንደተሞከረው በኢንዱስትሪው ዘርፍ ለሚሰማሩ ኢንቨስተሮች የታክስ እፎይታ በመስጠት ፣ መሠረተ ልማት በማሟላት ፣ ሙስናን ለማስወገድ ፣ ማነቆዎችን በመፍታትና ቀልጣፋ የፋይናንስ አቅርቦትን በማመቻቸት ለውጥ ለማምጣት ጥረት እያደረገ ነው ። የጨርቃጨርቅ፣ የልብስ ፣ የሌዘር ፣ የቆዳ ውጤቶች ፣ ሲሚንቶና ሌሎች የግንባታ ቁሳቁሶች ከሀገሪቱ ኢንዱስትሪዎች ዋና ዋናዎች ናቸው ። ሌላው ትኩረት እያገኛ ያለው የኢንዱስትሪ ዘርፍ ቴክኖሎጂ ነው ። መንግስት የቴክኖሎጂ መንደርና መናኸሪያ ያቋቋመ ሲሆን ፣ የቴክኖሎጂ ፈጣሪዎችን በፋይናንስ እየደገፈና እያበረታታ ይገኛል ። በዘርፉ የተሰማሩ ኢንቨስተሮችን ለመሳብ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል ።
“ኢትዮጵያ ታምርት”ንቅናቄ የአገር ውስጥ ችግሮችና ዓለማቀፍ ጫናዎች የሚቋቋም ኢንዱስትሪ እስከመፍጠር እንደሚዘልቅ ፤ በአገር ውስጥና በውጭ ጫናዎች እየተፈተነ ያለውን ኢንዱስትሪ መታደግ የሚያስፈልግበት ነባራዊ ሁኔታ መፈጠሩን የኢንዱስትሪ ሚንስትሩ መላኩ አለበል የዛሬ አንድ አመት በዘርፉ የተደቀነበትን አደጋና የመውጫ መንገዱን ለኢዜአ መግለጻቸው አይዘነጋም። በጦርነትና በተከሰተው የኮቪድ 19 ወረርሺኝ ሳቢያ በርካታ ኢንዱስትሪዎች ስራቸውን አቁመዋል። ቀሪዎቹም ማምረት ከሚገባቸው ከ50 በመቶ በታች እያመረቱ ነው።
በተለያዩ የአለም አገራት የሚደረጉ ግጭቶች ወደ ውጭ በሚላኩና ከውጭ በሚገቡ ምርቶች ላይ ጫና በማሳደሩ ኢትዮጵያንና መሰል በማደግ ላይ ያሉ አገራት ኢኮኖሚ በከፍተኛ ሁኔታ እየጎዳው እንደሆነ እንደ ማሳያ ሊወሰድ ይችላል። ኢትዮጵያ በነዚህና በሌሎች የተለያዩ ችግሮች ሳቢያ የተጎዳውን ኢንዱስትሪ በዘላቂነት ለማቋቋም “ኢትዮጵያ ታምርት”የሚል ንቅናቄ መጀመሯን አስታውሰው ፤ “ኢትዮጵያ ታምርት”የሚለው ንቅናቄ በዓለም ላይ በሚያጋጥም ኢኮኖሚያዊ አሻጥሮችና ማዕቀቦች የሚረበሸውን ኢንዱስትሪ ለመታደግና ዘላቂ እድገት እንዲኖረው ያግዛል።’’ኢትዮጵያ ጠንካራና ተወዳዳሪ አገር ሆና ውጫዊ ጫናዎችን ለመቋቋም ያላትን አቅም አሟጣ መጠቀምና ማምረት ያለባት ጊዜው አሁን ነው ሲሉ ጥሪ አድርገው ነበር ።
ራስን መቻል የሉዓላዊነትና የክብር ጉዳይ ነው ያሉት ሚኒስትሩ በእጃችን ላይ ያለውን ሃብት ተጠቅመን የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ የምንቀይርበትን ንቅናቄ ጀምረናል። ንቅናቄው በ2022 ዓም እንደ አገር የበጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተያዘውን ዕቅድ ለመተግበር ሰፊ እድል ይኖረዋልም ።ኢትዮጵያ በርካታ ጸጋ እና ሰፊ የሰው ኃይል እንዲሁም የተመቻቸ ፖሊሲ ቢኖራትም ይህንን ወደ ሃብት የመቀየርም ስራ ይቀራታል ። የ”ኢትዮጵያ ታምርት”ንቅናቄ በኢንዱስትሪው ላይ የሚያጋጥሙ የአጭር ጊዜ ችግሮችን መፍታት ብቻ ሳይሆን ለረጅም ጊዜ የሚያጋጥሙ ስጋቶችን መፍትሄ እንዲሆን እየተሰራ ነው ።
ኢትዮጵያ ያላትን ጸጋዎች በመጠቀም በቀጣይ አስር ዓመታት ኢንዱስትሪው አገራዊ የምርት ድርሻው ከ6 .9 በመቶ ወደ 17 . 2 በመቶ ለማሳደግ ግብ ተጥሏል ። አገሪቱ በ2022 ዓም ከአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ በዓመት ወደ ውጪ ከሚላክ ምርት አሁን ከሚገኘው 4 መቶ ሚሊዮን ዶላር ወደ 9 ቢሊዮን ዶላር ማሳደግ ዋነኛ ዓላማው ነው ። በተጨማሪም የአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ የማምረት አቅም ወደ 85 በመቶ ማሳደግ እንዲሁም ከ5 ሚሊዮን ለሚልቁ ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር እየተሰራ ነው። ከተጀመረ አንድ አመት የሞላው የ’ኢትዮጵያ ታምርት’ንቅናቄ በርካታ ባለሃብቶች ወደ ስራ እንዲቡ፤ ባለድርሻ አካላትም ተቀራርበው መስራት እንዲችሉ አግዟል ።
የመንግስት ከፍተኛ አመራሮችን፣ ባለድርሻ አካላት፣ ሚዲያዎችና ሌሎችም ጉዳዮን ትልቅ አገራዊ አጀንዳ አድርገው በመንቀሳቀሳቸው በዘርፉ ትልቅ መነቃቃት ተፈጥሯል። የኢንዱስትሪዎችን የማምረት አቅም ለመጨመር የሀይል አቅርቦት፣ የመሬት፣ የሥልጠና፣ የብድር አቅርቦትና ተያያዥ ችግሮችን ለመፍታት ከባለድርሻ አካላት ጋር ከመቼውም ጊዜ በላይ እየተሰራ መሆኑንም ሚንስትሩ አክለዋል። አለማቀፍ ጫናዎች የሚቋቋም ኢንዱስትሪ እስከመፍጠር የሚዘልቀውን ንቅናቄ ተግባራዊነት ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ሚኒስትሩ ጥሪ አቀርበዋል።
የአምራች ኢንዱስትሪውን ችግሮች በቅርበት ለመፍታት እና የዘርፉን ምርትና የማምረት አቅም ለማሳደግ ዓላማ አድርጎ ኢትዮጵያ ታምርት በሚል የተዘጋጀ ሀገራዊ የንቅናቄ የተጀመረው የዛሬ አመት ሲሆን ፤ የሀገራዊ ንቅናቄው አላማዎች የአምራች ኢንዱስትሪውን ችግሮች በጋራ በመፍታት ለዘርፉ ዘላቂ ልማትና ተወዳዳሪነት ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር ዘርፉ ለኢኮኖሚያዊ መዋቅራዊ ሽግግር የበኩሉን አስተዋጽኦ እንዲወጣ ማስቻል ፣ በዘርፉ ያለውን የስራ ባህል ማሻሻል ብሎም የኢንዱስትሪ ምርቶችን ጥራትና ተወዳደሪነት በማሻሻል ገቢ ምርቶችን የመተካት ሽፋንን ማሳደግ የሚሉ ናቸው፡፡
እንደ ሃገር ያሉን ያልተነኩ ጸጋዎች (የግብርና፣ የማእድን፣ የቱሪዝም ሃብቶች) እና ከገበያ፣ ስትራቴጅካዊ አቀማመጥና ሌሎች ምቹ ሁኔታዎች ባለቤቶች ሆነን እንዴት በምንጠላው የድህነት አዙሪት ውሰጥ እንኖራለን በሚል ጥያቄ፣ አምራች ኢንዱስትሪዎች በገጠማቸው ዘርፈ ብዙ ችግር ምክንያት ከጊዜ ወደ ጊዜ የማምረት አቅም አጠቃቀማቸው መውረድ እና በ2022 ኢትዮጵያ ልታሳካ የያዘችው ትልልቅ ሃገራዊ የብልጽግና ግቦች ግፊት ለንቅናቄ መርሃ ግብሩ ዋና መነሻዎች መሆናቸውን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል በንቅናቄው ማስጀመሪያ ስነ ስርዓት ላይ መናገራቸው ይታወሳል ።
የግብአትና አቅርቦት ችግር ፣ የሰለጠነ የሰው ኃይልና የፋይናንስ እጥረት ፤ የቅንጅታዊ አሰራር ፣ የክትትል እና ድጋፍ ስርአት ደካማ መሆን እንዲሁም ከመፈጸምና ማስፈጸም አቅም ግንባታ ስራዎች ጋር በተያያዘ ዘርፉ እያጋጠሙ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት የሁሉም ባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ አሰራርና የአመራር ቁርጠኝነት ይጠይቃል ። በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ አስቻይ ሁኔታዎችና መፍትሄዎች ላይ መግባባት መፍጠር፤ የአምራች ኢንዱስትሪዎችን የማምረት አቅም ማሳደግ እና ለዜጎች ተጨማሪ የስራ ዕድል መፍጠር፤ የውጪ ምንዛሬ ግኝትን ማሳደግ እና ገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት የውጪ ምንዛሬን ማዳን ለ10 ተከታታይ አመታት ከሚቆየው የንቅናቄ መርሃ ግብር የሚጠበቁ ውጤቶች እንደሆኑ ተገልጿል፡፡
ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ በሚቀጥሉት 10 ዓመታትም ተጠናክሮ የሚቀጥልና ራሱን የቻለ ፕሮጀክት ቢሮ ተቋቁሞለት በጥብቅ ዲስፕሊን እየተመራ እንደሚገኝ፤ በማምረቻ ኢንዱስትሪ ላይ ያሉትን ነባራዊ ሁኔታዎች ከግምት ውስጥ በማስገባት በሀገር ምርትና ምርታማነት ላይ በማተኮር የሀገር ሉዓላዊነት አጀንዳም ጭምር መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል በወቅቱ በተለይ ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት መግለጻቸው አይረሳም። እንደሀገር ለኢትዮጵያ የማምረት ጉዳይ የህልውና ጉዳይ ነው።
የምንፈልጋት ጠንካራ ኢትዮጵያ እንድትኖር ለማድረግ ሁሉም ዘርፎች ማምረት አለባቸው። ለዚህ ምቹ መደላድል ለመፍጠር የኢንዱስትሪ ፖሊሲውን የማሻሻል፣ ልዩ ልዩ የአምራች ዘርፍ የማበረታቻ መመሪያዎች በመዘጋጀት ላይ ሲሆኑ ቅንጅታዊ አሠራሩን ለማዘመን የሚያስችሉ ስራዎች መጀመራቸው ፤ የአምራች ዘርፉን የሐገር ውስጥ ገበያ ድርሻ ከ30 በመቶ ወደ 60 በመቶ ለማሳደግ በተያዘው እቅድ መነሻነትም በቅርቡ የሐገር ውስጥ የቢሮ መገልገያ ቁሳቁሶችን (ፈርኒቸሮችን) በሀገር ውስጥ ገበያ ለመተካት የሚያስችል እንቅስቃሴ እንደሚጀመር በወቅቱ መገለጹ አይዘነጋም ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በተሰናበትነው ወር መጨረሻ በሚሌኒየም አዳራሽ የ“ኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ”ባስጀመሩበት ወቅት ፤ የበለጸገችና ለሁሉም ምቹ የሆነች ሀገርን ለመገንባት ኢንዱስትሪዎቻችንን በማሳደግ ዐቅም መፍጠር እንደሚገባ ፤ ፈጠራ በታከለበት መንገድ ፈተናዎችን በማለፍ ኢትዮጵያን አንደኛዋ ትልቁ ኢኮኖሚ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል ። በኢትዮጵያ የአምራች ኢንዱስትሪውን ለማነቃቃት በአገር አቀፍ ደረጃ እየተካሄደ በሚገኘው ውጤታማ ስራ ለዘርፉ ምቹ የሆነ አውድ በመፈጠር ላይ ነው ።
አክለውም ኢትዮጵያ ማምረት ትችላለች የምንለው በቂ መሬትና ማምረት የሚችል በቂ የሰው ኃይል ስላላት ነው ብለዋል ። በንጽጽር ሲታይም በአሁኑ ወቅት አምራች ኢንዱስትሪውን መደገፍ የሚያስችል የተሻለ የፋይናንስ እና የኃይል አቅርቦት አቅም እያደገ መጥቷል ። በማዕድን ዘርፍ የነበሩ መቀዛቀዞችን በማነቃቃት በርካታ ለኢንዱስትሪ ግብዓት ሊሆኑ የሚችሉ ምርቶች እየተመረቱ ይገኛሉ ። ለአብነት በቀጣይ ዓመት የሚመረቀው ለሚ የሲሚንቶ ፋብሪካ አሁን ኢትዮጵያ የምታመርተውን ሲሚንቶ ከ50 በመቶ በላይ ያሳድገዋል ።
በአምራች ኢንዱስትሪው ላይ እየተፈጠረ የሚገኘውን አስቻይ ሁኔታ በመጠቀም ግጭት፣ ጥላቻና መራራቅን በመተው ልማት እና ፈጠራን ማበረታታት እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል ። ዓለም ካለችበት አስፈሪ ሁኔታ አንጻር የተዘጋጀ፣ ያመረተ እና የሰከነ አገር ይሻገራል። ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ከፍተኛ ዕድገት እያመጡ ካሉ ጥቂት አገራት መካከል አንዷ መሆኗን ፤ በማዕድን ፣ በኢንዱስትሪና በሰው ኃብት ልማት ላይ ቀጣይነት ያለው ስራ ይከናወናል ። የልማት ስራዎች ፈተና አልባ አለመሆናቸውን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ፈተናዎችን በሕብረት በማሸነፍ የበለጸገች እና የጸናች አገርን ለትውልድ እናሸጋግራለን ብለዋል።
ላለፈው አንድ አመት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ለአራት ሺህ አዳዲስ ኢንቨስትመንቶች ፈቃድ መሰጠቱን ፤ የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ውስጥ ለአምራች ዘርፉ እንቅፋት የሆኑ ችግሮችን በመለየት ተከታታይነት ያለው መፍትሔ መስጠት የንቅናቄው ተቀዳሚ ዓላማ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገልጸዋል። ንቅናቄው የዘርፉን ማነቆዎች በመለየት አምራችነትን መገለጫ ባህል የማድረግ ተልዕኮ የያዘ ነው። በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ አበረታች ውጤት ማስመዝገብ ተችሏል ያሉት ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ ጸጋ በመጠቀም ፈጣን እድገት እንድታስመዘግብ እየተሰራ ነው።
በሂደቱም በአምራች ኢንዱስትሪው ላይ የሚስተዋሉ ማነቆዎችን በመለየት ዘላቂና ቀጣይነት ያለው ተቋማዊ የመፍትሔ አቅጣጫ መቀመጡን አስረድተዋል። በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ስራ አቁመው የ ነበሩና ወደ ሥራ እንዲገቡ የተደረጉ ከ352 በላይ ኢንዱስትሪዎችን እንዲሁም 635 አዳዲስ ኢንዱስትሪዎች ማምረት ጀምረዋል ። ለ4000 አዳዲስ ኢንቨስትመንቶች ወደ አምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ለመግባት ፈቃድ ተሰጥቷል። አገልግሎት አሰጣጥን በማሻሻል የተቋማት ቅንጅታዊ አሰራር እያደገ መምጣቱንና በንቅናቄው የተገኙ ውጤታማ ተግባራትም ቀጣይነት ባለው መልኩ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አቶ መላኩ ተናግረዋል።
ሻሎም ! አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 6/2015