የመንደርደሪያ ወግ፤
ለዚህ ጽሑፍ የሰጠሁትን ርእስ በተመለከተ ከአሁን ቀደም ባስነበብኳቸው በርካታ ጽሑፎቼ የማጠቃለያ ሃሳብ በማድረግ ለመልካም ምኞት መደምደሚያነት ስጠቀምበት መቆየቴ ይታወቃል። ለወደፊቱም ቢሆን በዚሁ መቀጠሌ የሚቀር አይመስለኝ። “ስለምን ይህንን ርእሰ ጉዳይ በዚህ ወቅት ጎላ አድርጎ ለማስታዋስ አስፈለገ?” ተብዬ ብጠየቅ፤ ምክንያቱን አብራርቼ ባልገልጸውም ለአንባቢዎቼ ይጠፋቸዋል ብዬ አልገምትም። ቢሆንም ግን “በገመምተኛው ሀገራዊ ሰላማችን ላይ” ጥቂት ሃሳቦች መፈነጣጠቁ ይበጅ ስለመሰለኝ በግል ምልከታዬ ላይ ጥቂት መቆዘሙን መርጫለሁ።
በዚህ ወቅት ሀገሬን የራባት ዋነኛ ጉዳይ “የሰላም እጦት” እንደሆነ መገለጫው ሌላ ሳይሆን እኛ የሰላም ርሃብተኛ ዜጎች ነን። ስለ ሰላም ሲነሳ ብዙ የሚነካኩ ጉዳዮች እንደሚኖሩ አይጠፋኝም። “ኦ! ሰላም በስምሽ ስንት ግፍ ተሠራ?” የሚለውን ጯሂ ሃሳብ ለመጽሐፍ ርእስነት የተጠቀመው ኃይለ ሥላሴ ደስታ የተባለ የሀገራችን ቀደምት ደራሲ ሲሆን የመጽሐፉ የኅትመት ዘመን ደግሞ 1962 ዓ.ም ነበር።
ከሃምሳ ሦስት ዓመታት በኋላ ይህንን ርእሰ ጉዳይ እንደ አዲስ መቀስቀሳችን ቢቸግረንና ግራ ቢገባን ነው። ቅዱስ መጽሐፍ “ሰላምን ግዛት እንጂ አትሽጣት” ቢልም፤ በጊዜያችን እየተስተዋለ ያለው ግን ተቃራኒው ነው። ሰላምን ከውይይት ገበያ ለመግዛት ከመሽቀዳደም ይልቅ “ሰላምን በማንበርከክ ገብሪ!” እያሉ ማስፈራራቱ የተላመድነው ክስተት ሆኖ ከታመመን ሰነባብቷል።
እኮ ስለምን…!?
ሀገሬ በሰላም ውላ እንድታድር በየዕለቱ ከዜጎችና ከተቋማት፣ ከቡድንና ከጀማው የሚዥጎደጎደው ምርቃቱ፣ የጸሎቱና የዱዓው ዓይነት በክረምት ዶፍ ሊመሰል ይችላል። ችግሩ፡- ምርቃቱም ሆነ ምኞቱ፣ ጸሎቱም ሆነ ዱዓው፣ በኪራላይሶን የሚታጀበው ምልጃም ሆነ በኤሎሄ መቃተት የሚፈጸመው የሃይማኖት ቤተሰቦች ጩኸት ወደ ፈጣሪ መንበር ደርሶ ስለምን ፈውስ እንዳልመጣልን ብንሞግት ፈጣሪን እንደመዳፈር ተደርጎ ሊቆጠርብን አይገባም። ለጊዜው የሥነ መለኮቱ ድምዳሜም ሆነ የሊቃውንቱ ግምት ምንም ይሁን ምን ዋናው ጉዳይ ሀገራችን ሰላም ርቧት እያነባች መሆኑን ግን መካድ አይቻልም። የማሕበረሰብ የጥናት ዘርፍ ምሁራንም ቢሆኑ ለመፍትሔ ጥቆማው ግራ መጋባታቸው አይቀርም ብለን ብንጠራጠር አይፈረድብንም።
እንደ እውነቱ ከሆነ ለሰላም ርሃባችን ማሳበቢያዎቹ አሻግረን ጣት የምንቀስርባቸው ባዕዳንና የውጭ ባላንጣዎቻችን ሳይሆኑ ተቀዳሚውን ኃላፊነት መውሰድ ያለብን እኛው ራሳችን ልንሆን ይገባል። “ራሳችን ነን!” ብለን ስንል ደግሞ ጥቆማው እከሌ ተእከሌ፣ ያኛውና እነዚያ የምንላቸው ሳይሆኑ ከታች እስከ ላይ ያለውን ዘረ ኢትዮጵያ በሙሉ የሚመለከት ነው። ምናልባትም ይህንን እውነታ በዜማ በታሸ ግጥም እናጎላምሰው ካልን የሚከተሉትን ስንኞች ከጥላሁን ገሠሠ በመዋስ ልንጠቀምባቸው እንችላለን።
“በአንዱ ስትጠቁም ከጣቶችህ መሃል፣
ሦስቱ ግን ራስህን ይመለከቱሃል።
“አዝማች፡- አመልካች ጣት!”
ከረጅም ዓመታት በፊት ድምጻዊው እንዳንጎራጎረው ዛሬ ለምናማረርበት የሰላም ርሃባችን ምክንያቱ “እከሌ ወይንም እነ እከሌ ናቸው” ብለን በአመልካች ጣታችን ወደ ሌሎች ስንጠቁም፤ በሦስቱ ጣታችን ወደ ራሳችን መጠቆማችን እንደሆነ ልንገነዘብ ይገባል። በዜማው ግጥም ውስጥ ያልተጠቀሰው አራተኛው አውራ ጣታችን ደግሞ ወደ ፈጣሪ አቅንቶ “አንተስ? አንቺሽ? ንጹሕ ነሽ? ንጹሕ ነህ?” ብሎ እንደሚሞግተን ልብ ልንል ይገባል።
ቀደም ባሉት ዘመናት አንድ ሰው (ወይንም በርከት ያሉ የቤተሰብ አባላትም ሊሆኑ ይችላሉ) ከመኖሪያ አካባቢያቸው ራቅ ብለው ዘመድና ወዳጅ ጠይቀው ከሰነባበቱ በኋላ ወደ አድራሻቸው ለመመለስ ሲነሱ ወይንም መጓጓዣ መኪኖች ላይ ሲሳፈሩ በእንግድነት የሰነበቱበት የቤተሰብ አባላት ለመንገደኞቹ “በሰላም መድረስህን፣ መድረስሽን፣ መድረሳችሁን” በደብዳቤ ግለጹልን መባባል የተለመደ ነበር። ቴክኖሎጂው እየተስፋፋ ሲሄድም “ደህና መድረሳችሁን ደውላችሁ ንገሩን” መባል የባህል ያህል የጠነከረ የመተሳሰቢያ መገለጫ ነበር።
ዛሬ ዛሬ ግን ከመኖረያ አካባቢ ትንሽም ቢሆን ራቅ ከተባለ በደህና ለመግባትም ሆነ በመንገድ ላይ ተደናቅፎም ሆነ ውደቆ መቅረትን ተሽቀዳድመው “ወሬውን ወይንም መርዶውን” የሚበትኑት በየማኅበራዊ ሚዲያው የነገሱት ቡድኖች ወይንም ግለሰቦች ናቸው። ወሬውና መርዶው ደግሞ እውነት ብቻም ሳይሆን በፈጠራ ተቀነባብሮ ቤተሰባዊውንና ማሕበረሰባዊውን ሰላም የሚያደፈርስና ጭንቀት ላይ ጥሎ ምንም ነገር ሳይፈጠር ለእዬዬ የሚዳርግ ሊሆን ይችላል።
ለሀገሬ የሰላም እጦትና መናጋት ዋናዎቹ መንስዔዎች በክፋት ግብር ለቅሚያ የተደራጁ የጫካ ሽፍቶችና ዘራፊዎች፣ ለሽፋንነት እንዲረዳቸው የፖለቲካ ጭምብል ያጠለቁ ዓላማ ቢስ ጨካኞችና ደም የተጠሙ ክፉዎች ወይንም የጎዳና ላይ ቦዘኔዎችና ነውጠኞች ብቻም ሳይሆኑ በክብደቱ ከፍ ያለ ዋጋ የምንሰጠው በማኅበራዊ ሚዲያው ላይ የሚፈነጩት የሀሰት መፈልፈያ ግለሰቦችና ቡድኖች ጭምር መሆናቸው ሊዘነጋ አይገባም።
በዚህም ምክንያት በዚያም ተባለ በዚህ ምንም ማመካኛ ልንሰጥበት በማይገባ ድፍረት እንግለጽ ካልን ሀገራዊ ፖለቲካችን ታሞ አልጋ ላይ መዋሉን ማስተባበል በፍጹም አይቻልም። የሃይማኖት ተቋማትም ቢሆኑ በራስ ቤትና እርስ በእርስ በተፈጠሩ ሽኩቻዎችና “ምድራዊ በሆኑ የእኔ እበልጥ ፉክክሮች” መንፈሳዊው አቅማቸው ጤና አጥቶ ህመምተኛ ሆነው እያቃሰቱ እንዳሉ የየቤታችን ገመናና ፈተና በማሳያነት ሊጠቀስ ይችላል።
ኢኮኖሚያችንና ኑሯችንም እስትንፋሱ ጭል ጭል እያለ መተንፈስ ተስኖት ሲያጣጥር የምናየው በራሳችን የዕለት ተዕለት አኗኗር ውስጥ ነው። የእርስ በእርስ ማኅበራዊ ግንኙነታችንና ተራክቧችንም “በየራሳችን ቋንቋና ብሔር ስም በለጠፍናቸው ልዩ ልዩ ታፔላዎች” አማካይነት እየሰለለና እየመነመነ በመሄድ ላይ እንዳለ በብዙ ማስረጃዎች ማረጋገጥ ይቻላል።
ስለዚህም ነው፤ “የሰላም ርሃብና ጥማት” ሀገሬን የውጥር ይዞና መተንፈሻ አሳጥቶ ጭርሱኑ አልጋ ላይ እንድትውል እየተዘመተባት ያለው። “ተመኑ ይህ ልክህ” የማይባለውን የሰላም እሴት በተመለከተ ከአሁን ቀደም በዚሁ አንጋፋ ጋዜጣ ላይ “የሰላም ዋጋው ስንት ነው? የዋጋው ተመን የሚመዘነውስ በምንድን ነው?” በሚሉ ርእሰ ጉዳዮችና ሃሳቦች ላይ የግሌን ነጻ ሃሳብ መሰንዘሬ አይዘነጋም።
ዛሬም ያንኑ ርእሰ ጉዳይ ደግመን እናስታውስና በርግጡ “የሰላም ዋጋው ስንት ነው? ዋጋው የሚተመነውስ በምን መስፈርት ወይንም መለኪያ ነው? እስከ መቼስ ሀገራችን በሰላም እጦት አልጋ ላይ ወድቃ እያቃሰተች እንድትኖር እንፈርድባታለን? ሰላም እየደፈረሰ ሀገር ስትታወክ የሚጠቀመው ማን ነው? ጥቅሙስ ምንድን ነው? ተጠቅሞስ የት ለመድረስ ነው?”
በእነዚህ መሠረታዊ ጥያቄዎች ዙሪያ መወያየቱ የቀጠሮ ቀን የሚቆረጥለት ወይንም በይደር የሚተላለፍና “በይደርሳል” የምንዘናጋበት ጉዳይ ሳይሆን በዛሬዋ ጀንበር ልንመክርበት የሚገባ የጋራ ብሔራዊ አጀንዳችን ሊሆን ይገባል። “መወያየቱ ምን ሊረባ?” ብለን ተስፋ መቁረጡ ይብስን ለመቀበል ራስን ከማዘጋጅት ሌላ ምን ፋይዳ ይኖረዋል። በዝምታ፣ በኩርፊያና በአያገባኝም ግዴለሽነት ራስን ማግለሉ መከራን ያከብድ ካልሆነ በስተቀር ምንም ትርፍ ይገኝበታል?
እንደዚህ ጸሐፊ ምኞት ቢሆን ከመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች እስከ ተራ ዜጋ፣ ከፖለቲካ ልሂቅ እስከ ሃይማኖት መምህር፣ ከተማሪ እስከ መምህር ፣ ከነጋዴ እስከ ለፍቶ አደር፣ ከሹም እስከ ሐኪም፣ ከእቁብተኛ እስከ እድርተኛ፣ ከገበሬ እስከ ወታደር፣ ከፕሮፌሰር እስከ ለጥበብ አደር ወዘተ.፤ ዝርዝሩን ላልዘልቅበት ጀመርኩት እንጂ፤ ሁሉም የሀገር ልጅ በያገባኛል ስሜትና በራሴ ጉዳይነት መንፈሱን አስክኖ ለታመመው ሀገራዊ ሰላማችን በአንድ ድምጽ ተባብረን “ምን ነክቶን ነው? ምንስ አስነክተውን ነው?” ብለን በመጠየቅ ግራ ለተጋባንበት የሰላም ሕመማችን ልብ ተቀልብ ሆኖ መወያየቱ የግድ ይላል።
ያለበለዚያ የተለያዩ ራስ ተኮር ጥቅሞቻቸው እንዳይነኩባቸው ወይንም የሚመኙት እንዲሳካላቸው በእብደትና በእብሪት ከሚቃዡና ከታወሩ ፀረ ሰላም የማሕበረሰብ ተባዮች ጋር አብሮ በማበድ ጨርቅን እየጣሉ መክነፍ በሀገሪቱ ዕጣ ፈንታ ላይ ብቻ ሳይሆን በራስም ላይ መከራ ከመጋበዝ ውጪ ሌላ ውጤት ሊያስከትል አይችልም። ይህ ተግባር በርግጥም ተፈጻሚ እንዲሆን ደግሞ ከእያንዳንዱ ዜጋም ሆነ በየሙያ ዘርፋቸው “አንቱታን” ካተረፉ ዜጎች ውጤታማ የተግባር እርምጃ ይጠበቃል። ሌላው ቀርቶ ሰሚ ጆሮና አሰላሳይ ልቦና ካላቸው እየተነቀፉና እንዲታረሙ እየተመከሩም ጭምር አልሰማ ብለው በተደፈነ ልብ በጥፋት ምህዋራቸው ላይ የሚሽከረከሩ ዜጎችም ቢሆኑ ሀገር እንድትፈወስ ከፈለጉ በሚከተለው አንድ መሠረታዊ የግል ውሳኔ ላይ መድረስ የግድ ይላል።
በጎ ፈቃድ!
የኢትዮጵያ መከራ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲያበቃ፤ መከራዋ ምክንያት ሆኖ የተጎናጸፈችው የሀዘን ማቅም ከላይዋ ላይ ተቀዶ እንዲወገድና እርሷም በእፎይታ እንድትተነፍስ፣ ዜጎችም በሰላም ውለው በሰላም እንዲያድሩ መወሰድ የሚገበው ቀዳሚው እርምጃ ያለ ተጨማሪ አማራጭ አንድና አንድ ብቻ ነው። ለበጎ ፈቃድ ራስን ማዘጋጀትና ማስገዛት።
በጎ ፈቃድ ከፖለቲካ ፕሮግራም የሚመነጭ ርዕዮተ ዓለም ወይንም ከሃይማኖቶች ቀኖናና ዶግማ የሚቀዳ መንፈሳዊ መርህም ሆነ መመሪያ አይደለም። በፍጹም። በጎ ፈቃድ በጸሎትም ሆነ በዱዓ ፈጣሪን በመማጸን እጎናጸፈዋለሁ የሚባልለት ትሩፋት አይደለም። በጎ ፈቃድ ራስን ገዝቶና ኅሊናን አድምጦ በራስ መልካም ውሳኔ የሚተገበር የሰብኣዊነት መገለጫ ነው። ጠንከር እናድርገው ከተባለም በውጭ አካል አስገዳጅ ግፊት፣ ማስፈራሪያም ይሁን ማባበያ ወይንም ትዕዛዝ በጎ ፈቃድን መጎናጸፍ ከቶውንም የሚቻል አይደለም። እያንዳንዱ ዜጋ በራሱ ፈቃድ በጎነትን የውስጣዊ እሴቱ መርህ አድርጎ የሰላም መልእክተኛ ካልሆነ በስተቀር ስለ ሰላምና ሰላማዊነት ተነጋግሮም ሆነ ተመካክሮ ለመግባባት ማዳገቱ አይቀሬ ይሆናል።
መልኩና ዓይነቱ ይለያይ ካልሆነ በስተቀር የሰላም መሠረት ያልተናጋበት አህጉርና ሀገር ይኖራል ለማለት ያዳግታል። የአንዳንድ ሀገራት ዜጎች በሰላም ወጥቶ መግባት ብርቅ ስለሆነባቸው የዕለት ተዕለቱ እንቅስቃሴያቸው በጥይት መካከል በመሹለክለክ ከሞት ጋር ድብብቆሽ የመጫወት ያህል እጅግ የከፋ ነው። በአንዳንድ ሀገራት በሕጻናት ት/ቤቶች ውስጥ ሳይቀር የሚፈጸሙት የአጥፍቶ መጥፋት ግድያዎች በእጅጉ እየተበራከቱ በመሄድ ላይ ናቸው።
“ብልህ ሰው ከጎረቤቱ ይማራል” እንዲሉ የቅርባችን የእህት ሀገር ሕዝቦች በእርስ በእርስ ጦርነት እየታመሱ ሲጨራረሱ እያየንና እየሰማን ነው። በእኛም ሀገር ያለፍንበት የትናንት ከትናንት ወዲያ መሰል ቁስል ገና ጠግጎ ፈውሳችን ሙሉ አልሆነም። እናስ በዚያም ተባለ በዚህ የሰላምን ርግብ በማቁሰል እኛ ምን ትርፍ እናገኛለን? ዜጎች በሰላም ውለው እንዳይገቡና ተረጋግተው ተግባራቸውን እንዳይከውኑ በማሳቀቅስ ምን ይሉት የፖለቲካ ምርት ይመረታል? “ጥያቄ አቅርቤያለሁ መልስ ብትሰጡኝን” ያለው ዜመኛ ለካንስ ቢቸግረው ኖሯል። ሰላም ለሀገራችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ።
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 5/2015