የሰላም ድምጽ የኩራትና የሉአላዊነት ፋና ወጊ ሆኖ ለዘመናት ዘልቋል። የሰው ልጅ ትልቁን ጥያቄ ሰላም ያደረገው ከዚህ የኩራትና የደህንነት ስሜት በመነጨ መንፈስ ነው። እንደ አገር ይሄን እውነት በመፈተሽ ሀሳብ እንለዋወጣለን።
ኢትዮጵያ ምን አጣች? ስል በጥያቄ ጀምሬያለሁ። ይሄ ጥያቄ የጋራ ጥያቄአችን ነው፣ የምንመልሰውም በጋራ ነው። እርግጥ ያጣነው ምንም የለም፤ ተፈጥሮ ሙሉ አድርጋ ነው የፈጠረችን። አንድ ነገር ግን ይጎድለናል እላለሁ . . . እሱም ተነጋግሮ መግባባት ነው። ተነጋግሮ ባለመግባባት ብዙ እሴቶቻችንን አጥተናል። ያልጠፋ የሰው ሕይወት፤ ያልወደመ ሀብትና ንብረት የለም።
የሰሜኑን ጦርነት ጨምሮ ሌሎች ዋጋ የከፈልንባቸውን አጋጣሚዎች ብናስታውስ እንኳን ተነጋግሮ ባለመግባባት የመጡ እንደሆኑ እንደርስባቸዋለን። እርግጥ ተነጋግሮ ለመግባባት የሁለት ኃይሎች ፍቃደኝነት ያስፈልጋል። ተነጋግሮ ለመግባባት የአንድ ወገን ፍቃደኝነት ብቻውን ዋጋ የለውም።
አንዱ ሰላምን እየፈለገ አንዱ ጦርነትን በሚፈልግበት ሁኔታ ላይ ተነጋግሮ መግባባት አዳጋች ነው የሚሆነው። የአገራችን ሁኔታም ይሄን እውነት የተላበሰ ሆኖ እናገኘዋለን። ሰላም በሚፈልጉና ነውጥ በሚፈልጉ ቡድኖች መካከል አገር ፀንታ መቆም አትችልም። አገር በጽናት እንድትቆም ሰላም ፈላጊና የሰላምን ዋጋ የተረዳ መሪና ተመሪ ያስፈልጋታል።
አበው ሲተርቱ ባለመናገር ደጃዝማችነት ይቀራል ይላሉ። እውነት ነው ባለመነጋገራችን ደጃዝማችነታችንን አጥተናል። ሰላማችንን አጥተናል። ክብራችንን፣ ከፍታችንን ተነጥቀናል። ባለመነጋገራችን ወደ’ማይገባንና ወደ’ማይመጥነን እልቂትና ትንቅንቅ ገብተናል።
የሰላም አማራጮችን እየዘጋን የመገፋፋት መንገዶችን ስንጠርግ እንደነበር ያለፉ ታሪኮቻችን አስታዋሾቻችን ናቸው። ይህ ዓይነቱ አካሄድ አገርን ከማቀንጨር፣ ትውልድን ከመመረዝ ባለፈ ይሄ ነው የሚባል የልዕልና ስም አልሰጠንም። ዓለም ላይ በጦርነት የከፋ ታሪክ ያላቸውን አገሮች ብንመለከት ሁሉም ታሪካቸውንና መሠረታቸውን ያበላሹ ሆነው ነው የምናገኘው።
ሰላም በመነጋገር ውስጥ፤ ጦርነት ደግሞ በእልህ ውስጥ የሚፈጠሩ ነገሮች ናቸው። በመነጋገር ሰላምን ማምጣት እየቻልን በእልህ ወደ ጦርነት የምንገባው ለዘመናት የተጠናወተን ልክፍት መች እንደሚለቀን አይገባኝም። ዛሬም ብዙ ነገር ባጣንበት፣ ብዙ ነገራችንን ባሳጣን የጦርነትና የራስ ወዳድነት አስተሳሰብ ውስጥ ነን።
የስቃዮቻችን ፈጣሪዎች ራሳችን ነን። በሰሜኑ ጦርነት ምን ያክል ዋጋ እንደከፈልን እማያውቅ ካለ እሱ እዚህ አገር የለም ማለት ነው። ከፕሪቶሪያው ስምምነት ወዲህ የታየውን የአንድነትና የሰላም መንፈስ ስናይ ሰላም ይህን ያክል ደስታን ከሰጠን፣ ጦርነትን መሻታችን ለምን ይሆን የሚል ጥያቄን ያስነሳል።
እንደ አገር ብዙ ችግሮች አሉብን። ሁሉም ችግሮቻችን ግን በጠረጴዛ ዙሪያ መፈታት የሚችሉ ናቸው። ከሰላም የላቀ፣ ከሰላም የተለቀ ችግር በዓለም የለም። ችግሮቻችን ከሰላም ተልቀው ወደ ጦርነትና ሞት እንዲወስዱን ዕድል የምንሰጣቸው ራሳችን ነን። ከዚህ በኋላ ባለው የፖለቲካም ሆነ የማህበራዊ መስተጋብር ውስጥ ጥልን በፍቅር፤ ቂምን በይቅርታ፤ ጦርነትን በሰላም በማሸነፍ ሞት የበቃባት አገር መፍጠር የሁላችንም ድርሻ ይሆናል።
በአገራችን የማንክዳቸው በርካታ ሀቆች አሉ። ፖለቲካችን በብሔር የተመረዘ ነው። ፖለቲከኞቻችን ከራስ ወዳድነት የፀዱ አይደሉም። ኮሽ ባለ ቁጥር ጎራዴ የምንመዝ፣ ሽመል የምናነሳ፣ መሣሪያ የምንነቀንቅ ነን። እነዚህ ልማዶቻችን የአገራችንን መልክ ከመቀየራቸውም ባለፈ በእድገትና በልማቱም ረገድ ጎታታ እንድንሆን ፈርደውብናል።
ሌላው የማንክደው ሀቅ ቢኖር አገራችን በሰሜኑ ጦርነት ብዙ ኪሳራ ደርሶባታል። የሞት፣ የአካል መጉደል፣ የንብረት መውደም፣ የመፈናቀል ወዘተ እና ሌሎች የማይተኩና በታሪክ እንደመጥፎ የሚታወሱ ነውሮችን አስተናግደናል። ካለፈውም ሆነ ካለው ልንማረው የሚገባ አንድ ነገር ቢኖር የሰላምን ዋጋ ነው።
የሰላም ዋጋ አቻ ትርጓሜ የለውም። አንዳንድ ፈላስፎች ዓለም ከሰላም ውጪ ሁሉን አጥታ መኖር እንደምትችል ይገልጻሉ። ይህን የፈላስፎች ንግግር ዘርዘር አድርገን ብናየው የዓለም ታሪክ ሁለት ዓይነት መልክ ያበጀው በትንሽ ሰላምና በብዙ ጦርነት ነው ይላሉ።
አሁን ላይ እዚህም እዛም የምንሰማቸው ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ኃያላን ነን በሚሉ ራስ ወዳዶች የፈጠሩት የጥፋት ዋጋ ሲሆን፤ ይህ የዓለምን መልክ ወደ አንድ እንዲያጋድል አድርጎታል ሲሉ ይናገራሉ። በተቃራኒው የሰው ልጅ ስቆና ተደስቶ የሰላም አየር ተንፍሶ የኖረባቸው በጣት የሚቆጠሩ ጊዜያቶች ዓለም በእርቅና በመረጋጋት ባስተናገደችው የሰላም እሳቤ የሆነ እንደሆነ ይጠቁማሉ።
የሰላም ማጣት በድሀ አገር ላይ በቦሀ ላይ ቆረቆር ነው። አከን ባልሻርነው ቁስል ላይ ሌላ የማይድን ቁስልን ማከል ነው። በተለይ በፖለቲካው ምህዳር አከን ያላሻርነው፣ በመጣውና በሄደው እየታከከ የመረቀዘ የፖሊቲካ ሥርዓት ያለን ሕዝቦች ነን። በኢኮኖሚውም እንዲሁ ለብዙ አመት ታኮ ያልሻረ፣ እየመረቀዘና የቆላ ቁስል እያበጀ ያለ የኢኮኖሚ ግንባታ ነው ያለን።
ዘር ያልገባበት፣ ብሔርተኝነት ያልተነሰነሰበት . . . ማህበራዊ መስተጋብር የለንም። ይህ ሁሉ አልድን ያለ ቁስል ባለባት አገር ላይ ጦርነትና አለመግባባት ታክለውበት የሚሆነውን አስቡት። በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ሲያንሰን ነው። እንደ አገር እንቅርቱ ብቻ በቂያችን ነው። ድህነት የወለደውን፣ ኋላ ቀርነት ያሳደገውን እንቅርታችንን ሳናሽርና ሳናፈርጥ ሌላ ጣጣ የሚያስፈልገን አይደለንም።
የድህነት እንቅርታችንን አፍርጦ ባጣነው ያክል የሚክሰን የሰላም ዋስትና ያስፈልገናል። መንግሥት በአሁኑ ሰዓት ለሰላም ቅድሚያ ሰጥቶ እየሠራ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው። ከሁሉም ወገን ጋር የተጀመረው ሰላም ፍሬ አፍርቶ ጦርነትና አለመግባባት ያወየባትን አገራችንን ነፃ የምናወጣበት አዲስ አስተሳሰብና አዲስ ልምምድ የምናስተናግድበት ጊዜ ላይ ነን።
አሁን ከየትኛውም እውቀት በላይ ሊገባን የሚገባው አንድ ነገር ብቻ ሲሆን፤ እርሱም የሰላም እውቀት ነው። አገር በሰላም እውቀት ካልተመራች፣ ማኅበረሰብ በሰላም እውቀት አብሮ እስካልኖረ ድረስ ለእድገትና ለለውጥ የምናደርገው ጥረት ፍሬ አልባ ነው የሚሆነው። ያጣነው ታሪክ አይደለም፣ ያጣነው ምቹ አገር አይደለም። ያጣነው ከፉክክር ወደ ምክክር፣ ከነውጥ ወደ ለውጥ ለመግባት የተሰናዳ ሥነልቦና ነው።
ሀሳቦቻችን ሰላምን እንዲወልዱ፣ አንድነትን እንዲጸንሱ ዕድል ልንሰጣቸው ይገባል። ሀሳቦቻችን ወደ እርቅ የሚወስዱ፣ ወደ ምክክር የሚያደርሱ መሆናቸውን ማጤን ወደ ድል እና ዕድል የሚወስዱን ጎዳናዎቻችን ናቸው። አገራችን ሰላማዊ ሀሳብ ይጎድላታል። ሀሳቦቻችን ነውጥ ፈጣሪዎች ሆነው አሳምመውን ያውቃሉ።
በተማሩትም ባልተማሩትም የሚፈበረኩ ሀሳቦች ለአገራችን የሚበጁ ሳይሆኑ ለጥቂት ቡድኖች የሚበጁ ሲሆኑ አይተናል። ሀሳብ ሲፈጠር አገርና ሕዝብን ታላሚ አድርጎ ነው። አገርና ሕዝብ የሌሉበት ሀሳብ አላማው ልማት ሳይሆን ውድመት መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ነው።
ሰላምም ሆነ ጦርነት ከሀሳብ የሚጀምሩ ናቸው። መልካም ቃል ሁልጊዜም የሕይወት ምንጭ ነው። መልካም ቃል አጥተን ነው በምንም የማይተካ ሕይወታችንን ለሞት ስንገብር የምንታየው። ለውጥ መሠረቱ መልካም ቃል ነው። እንደ ብዙሀነታችን ብዙ ሀሳቦችን ልናስብ እንችላለን ከዚያ ብዙ ሀሳብ ውስጥ ለአገር የሚበጀውን በመምረጥ ለሁላችን የምትበቃን ኢትዮጵያ መሥራት እንችላለን።
ሀሳብ አላጣንም። ሀሳብ አጥተንም አናውቅም። ግን በሀሳቦቻችን መካከል የመከባበርና የመቻቻል ዝንባሌ የለም። እኔ ያልኩት ካልሆነ በሚል የእልኸኝነት አውድ ውስጥ የቆምን ነን። ሀሳብ ያለ ትዕግስትና ያለቅንነት፣ ሀሳብ ያለ መቻቻልና ያለመከባበር ዋጋ የለውም።
ባቢሎናውያን ትልቁን ግንብ ለመገንባት ሲነሱ እንደ አላማ የያዙት ከፈጣሪ ጋር መገዳደርን ነበር። ማሰብ ቢችሉ ኖሮ ፈጣሪ የሚበቃቸውንና የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ ሰጥቷቸው ነበር። ግን በዚያ ሳይረኩ ሰማይ የሚደርስ ግንብ እንገንባ ብለው ተነሱ። እንዳሰቡት የሆነ ምንም የለም። ቋንቋቸው ተዘበራረቀና እንኳን ሰማይ ጠቀስ ግንብ ሊገነቡ ቀርቶ በሀሳብ ሳግባቡ ቀርተው ያላቸውን አጥተዋል።
እኛም ያለንን እያጣን ነው። ፈጣሪ ከሌላው አገርና ሕዝብ የተለየች ቅዱስና መልካም፣ በተፈጥሮ ሀብቷ የታደለች፤ በሁሉም ነገሯ የሚቀናባትን አገር ተሰጥቶናል። ከእኛ የሚጠበቀው በአንድነትና በፍቅር፣ በእርቅና በምክክር ይቺን አገራችንን ማበልጸግ እንጂ እንደባቢሎናውያን የማይሆን ነገር ሽተን ፈጣሪ ከማይወደው ጥልና ክርክር፣ ዘረኝነትና ብሔርተኝነት ውስጥ ተዘፍቀን ጸጋችን እንዳይሰወርብን እፈራለሁ።
አገራችን ሰላም እስካልሆነች ድረስ መጪው ጊዜ ሁላችንንም ነው የሚያስፈራን። መጪው ጊዜ ተምረን እንድንመረቅበት፣ ሠርተን እንድንከብርበት፣ ዘርተን እንድንቅምበት፣ ወግ ማዕረግ እንድናይበት ሰላም ሊሆን ይገባል። ሰላም የሚሆነው ደግሞ በጋራ ሀሳብ የጋራ አገር ስንፈጥር ነው።
ዓለም ላይ በጥላቻ ሰላም ያመጣ አገር የለም። ጥላቻ ወደ ጦርነት የሚወስድ፣ ወደ አለመጋባባት የሚያደርስ የመለያየት መንገድ ነው። ሰላም ወደ’ሚገኝበት የአብሮነት ስፍራ መማተር አዲሲቷን ኢትዮጵያ ለመፍጠር የመጨረሻ ምርጫችን ነው። አቅጣጫችንን መቀየር አለብን።
ፖለቲካ ልዩነት ይኖረዋል፣ ሁሉም ነገር በአንድ ሀሳብ፣ በአንድ መንገድ ላይሄድ ይችላል። ግን ደግሞ ልዩነት በተፈጠረ ቁጥር ወደ ጦርነትና ወደ መለያየት መሄድ ሳይሆን ያልሞከርነውን የውይይትና የእርቀ ሰላም አማራጮችንም ማየት ይበጃል። ይህ ዓይነቱ አዲስ እሳቤ ነው በልዩነት ውስጥ ተግባቦትን፣ በብዙሀነት ውስጥ አንድነትን የሚሰጠን። ይህ መንግሥት ሊለምደው የሚገባ፣ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ሊቀበሉት የሚገባ ለአዲሱ ትውልድ ልናወርሰው የሚገባ ጦርነት አልባ የሰላም ውርስ ነው።
ጦርነት ሁሌም አንድ ዓይነት ነው። በሀሳብ ልዩነት ይጀመርና ብዙዎችን ለሞትና ለአካል ጉዳት ይዳርጋል። ገዳይና ሟች እስኪበቃቸው እየገደሉ የሚሞቱበት ነው። መጨረሻው ግን በእርቅ ይቋጫል። የዚህ ጽሑፍ ዋና አላማ ገዳይና ሟች ሳይኖር፣ ችግርና ጉስቁልና ሳይደርሱብን ወደ ጦርነት የሚወሰዱንን የመለያየት መንገዶች እንዝጋ ነው።
የዚህ ጽሑፍ ፍሬ ነገር ሳንገድልና ሳንሞት፣ ታሪክ ይቅር የማይለውን ጠባሳ ሳንጽፍ፣ ከብዙ እልቂት ዋጋ መክፈል በኋላ ሳንጨባበጥ ልዩነታችንን አጥበን ወደ ሰላም እንምጣ ነው። በውይይትና በምክክር በጋራ ሀሳብ የጋራ ቤት እንሥራ ነው። ሰላም መልኳ ቀይ ዳማ ነው። በእሷ ውስጥ ሁሉ ስቆ ይኖራል። ሳቃችንን የሚያደበዝዝብን መልከ ውይቡ ጦርነት ነው።
ባለፉት አራት አመታትም ይሁን ከዚያ በፊት የነበሩ ጦርነቶችና የእርስ በርስ ግጭቶች በሰላማዊ መንገድ ተቋጭተው ቢሆኑ ኖሮ ዛሬ ላይ እንደ አገር በምን ደረጃ ላይ እንደምንገኝ አስባችሁታል? ጦርነት ዛሬን ብቻ ሳይሆን ነገንም ነው የሚቀማን። ጦርነት ቅስም ይሰብራል። ቅስም ብቻ አይደለም የሚመጣውን ሃምሳና መቶ አመት ጨምሮ ዋጋ የሚያስከፍል ነው።
ስንዋጋና ስንሞት ዛሬ ላይ ብቻ አይደለም ከዛሬ ለራቀ ነገ ዋጋ እየከፈልን ነው። የሚያምርብን መጨባበጥ ነው። መጨባበጥ ስላችሁ ከጦርነት በኋላ ያለውን መጨባበጥ ሳይሆን ከጦርነት በፊት ልዩነትን አጥቦ በፍቅር የምንጨባበጠውን መጨባበጥ ማለቴ ነው።
እንደ አገር ከሰላም ውጪ ምንም አማራጭ የሌለን ሕዝቦች ነን። ጦርነትን ከማንም በላይ ሞክረነዋል። ትርፍ ግን አላመጣልንም። የአሁኗ ኢትዮጵያ ብቻ አይደለችም የትናንቷን ጨምሮ ወደፊት የምትፈጠረው ኢትዮጵያም ጦርነት የሚያስፈልጋት አይደለችም። ድህነት የቀደዳቸው፣ ማጣት የገበጣቸው ብዙ ቀዳዳዎች አሉብን። እነሱን መድፈን እንጂ በሆነ ባልሆነ ጦር መማዘዝ አሁን ላለንበት አገራዊ ሁኔታ የሚመች አይደለም።
በሰላም ሀሳብ ወደ ፊት መሄድ ብቻ ነው የሚያዋጣን። ችግሮቻችን፣ ድህነቶቻችን፣ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ነውሮቻችን በሰላማዊ መንገድ ካልሆነ በሌላ በምንም እንዳይፈቱ ሆነው የተተበተቡ ናቸው። ረጋ ካልን፣ ዝግ ካልን የምንፈታቸው ብዙ ቋጠሮዎች አሉ። በሰላም የማይፈታ ቋጠሮ የለም። ጥላቻ ቋጠሮ ያጠብቃል እንጂ ቋጠሮ አያላላም።
የአገር ክብርና ሉአላዊነት ያለው በሰላም ድምጽ ውስጥ ነው። ድምጻችን ሰላምና ስለሰላም ከሆነ ብቻ ነው የምንፈልጋቸው የክብርና የሉአላዊነት፤ የመታፈር መንፈሶች የሚላበሱልን። ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ላይ ክብርና ልዕልና ከስም ባለፈ ምንም ናቸው። የአገር ክብር በሰላም በኩል እንደሚጸና መረዳቱ አፍራሽ ከሆነ አካሄድ የሚመልሰን የተጠና እርምጃ ነው።
ዛሬ ላይ የምንገዳደልባቸው ችግሮቻችም በትናንት ፖለቲካ፣ በትናንት እኔነት የተቋጠሩ ናቸው። ቋጠሮዎቻችን እንዲላሉ የሰላም አማራጮችን መመልከት አለብን። ጦርነት ምን ያክል አስከፊ እንደሆነ ያለፉ ታሪኮቻችን ምስክሮቻችን ናቸው። እነሱን እማኝ አድርገን ወደ ሰላም እንጂ ወደ ነውጥ መመለስ አይኖርብንም። በጋራ ሀሳብ የሰላም አገር መገንባት ቀጣዩ የቤት ሥራችን ነው።
በወረደው የእርቀ ሰላም ጥላ ስር ብዙ የኢትዮጵያ ህልሞች አሉ። የኢትዮጵያ ህልሞች የእኔና የእናንተ ህልሞች ናቸው። የእኔና የእናንተ ህልሞች ደግሞ የትውልዱ ህልሞች ናቸው። አገር የምትፈጠረው በዚህ እውነት ውስጥ ነው። ህልሞቻችን ሰላም ሲለብሱ የኔ አገር ትፈጠራለች። ያኔ ሁሉም ነገር መስተካከል ይጀምራል። ህልሞቻችን ነፍስ የሚዘሩት ደግሞ ኢትዮጵያ ሰላም ስትሆን ነው።
ከፊታችን የኢትዮጵያን ከፍታ የሚያረጋግጡ ብዙ የሰላም አዋጆች እየተሰሙ ነው። ከዚህ ውስጥ አንዱ ስለሰላም የምናወራበት፣ ስለአንድነት የምንመካከርበት አገራዊ ምክክር ነው። እንዳየነው፣ እንደሰማነው፣ እንደደረሰብን፣ እንደተጎዳነው ጥቂት ሰላም ሳይሆን ብዙ ሰላም ነው የሚያስፈልገን። ብዙ ሰላም እንዲመጣልን ደግሞ ሁላችንም የበኩላችንን መወጣት ይጠበቅብናል።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ግንቦት 4/2015