በአገሪቱ ያልተረጋጋ የገበያ ሥርዓት መስተዋል ከጀመረ ውሎ አድሯል። ለዚህ ችግር ዋንኛው ምክንያት ደግሞ በአቋራጭ የማትረፍ፣ ያለቅጥ የማግበስበስ ፍላጎት አንዱ ነው። ይህ ቅጥ ያጣ እራስ ወዳድነት በአገሪቱ ምጣኔ ሀብቱ ላይም ከፍተኛ ጫና እየፈጠረ ይገኛል።
በአብዛኛው በደላሎች እየተዘወረ ያለው የአገሪቱ የገበያ ሥርዓት ከሁሉም በላይ ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኘውን የኅብረተሰብ ክፍል ኑሮ በከፍተኛ ደረጃ እየተፈታተነው ይገኛል። አሁን ላይ በጠንካራ የሕግ ሥርዓት የሚመራ የገበያ ሥርዓት መገንባት ካልተቻለ ሁኔታው አገራዊ የስጋት ምንጭ እንደሚሆን ይታመናል።
ከችግር ፈጣሪዎች ልብ መደንደን የተነሳም በየወቅቱ መንግሥት ገበያውን ለማረጋጋት የሚያደርጋቸው ጥረቶች ብዙም ውጤታማ መሆን አልቻሉም። ጥረቶቹ ትርጉም አልባ እንዲሆኑ ነግቶ በመሸ ቁጥር አያሌ ሴራዎችና አሻጥሮች ተፈልፍለው ያድራሉ። አሁን አሁን ችግሩ ዝቅተኛ የኅብረተሰብ ክፍል ብቻ ሳይሆን መካከለኛ ገቢ ያለውን ክፉኛ እየተፈታተነ ይገኛል።
በአዲስ አበባ ያለውን ተጨባጭ እውነታ አንስተን ብንነጋገር እንኳን፤ በመዲናዋ ተስፋ ሰጪ ታላላቅ ፕሮጀክቶች እየተገነቡ ቢሆኑም፤ የነዋሪውን የዕለት ተዕለት ሕይወት የሚፈታተኑ ችግሮች በስፋት ይስተዋላሉ።
በከተማዋ የነዋሪዎቹን ተስፋ የሚያጨልሙ በደላሎች ጣልቃ ገብነት የሚፈጠሩ ችግሮች ብዙ ናቸው። አሁን አሁን ደላላ ሳይገባበት የሚደረግ ግብይት አለ ብሎ አፍ ሞልቶ ለመናገር የሚከብድ ነው። ከዕለት ተዕለት የምግብ አቅርቦት ጀምሮ፤ የቤት ኪራይ እና ሽያጭ፤ የመሬት እና ተሽከርካሪዎች ንግድ በደላሎች ተይዟል። የዚህ ሁሉ ድምር ውጤት የአገር ምጣኔ ሀብት ላይ ከፍተኛ ጫና ይዞ መጥቷል።
መረጃዎች እንደሚያመለክቱት የዋጋ ግሽበቱ 37 በመቶ እንዲደርስ ምክንያት ከላይ ያነሳናቸው በርካታ ውጥንቅጦች ተጨምረውበት ነው። ዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪና የገበያ ጫና፣ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ቀውሶች ሲታከሉበት ደግሞ ነገሩን ከድጡ ወደማጡ እንዲሆን አድርጎታል።
ሕገ-ወጥ የደላሎች ሰንሰለት
የፖሊሲ፣ የሕግና ሥርዓት ክፍተት ከሚፈጥረው የዋጋ ንረት፣ የኮቪድ ወረርሽኝና ጦርነት ይዘውት ከሚመጡት ጫና በላይ ሕገወጥ ደላሎች በአገሪቱ ምጣኔ ሀብት፤ በዜጎች የዕለት ተዕለት ኑሮ እንዲሁም በጥቅል የገበያ ሥርዓቱ ላይ እየፈጠረ ያለው ጫና እጅግ ከፍተኛ ነው።
ለዚህ ማሳያ የሚሆነው ደግሞ በአንድ ሌሊት ተቆልሎ የሚያድረውን የቤት፣ የመኪና፣ የኮንስትራክሽን፣ የዶላር ምንዛሬ ነው። ነገሩን ከሥሩ እንድንረዳው ያለፈውን ሁለት ዓመት የቤትና የተሽከርካሪ ሽያጭ እንመልከት።
ቤትና መኪና- የገበያው እብደት ማሳያ
በአገራችን ውስጥ የሕገወጥ ደላሎች እጅ እረጅም ከሆነባቸው ውስጥ የመኪናና የቤት ሽያጭ ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛሉ። ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኘው ነዋሪ ቤትና መኪና የሰማይ ያህል እንዲርቁትና የሀብት መለኪያ መሆናቸውን እንዲቆጠር ያደረጉት እነዚሁ ደላሎች ናቸው። ነግቶ በመሸ ቁጥር እብደት እስኪመስል ድረስ ዋጋቸው በሚሊዮኖች እንዲጨምርና ብር ዋጋውን እንዲያጣ የሚያደርግ ሥርዓት በዚህ ግብይት ውስጥ ይስተዋላል።
ይህ ሥርዓት ለሕገወጦች የተመቸ በመሆኑ ባልተገባ መንገድ ያጋበሱትን ረብጣ ገንዘብ ሳይሰስቱ በማውጣት ይሸምቷቸዋል። የምርት እጥረት ሲከሰት ዋጋውም በፍጥነት ያሻቅባል። ደላሎች በዚህ ውስጥ የአንበሳውን ድርሻ ይጫወታሉ። እሴቱ ከሚገባው በላይ የሚተመንለት ዋጋ ሌላው ተወዳዳሪ ተገፍቶ እንዲወጣ ሃቀኛ የግብይት ሥርዓት እንዳይኖር ያደርጋል። ዛሬ በኢትዮጵያ የመኪናና የቤት ሽያጭ እያየን ያለነው ይህንን ነው። ከውጪ በ7 ሺህ ዶላር ተገዝቶና አነስተኛ ቀረጥ ተቆርጦለት የገባ መኪና ያለምንም አሳማኝ ምክንያት 4 እና 5 ሚሊዮን ብሮች በኢትዮጵያ ገበያ ይቸበቸባል።
የቤትና የመሬት ዋጋም ከዚህ የተለየ አይደለም። ሪል እስቴት አልሚዎች ከመንግሥት በተመጣጣኝ ዋጋ በሊዝ በወሰዱት የተንጣለለ መሬት፣ ከቀረጥ ነፃ ባስገቡት የኮንስትራክሽን መሣሪያ፣ በልዩ ፍቃድ በርካሽ በሚወስዱት ሲሚንቶና የመሳሰሉት እንዲሁም በርካሽ የሰው ኃይል የገነቡትን ሪል ስቴት ያለምንም መሸማቀቅና «ሃይ ባይ» 50 እና 60 ሚሊዮን ብር ይጠራሉ።
በአገሪቱ ኢኮኖሚ ምንጩ ከየት እንደሆነ የማይታወቅ ከፍተኛ ገንዘብ እየተረጨ በመሆኑ፤ የብዙዎች የመግዛት አቅም እየተዳከመ ጥቂቶች የገበያው ተዋንያኝ የሚሆኑበት አገራዊ አውድ እየተፈጠረ ነው። «ነፃ ገበያው» ወደ «ነፃ ሕገወጥነት» ተቀይሮ የትርፍ ህዳጉ ከሚፈጥረው በላይ ጥቂቶች ገበያውን ከሚመሩት ሕገወጥ ደላሎች ጋር እየተቀራመቱት ይገኛሉ። እነዚሁ አካላት በሂደት አገር ሁለንተናዊ በሆነ መልኩ ወደ አለመረጋጋት ሊወስዱ እንደሚችሉ ይታመናል። ከዚህ አንጻር «ነፃ ገበያ» «ነፃ ዝርፊያ» ስላልሆነ መንግሥት ዜጎቹን የመጠበቅና ጤናማ የትርፍና ውድድር ሥርዓት ሊዘረጋ ይገባዋል።
«ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል»
«ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል» የሚባለው ያረጀና ያፈጀ ብሂል ከመዝገቦቻችን ብቻ ሳይሆን ከአእምሯችን ውስጥ መሠረዝ የሚኖርበት ነው። ትናንት እንደነበረው ሁሉ ዛሬም በሥልጣን ቆይታቸው ሕዝብንና አገርን ለማገልገል የተሰጣቸውን ኃላፊነት ለግል ጥቅማቸው የሚያውሉ ስለመኖራቸው የሚካድ አይደለም። ይህንን በማስረጃ ለማሳየት ሁለት የቅርብ ጊዜ አውነታዎችን ለማንሳት እንሞክር።
አንዱ በደህንነት መስሪያ ቤቱ ውስጥ ኃላፊነት የነበራቸውና ይህ መሰል አሻጥር ለማስቀረት ሁነኛ የሥልጣን አቅም የነበራቸው ናቸው። ይሁን እንጂ ሥልጣናቸውን የግል ሀብት ለማጋበስና በሕገወጥ የግብይት ሥርዓቱ ላይ ቤንዚል ለማርከፍከፍ ተጠቅመውበታል። የመንግሥትን ማህተም ተጠቅመው የኮንስትራክሽን ግብአት የሆነው ሲሚንቶ ለመስሪያቤቱ የግንባታ ሥራ የሚፈለግ አስመስለው በአየር ላይ ለመሸጥና 30 ሚሊዮን ብር ትርፍ ለማግኘት ሲሞክሩ በቁጥጥር ስር ውለዋል።
ይህ ሙከራ ቢሳካ በምጣኔ ሀብቱ ላይ ምን ጫና እንደሚያስከትል፤ በሕገወጥ ንግዱ ላይ ምን ያህል ጉዳት እንደሚያደርስ ግልፅ ነበር። እነዚህ ተደረሰባቸውና የፍትህ በትር አረፈባቸው እንጂ በርካታ መሰል አፀያፊ ሌብነት የሚፈፅሙ ባለሥልጣናት ስለመኖራቸው አንድ ተጨባጭ ማሳያ ነው።
ሁለተኛው የቅርብ ጊዜ ማስረጃ ደግሞ ከሳምንታት በፊት የተወካዮች ምክር ቤት እንደራሴዎች ያለመከሰስ መብታቸውን አንስቶ ዘብጥያ ያወረዳቸው ባለሥልጣን ነው። ዝርዝሩ በመገናኛ ብዙኃን የተነሳ በመሆኑ ብዙ ማለት ባያስፈልግም እኝህ አንድ ግለሰብ (ባለሥልጣን) ብቻ የሕዝብ ሀብት የሆነ በርካታ ሚሊዮን ብሮችን ካዝናቸው ውስጥ በማስገባት የግል ፍላጎታቸውን ያለስስት ሲያሟሉ ነበር። ያለምንም ፍራቻ በገበያ ውስጥ እጃቸውን ከትተው ቤትና መኪናዎችን በሚሊዮኖች ሲሸምቱ እንደነበር በማስረጃ መረጋገጡን ፖሊስ አርድቶናል።
መንግሥት በተደጋጋሚ እንደሚነግረን ገበያው እንዳይረጋጋ ምርትን የሚያንሩ፣ የሚደብቁና ዋጋን ያለቅጥ የሚቆልሉ ሕገወጦች እዚህም እዚያም ይታያሉ። በመንግሥት ውስጥ የመሸጉ ወንጀለኞች እንዳሉም በተደጋጋሚ ሹክ ይለናል። ኅብረተሰቡ ተባባሪ እንዲሆን ተደጋጋሚ ጥሪ ያደርጋል ይህ ጥሪ ተገቢ ቢሆንም በእጁ «ሕግም ሆነ በትር» የያዘው መንግሥት ዋንኛውን ሚና መጫወት ይኖርበታል። ከምንም በላይ በውስጡ የመሸጉትን በግ መሳይ ተኩላዎች ማጥራትና መለየት አለበት።
የተዘረፈ ገንዘብ አያሳሳም
ምንጩ ያልታወቀ የተዘረፈ ገንዘብ ሲያወጡት አያሳሳም። ብርን ይዘው ከሚቀመጡ ደግሞ ወደ ንብረት መለወጡ የተሻለ እንደሆነ እነዚህ ሕገ ወጦች ጠንቅቀው ያውቁታል። በገንዘብ አጠባ “Money laundering” ቀዳሚ ተሳታፊዎች ናቸው። ጥቁር ገበያ “black market” ውስጥም እጃቸው አለበት። እነዚህ ሕገ ወጥ እንቅስቃሴዎች ደግሞ ለኑሮ ውድነት ዋንኛውን ድርሻ የሚወስዱ ናቸው። የገበያ ሥርዓቱን ያናጉታል። እንደልብ በሚረጭ ሀብት ዝቅተኛውም ሆነ መካከለኛ ገቢ ላይ የሚገኘው ነዋሪ ምርትን ባለው ሀብት መጠን እንዳያገኝ ያደርጋሉ።
ሕገ-ወጦች ሁሌም ስጋት አለባቸው። ስለዚህ ከዘረፋቸው እኩል የዘረፉትን ሀብት የሚሸሽጉበት መንገድ ይፈልጋሉ። በዚህ ትርምስ ገበያው ውስጥ አመረጋጋት ይፈጥራሉ። ያገኙትን ይገዛሉ። ለሚያወጡት ገንዘብ አይጨነቁም። የሕዝብን ሀብት ያለስስት ይረጫሉ። ይህንን የሚያሳኩ ሕገወጥ ደላሎች ደግሞ ትልቁን ድርሻ ወስደው የትርምሱ አካል ያደርጋሉ። በዚህ ምክንያት መኪና፣ ቤት፣ የኮንስትራክሽን ግብአት፣ ነዳጅ፣ መሠረታዊ ግብአት ወዘተ ዋጋቸው ጣራ ነክቶ የሕዝቡን ጣር ያበዙታል።
መፍትሄ
መንግሥት ሕግ አውጪ፣ ሕግ ተርጓሚና ሕግ አስፈፃሚ ነው። የአንድ አገር ሰላምና ፀጥታ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ሥርዓት ባለው መልኩ የሚሄዱት ሦስቱ አካላት ተመጋግበው ሲሄዱ ነው። በተለምዶ አራተኛ መንግሥት የምንላቸው የመገናኛ ብዙኃን ሚናም በዚህ ውስጥ ጉልህ ነው። በመሆኑም እነዚህ አካላት ሁሉም በተደራጀ ተቋማዊ ሥርዓት አሁን አገሪቱ የገጠማትን የኢኮኖሚ እንቅፋት እንድትሻገርና ሕዝቡ እፎይታን እንዲያገኝ በቁርጠኝነት እንዲሠሩ መንገዱን መጥረግ ይገባል። የፖሊሲና የሕግ ክፍተቶችን ማረም፣ ሕገወጥ ደላሎች የዘረጉትን የተደራጀ ሰንሰለት መበጣጠስ። መረጃውን ለኅብረተሰቡ በፍጥነት በማድረስ የሌቦችና የቀማኞች መሸሸጊያ እንዳይሆን ማንቃት ይገባል።
ነፃ የኢኮኖሚ ሥርዓት የሚባለው ፅንሰ ሃሳብ የዜጎችን ኑሮ ለማቅለል እንጂ ለማክበድ አይደለም ከዚህ አንጻር፤ የተጀመረውን የነፃ ኢኮኖሚ ሥርዓት ግንባታ ውጤታማ እንዲሆን በጠንካራ ፖሊሲ፣ ሕግ፣ መመሪያ ሊያጠናክረው ይገባል።
በጥቁር ገበያ ውስጥ የሚሳተፉ ወንጀለኞች በመዲናዋ በግልፅ ሱቅ ከፍተው እንደሚንቀሳቀሱ ይታወቃል። ይሄ አይደለም ጠንካራ የደህንነት ሰንሰለት ላለው መንግሥት ለተራውም ዜጋ በግልፅ የሚታይ ነው። ስለዚህ ዳተኝነትን አስወግዶ በእነዚህ አካላት ላይ ጠንካራ ሕጋዊው እርምጃ ሊወስድ ይገባል። በተለይ የኑሮ ውድነትን ለመግታት፣ ሌብነትን ለመቆጣጠር የሚያመች የፋይናንስ ደህንነትና ሕግን በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ውስጥ ማስረፅ ለነገ የሚባል አይሆንም። ሰላም!!
ዳግም ከበደ
አዲስ ዘመን ግንቦት 1/2015