የጎዳናውን ዳር ይዘው ወደላይና ወደታች የሚወርደውን መንገደኛ ‹ተመዘን ›እያሉ የሚማፀኑ ህፃናትና ታዳጊዎችን ማየት የተለመደ ነው:: ምንም አይነት መጠለያ በሌለበት ነው ቀኑን ሙሉ አላፊ አግዳሚውን ‹‹ተመዘን›› ሲሉ ይውላሉ:: አንዳንዶቹም የያዙት የክብደት መለኪያ ሚዛን ከእነርሱ አቅም በላይ ነው:: ምግብ ሲበሉም ሆነ ውሃ ሲሰጡ አያጋጥሙም:: ሆቴል ሄደው ይበላሉ ብሎ ለመገመት የገንዘብ አቅም ብቻ ሳይሆን እድሜያቸውም አይፈቅድም::
በአስቸጋሪ ሁኔታ በጎዳና ሥራ ላይ የተሰማሩት ህፃናትና ታዳጊዎች በእድሜ የበሰሉ ሰዎች እንኳን የሚቋቋሙት የሥራ አይነት አይደለም:: እነዚህ ህፃናትና ታዳጊዎች የወላጅ ወይንም የአሳዳጊ እንክብካቤ በሚያስፈልጋቸው፣ በትምህርት ገበታ ላይ በሚገኙበት እድሜያቸው ነው ከአቅማቸው በላይ የሆነ ጫና የተሸከሙት:: በእድሜያቸው የመጫወት እድል እንኳን ተነፍጓቸዋል::
በአይነህሊናዎ በወላጆቻቸው ወይንም ባሳዳጊዎቻቸው እንክብካቤ የሚደረግላቸውንና እነዚህ እጅግ ከአቅማቸው በላይ በሆነ ሥራ ውስጥ የሚገኙትን ልጆች ሲያዩ የእነዚህ ህፃናት እጣ ፈንታ ለምን እንዲህ ሆነ ብለው ማሰብዎ አይቀርም:: በእርግጥ የኑሮ ወይንም የኢኮኖሚ ሁኔታ የፈጠረው ልዩነት እንደሆነ ለሁላችንም ግልጽ ነው:: ግን ደግሞ ወላጅ ወይንም አሳዳጊ ልጆቹን ለከፋ ነገር አጋልጦ ይሰጣል ወይ? የሚለው ነው በትልቁ መሠመር ያለበት:: በአነስተኛ የሥራ መስክ ላይ ተሰማርተው ልጆቻቸውን በአቅማቸው የሚንከባከቡ ብዙ ወላጆችን በየአካባቢያችን እናስተውላለን::
እነዚህ የክብደት መለኪያ ሚዛን ይዘው በጎዳና ላይ ‹‹ተመዘን›› እያሉ የሚውሉ ህፃናት ጉዳይ ግን ይለያል:: ቋንቋቸው ተመሳሳይ ነው:: ይህ ደግሞ ከአንድ አካባቢ የመጡ ለመሆናቸው አንዱ መለያ ወይም ማሳያ ነው:: አብዛኞቹም በተመሳሳይ እድሜ ላይ የሚገኙም ናቸው:: ይሄ ሁኔታና የህፃናቱም አኗኗር ለምን? የሚል ጥያቄ ይፈጥራል:: በአንድ ወቅት በአዲስ አበባ ከተማ በተለምዶ ሽሮሜዳ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በስፋት የባህላዊ ሽመና ሥራ የሚሰሩ ግለሰቦች ከደቡብ የኢትዮጵያ ክፍል ህፃናትን በስርቆትና ወላጆቻቸውን በገንዘብ በማማለል ከጉያቸው እንዲወጡ በማድረግ ከእድሜያቸው በላይ በሆነው የሽመና ሥራ ላይ በማሰማራት ያደርሱ የነበረው የጉልበት ብዝበዛ በስፋት ይነሳ እንደበር ይታወሳል:: እነዚህ ልጆች ማምለጥ የሚችሉበት እድል እንኳን እንዳይኖር ከቤት አያስወጧቸውም:: ትምህርትቤትም መሄድ አይችሉም:: ቀኑን ሙሉ በጉድጓድ ውስጥ የሽመና ሥራ ሲሰሩ እንደሚውሉና የመኝታ ሰዓት እንደሚገላግላቸው ነበር ሲነገር የነበረው::
ህፃናቱ በአካልም በአእምሮም ነበር የሚጎዱት:: በአንድ ወቅት መገናኛ ብዙሃንን ጨምሮ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች አጀንዳ ሆኖ ጉዳዩ በስፋት ሲነሳ ነበር:: የነበረው ርብርብ ችግሩን ሙሉ ለሙሉ ባይቀርፈውም በህብረተሰቡ ዘንድ ግንዛቤ መፍጠሩ አይዘነጋም:: አሁን ደግሞ በህፃናት ላይ የሚደረገው የጉልበት ብዝበዛ መልኩን ቀይሮ መጥቷል:: በምንዘዋወርበት ጎዳና ልብሳችንን እየጎተቱና ከፊታችን እየቀደሙ እጃቸውን ለምጽዋት የሚዘረጉ የህፃናት ጉዳይም አንዱ ነው::
በተለይ ‹‹ተመዘን›› እያሉ በጎዳና ላይ ስለሚሰሩ ህፃናት ጉዳይ አንድ ወዳጄ እንዳጫወተኝ በአሰሪዎቻቸው ከፍተኛ የማስፈራራት ጫና ስለሚደረግባቸው አብዛኞቹ ስለሚደርስባቸው ችግር፣ የሥራ ጫና እና ስለቤተሰባቸው ሁኔታ ለመናገር አይደፍሩም:: የቀጣይ ኑሮአቸው ስለሚያሳስባቸው ዝምታን ይመርጣሉ:: ይህ ወዳጄ ባደረገው ከፍተኛ የማባበል ሙከራ የተወሰኑ ህፃናትን አነጋግሮ ወላጆቻቸው በማያውቁበት ሁኔታ ወደ አዲስ አበባ ከተማ እንዳመጧቸውና ያመጧቸውን እንደማያውቋቸው ነበር የነገሩት::
ህፃናቱ የቀን ገቢ ማስገባት ዋና ተግባራቸው ነው:: አሰሪያቸው በህብረት እንዲኖሩ ላመቻችላቸው የኪራይ ቤት ደግሞ በጋራ በማዋጣት መክፈል ይጠበቅባቸዋል:: ምግባቸውንም የሚችሉት እራሳቸው ናቸው:: ይሄን ሁሉ ኃላፊነት ለመወጣት በየቀኑ መሥራት ይኖርባቸዋል:: የሥራ ስምሪታቸውም ከጠዋት 12 ሰአት እስከ ማታ 12 ሰአት ነው:: በዓለም አቀፍ ህግ አንድ ሰው በህግ አግባብ ለስራ እድሜው ከደረሰ በኋላ እንኳን በቀን ስምንት ሰዓት ብቻ እንዲሰራ ተቀምጧል:: በዚህ ላይም የዓመት ፈቃድ አለው:: ህጻናቱ ግን ባልመረጡት የእለት ኑሮቸው በዚህ ሁኔታ እንዲያልፍ ተገደዋል:: እነዚህ ህፃናት ላይ እንዲህ የፈረደው ሰው ግን በእነርሱ ጫንቃ ይኖራል::
ወዳጄ ያገኛቸው ህፃናት ወላጆቻቸው ናፍቀዋቸው እንደነበር ነው የነገሩት:: መረጃውን ስለሰጡት የሚደርስባቸውን ጫናም በመገንዘቡ ልጆቹን ከወላጆቻቸው ጋር ለማገናኘት መስዋእትነት ከፍሏል:: በወቅቱ የአንደኛው ህፃን እናት ልጃቸው ሞቷል ብለው ተስፋ ቆርጠው እንደነበርም ነው ልጃቸውን ይዞላቸው በሄደ ጊዜ ያጫወቱት::
ልጆቹን ወደወላጆቻቸው ለመቀላቀል ለወዳጄ ቀላል አልነበረም:: ለጊዜው ማቆያና ምግብ ከመቻል ጀምሮ ወላጆቻቸው ያሉበት ድረስ ለማድረስ ወጪና ጊዜን ይጠይቅ ነበር:: እንዲህ ባለው ሁኔታ አንድ ሰው የሚያደርገው ጥረት ልጆቹን ካሉበት ችግር ለመታደግ እጅግ ከባድ ሆኖ ነው ያገኘው:: እንደርሱ መስዋእትነት ለመክፈል ባልችልም ለግንዛቤ ብዬ አንዳንዶችን ለማነጋገር ሞክሬ ነበር:: ወዳጄ እንዳለው ልጆቹ ፍርሀት አለባቸው:: በቋንቋም ልንግባባ አልቻልንም::
‹‹ጋን በጠጠር ይደገፋል›› እንዲሉ ለእነዚህ ህፃናት ለመድረስ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችንም የጋራ ትብብር ይጠይቃል:: በዚህ ወቅት በኢትዮጵያ ህፃናት ላይ በተለያየ መንገድ እየተፈፀመባቸው ያለው የጉልበት ብዝበዛ ትልቅ አጀንዳ መሆን እንዳለበት ከዚሁ ጉዳይ ጋር በተያያዘ በተካፈልኩበት ሥልጠና ላይ በነበሩ ተሳታፊዎች ተነስቶ የነበረው የተለያየ ተሞከሮ የጉዳዩን አሳሳቢነት ነበር የተገነዘብኩት::
በወቅቱ ስልጠናውን የሰጡን በኬር ኢትዮጵያ የፕሮጀክት ዳይሬክተር ወይዘሮ ፀደይ አማረ እንደነገሩን በህፃናት ላይ የሚፈፀም የጉልበት ብዝበዛን በተመለከተ የተደረጉ ጥናቶች የቆዩ ናቸው:: በተለይ በአገር አቀፍ ደረጃ የተደረገ ጥናት እኤአ በ2015 አካባቢ እንደሆነ ነው መረጃዎች የሚያሳዩት:: አሁን አገሪቱ በውስጥ በገጠማት የተለያየ ችግር ህፃናት ለጉልበት ብዝበዛ የበለጠ ተጋላጭ የሚሆኑበት እድል ስለሚሰፋ ቁጥሩን በትክክል ማስቀመጥ ይከብዳል ነው ያሉት እንደሚከብድም ተናግረዋል::
ኢትዮጵያ የህፃናት ጥበቃ (ቻይልድ ፕሮቴክሽን) ፖሊሲ ውስጥ የተካተተ ካልሆነ በስተቀር እራሱን የቻለ የህፃናት ጉልበት ብዝበዛ (ቻይልድ ሌበር) ፖሊሲ እንደሌላትም ገልጸዋል:: ይህም ህፃናት ላይ ከሚደርሰው የጉልበት ብዛበዛ አንፃር የተሰጠው ትኩረት አናሳ መሆኑን ያሳያል ነው ያሉት:: በአሁኑ ጊዜ የፖሊሲ ማሻሻያ እንዲደረግ ባለድርሻ አካላትን በስልጠና ግንዛቤ በማስጨበጥ እንዲሁም ህፃናት ላይ የሚደርሰውን ጉልበት ብዝበዛ አገራዊ ገጽታ የሚያሳይ የጥናት ሥራም ለመሥራት ኬር ኢትዮጵያ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል ብለዋል::
ኬር ኢትዮጵያ ከህፃናት ጉልበት ብዝበዛ ጋር በተያያዘ ከሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር ሥራዎችን እየሰራ ይገኛል:: በተጨማሪ ለተለያዩ ባለድርሻ አካላት የግንዛቤና ስልጠናዎችን በመሥጠት ንቅናቄ እንዲፈጠርም እንዲሁ እየሰራ ነው:: ባጠቃላይም በህፃናት ላይ የሚደርሰውን ጉልበት ብዝበዛ ለመከላከል ትምህርት ሚኒስቴር፣ ማዕድን ሚኒስቴርና ሌሎችም አስፈጻሚ አካላት ኃላፊነት እንዳለባቸውና እነዚህን ባለድርሻ አካላት ያካተተ ሥራም እንደሚያስፈልግ በመርሃግብሩ ተብራርቷል:: እኔም ይህንን የህጻናትን ህይወት የሚያጨልም የአገር ገጽታን የሚያበላሽ ተግባር እንዲገታ የሚመለከታቸው አካላት ትኩረት እንዲሰጡ ስል መልእክቴን አስተላልፋለሁ።
ለምለም መንግሥቱ
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 10/2015