«አስተማማኝ ሰላም ለዘላቂ እድገትና ብልጽግና ነው» የምትለው ይቺ አባባል በተለያዩ ግዜያት በበርካታ ምሑራንና ፖለቲከኞች ስትነገር እንሰማለን። ምን አልባትም አብዛኛው ልሂቅ ከሚያስማሙ መሠረታዊ ሀሳቦች መካከል ቀዳሚዋም ትመስለኛለች። ለዚህ ማሳያችን ዛሬ አደጉ የምንላቸው ሀገራት በተለይም ባለፉት ስልሳና ሰባ ዓመታት ፈጣን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ እድገት ያመጡት በቅድሚያ የተረጋገጠ ሰላም በሀገራቸው ማስፈን በመቻላቸው ነው።
እነዚህ ሀገራት ቀደም ባለው ጊዜ ውጪውም ሆነ ውስጣዊ ችግሮች ነበሯቸው። ለሰላማቸው ቅድሚያ ሰጥተው በመሥራታቸውና የውስጥ ሰላማቸውን በማረጋገጣቸው ዛሬ ሕዝባቸውን ከዳር እስከ ዳር ተጠቃሚ የሚያደርግ እድገትና ብልጽግናን ማስመዝገብ ችለዋል። እንደ ጎረቤታችን ሶማልያ ደግሞ እርስ በእርስ ባለመስማማት ሕዝባቸውን ዛሬም ድረስ ለስቃይና ለስደት ብሎም ለእልቂት እየዳረጉ አሉ ።
በተለይም ይህ እውነታ በአፍሪካ ሀገራት በስፋት የሚስተዋል ነው። አፍሪካውያን ሀገራት ሰላማቸውን አስከብረው በልማት አሁን ካሉበት ኋላ ቀርነት ለመውጣት ብዙ መሻት ቢኖራቸውም በተለያዩ ምክንያቶች መሻታቸውን መኖር አልታደሉም። ዛሬም በእርስ በርስ ግጭቶች እየታመሱ ፤ ሕዝባቸውን ለረሀብና ለችጋር እንደተጋለጡ ነው ።
እነዚህ ሀገራት «ቅድሚያ ለሰላም» በመስጠት የውስጥ ችግሮቻቸውን በራሳቸው አቅም በውይይት ለመፍታት በቂ ዝግጁነት ባለመፍጠራቸው፤ ሕዝባቸው ተፈጥሮ ያደለውን በረከት ተጠቅሞ በራሱ ካለበት ጉስቁልና እርዳታ ጠባቂነት ሊወጣ አልቻለም ።
ሀገራችን ኢትዮጵያም ያለፉትን ሀምሳ ዓመታት በተለያዩ ጊዜያት ብልጭ ድርግም በሚሉ የውስጥ ችግሮች በብርቱ ተፈትናለች ፤አሁንም እየተፈተነች ነው። የሩቁን ታሪክና ተረት ወደ ጎን ትተን ባለፉት ሦስት አራት ዓመታት ብቻ በሀገራችን የተከሰተውን ብንመለከት በአንዳንድ ሁኔታዎች ኢትዮጵያ አበቃላት እስከማለት የተደረሰባቸው ተደጋጋሚ ግዜያቶች ነበሩ።
ነገር ግን ውድቀታችንን የሚመኙ እንዳሰቡት ሳይሆን ቀርቶ ነገሮች ተዓምር ሊባል በሚል ደረጃና ፍጥነት ተለውጠዋል ። የዚህ ጅማሮ መነሻው ደግሞ በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ የተደረገው የሁለትዮሽ ስምምነት ነበር። በእርግጥ የነበረውን ሁኔታ በቅርበት ሲከታተል ለነበረ ኢትዮጵያዊ ይቅርና የምሥራቅ አፍሪካን ፖለቲካ ለሚከታተል ማንኛውም ሰው እውነታ አንዳች ስሜት የሚያጭር ነበር። በወቅቱም በርካቶች በነቀፋም… በድገፋም.. በትችትም.. በመገረምም የሰጧቸው አስተያየቶች ለዚህ ማሳያዎች ይመስሉኛል።
በእውነትም አብዛኞቻችን ዘንድ እውን ስምምነቱን ተከትሎ የሰላም አየር ይሰፍን ይሆን የሚል ጥያቄ አስተናግደን እንደነበር እገምታለሁ። ምክንያቱም ነገሩ ሕልም እንጂ እውነት ስለማይመስል ነው። እያደር ግን ነገሮች ወደተቀመጠላቸው መስመር መግባት መጀመራቸውን ለመመልከት በቃን።
የሰላም ፍሬ ለሰው ልጅ እንደ ጥሩ ገበሬ ያለመታከት በሚደረግ ልፋት እንጂ እንደ እንስሳት ወፍ ዘራሽ ሆኖ ሊገኝ እንደማይችል የሚዘነጋ አይኖርም። ያለ መታከት ለሰላም መሥራትና መዘመር ያለበት ደግሞ በመንግሥት፤ በሀይማኖት አባቶችና በፖለቲከኞች ብቻ ሳይሆን እንደ ዜጋም በእያንዳንዱ ተግባርና አንደበት ሊሆን ይገባል።
ይህ መደረግ ያለበት ዋነኛው ምክንያት በመጀመሪያ ደረጃ መንግሥት ምንም ያህል ጠንካራ ቢሆን ያለ ሕዝብ ተሳትፎ የሚሠራቸው ሥራዎች ውጤታማ ሊሆኑ ስለማይችሉ ነው ። ሁለተኛው ደግሞ በሰላም መደፍረስ ቀዳሚ የገፈቱ ቀማሽ የሚሆነው የመንግሥት አመራር አልያም ፖለቲከኛው ሳይሆን ሰፊው ሕዝብ መሆኑ ነው።
ሕዝብ እንደ ሕዝብ በሁለንተናዊ መልኩ ለሰላሙ መቆም አለበት። በአሁኑ ወቅት በሀገራችን በተለያዩ ቦታዎች እየተፈጠሩ ያሉ የሰላም እጦቶች በባእድ ወራርያን ሳይሆን እርስ በእርሳችን ነው። እዚህ ላይ የችግሩ መነሻ ምንም ይሁን ምን የባዕዳን እጅ ይኑርበት አይኑርበት በመድረኩ ላይ ተዋናዮቹ እኛው ኢትዮጵያውያን እራሳችን ነን ።
የተለያዩ የጥፋት ትርክቶችን ፈብርከው በችግሮቻችን ላይ ቤንዚን ለሚያርከፈክፉ የግጭት ጠማቂዎች ፤ የማኅበራዊ ሚድያ ጀብደኞች ጆሮአችንን ከመስጠት ጀምሮ በትርክቶቻቸው ተታልለን በሰላማችን ላይ የመጀመሪያው ሰልፈኞች እየሆንን ያለነው እኛው ነን። ለዚህ ደግሞ የእለት ተእለት እንቅስቃሴያችንን ቆም ብሎ ማየት በቂ ነው ።
በውስጣችን ፈቅደን የተዘራብንን የጥላቻና የሁከት ዘር ተሸክመን ቀጣይ የጉዞ መስመራችን ምን ሊሆን እንደሚችል ነጋሪ የሚጠይቅ አይደለም። እንደ ግለሰብ ጥላቻንና ጸብ ተዘርቶብን ፍቅርን ለማጨድ የምንችልበት ፍጥረታዊ አካሄድ/አቅም የለንም።
መንግሥትም ውጪያዊውን ሁከትና ብጥብጥ ካለበት የሀገርና የሕዝብ ሰላም የማስከበር ሕገመንግሥታዊ ኃላፊነት አንጻር የሚቻለውን አማራጭ ይጠቀም ይሆናል እንጂ በኛ ውስጥ ፈቅደንና ወደን ያዘራነውን ክፉ ዘር ፍሬ እንዳያፈራ የማድረግ የተሟላ አቅም የለውም ።
የሀገር ሰላምን በማስፈን እና ጠብቆ በማስቀጠል ሂደት ውስጥ ዋንኛው ተዋናይ ሕዝብ ነው፤በራሱ የሰላም ሐዋርያ በመሆንና ለሰላም ዘብ በመቆም፤ይህ ደግሞ ሰላምን የሚገዳደሩ ሁኔታዎችን/ አቅሞችን በሙሉ ካለመቀበል ጀምሮ አምሮ እስከመታገል በሚደርስ ቁርጠኝነት ሊገለጥ ይገባል ።
ዛሬም በሀገራችን በብርቱ ምላሽ የሚሹ በርካታ ፖለቲካዊ፤ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጥያቄዎች ቢኖሩም እነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ ሊያገኙ የሚችሉት ሁሉም ዜጋ ለሰላም ቅድመ፣ ሲሰጥና ስለሰላም በኃላፊነት መንፈስ ሲንቀሳቀስ ብቻ ነው ።እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ ሰላምን መረበሽም ዘላቂ መፍትሔ ሊሆነን አይችልም።
የየትኛውም አካል/የትኛውም ጥያቄ ዘላቂ መፍትሔ ይዞ እንዲመጣ የሕዝብን ሰላም በማይነሳ ፤ አብሮነትን በማያላላ ሕግ በማይጥስ መንገድ ሊሆን ይገባል። እያንዳንዱ ዜጋ እንደ ግለሰብም ሆነ ማኅበረሰብ ፤ አልያም እንደ ልሒቅ በራሱም ሆነ በሕዝብ ስም ጥያቄ ሲያነሳ ስለ ጥያቄው አቀራረብ ደግሞ ደጋግሞ ሊያስብ ይገባል።
ከዚሁ ጋር በተያያዘ የሚስተዋሉ ሁለት መሠረታዊ ችግሮች አሉ፤ አንደኛው በብዙዎቻችን ጥያቄ ውስጥ የፍላጎት መደራረብ መኖሩና ሁላችንም በጠየቅነው ልክ መንግሥት ምላሽ ሊሰጠን ይገባል የሚል ነው። ወቅታዊ ሁኔታን ፤ሀገራዊ ተጨባጭ እውነታን እያወቁ አላዋቂ ሆኖ በመገኘት ፤ጉዳዮችን የፖለቲካ ቁማር ካርድ አድርጎ መጠቀምን የሚመለከት ነው ።
ሁለተኛው ደግሞ የትኛውንም ጥያቄ ለመመለስ ጊዜ የሚፈልግ ትዕግስት የሚጠይቅ መሆኑን ካለመረዳት ሳይሆን ከችግሮች የፖለቲካ ትርፍ ከመፈለግ የሚመነጭ ነው። እነዚህ ችግሮች በአግባቡ በመረዳት ሕዝባችን ጥያቄዎቹን በሰላማዊ መንገድ ማቅረብን መልሱንም በትዕግስት መጠበቅ ይኖርበታል ፤በተለይም አሁን ካለንበት አስቸጋሪ ሀገራዊ እውነታዎች አንጻር ሁሉም ለሀገራዊ ሰላም ዘብ ሊቆምና ቅድሚያም ሊሰጥ ይገባል እላለሁ።
በጋዜጣው ሪፖርተር
አዲስ ዘመን ሰኞ ሚያዝያ 9 ቀን 2015 ዓ.ም