“የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና መቀላጠፍ” በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ የተካሄደው የዘንድሮው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባዔ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2019 ወደ ሥራ የገባውንና 1 ነጥብ 4 ቢሊየን ያህሉን የአሕጉሪቱን ሕዝብ በንግድ ለማስተሳሰር የታለመውን የንግድ ቀጣና ይበልጥ ተግባራዊ ማድረግ በሚቻልበት ጉዳይ ላይ መክሯል።
በተለይም የጋራ የጉምሩክ ሥርዓትና ወጥ የታሪፍ አስተዳደር በአሕጉሪቷ ለመተግበር ትኩረት እንዲደረግበት፣ የእርስ በርስ የንግድ ግንኙነትን የሚያቀጭጩ አሰራሮች መሻሻል እንደሚገባቸውና የተሳለጠ የንግድ ሥርዓት ለመፍጠር ሀገራት ትኩረት እንዲሰጡ መክሯል፤ በአፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ የተከሰቱ የድርቅና ረሃብ ጉዳቶችን እንዲሁም በዩክሬንና በሩስያ ጦርነት ምክንያት አደጋ ላይ የወደቀውን የአሕጉሪቱን የምግብ ዋስትና ችግር በተመለከተ ምክክር አድርጓል።
የአፍሪካ የ2063 አጀንዳ አፈጻጸም፣ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በአፍሪካ ሰላምና ደኅንነት ለማረጋገጥ እንዲሁም የተሻለች አፍሪካን ለመገንባት የተቀመጠውን የረዥም ጊዜ ዕቅድ አፈጻጸም ላይም የኮሚሽኑን ሥራዎች ሪፖርት ተመልክቷል።
በጉባኤው እነማን ተገኙ?
በመረጃዎች እንደሚያመለክተው በጉባኤው፤ የ35 የሀገራት መሪዎች (ፕሬዝደንቶች እና አራት ጠቅላይ ሚኒስትሮች)፣ 11 የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች፣ 13 ቀዳማዊ እመቤቶችና 10 የዓለም አቀፍ ድርጅት ኃላፊዎች ታድመዋል።
በጥቅሉ 852 ጋዜጠኞች (332ቱ የሀገር ውስጥ እንዲሁም 70ዎቹ ተቀማጭነታችውን ኢትዮጵያ ያደረጉ የውጭ ሀገራት መገናኛ ብዙኃን የዜና ወኪሎች) 450ዎቹ ደግሞ ከተለያዩ ሀገራት የመጡ የውጭ ሀገራት መገናኛ ብዙኃን ጊዜያዊ የዜና ወኪሎች ጉባኤውን ለመዘገብ በኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን ፈቃድ አግኝተው ጉባኤውን ዘግበዋል።
በጉባኤው መሪዎች ምን አሉ?
የሲኔጋል ፕሬዚዳንት ማኪ ሳል/የቀድሞው አፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር/
ባለፈው ጉባኤ አፍሪካ የቡድን 20 አባል ሀገራት ሙሉ አባል ለመሆን ጥያቄ እንደታቀረብ በተሰጠው አቅጣጫ መሰረት ያቀረበችው ጥያቄ በጥሩ ሂደት ላይ መሆኑን ገልጸዋል።
አህጉሪቷ በሽብርተኝነት፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የእርስ በእርስ ግጭትና ሌሎችም የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ችግሮች እየተፈተነች ነው ፤ በመሆኑም በምጣኔ ሀብት የበለጸገች፣ ሰላም የሰፈነባትና የምንመኛትን ጠንካራ አፍሪካን ዕውን ለማድረግ ከዓለም መንግስታትና በአሕጉሪቱ ያለውን የእርስ በርስ ትብብር ማጠናከር ይገባል ብለዋል።
በአውሮፓ ሕብረት፣ የቡድን 7 አባል አገራት እና መሰል ስብሰባዎች ላይ ከአፍሪካ ጋር የትብብር ግንኙነቶች እንዲጠናከሩ የማድረግ ፍላጎት መኖሩን ጠቁመዋል። አሕጉሪቷ ከዓለም መንግስታት ጋር ያላትን ግንኙነት በማጠናከር በኩል የተለያዩ ስራዎች መከናወናቸውን አስታውቀዋል። በዓለም ምጣኔ ሃብትና የፋይናንስ ስርአት ፍትሃዊነት ጉዳይ እንዲሁም የቡድን 20 አባል ሀገራት ሙሉ አባል ለመሆን አፍሪካ ያቀረበችው ጥያቄ በመልካም ሂደት ላይ መሆኑን አስታውቀዋል።
በአሁኑ ወቅት ሩስያ፣ አሜሪካ፣ ፈረንሳይ፣ ደቡብ አፍሪካ እና ቻይናን ጨምሮ ከ20 በላይ የቡድን 20 አባል አገራት ድጋፋቸውን መግለጻቸውንም ያብራሩት ማኪሳል፤ ሌሎች አባል ሀገራትም ይህንን ድጋፍ በመቀላቀል በቀጣይ በህንድ በሚካሄደው የአባል ሀገራቱ ስብሰባ ላይ አፍሪካ የቡድን 20 አባልነት ዕውን ይሆናል የሚል ግምት እንዳላቸው ገልጸዋል።
በአሕጉሪቱ የምጣኔ ሃብት መነቃቃትን ለማምጣት የተፈጥሮ ሃብትን በመጠቀም ለዓለም ገበያ በተወዳዳሪ ዋጋ ማቅረብ እንደሚያስፈልግ፤ በተለይም በአሕጉሪቱ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ማግኘት ላልቻሉ ከ600 ሚሊዮን በላይ ዜጎች የኃይል አቅርቦት ዕውን ማድረግም ጊዜ ሊሰጠው አይገባም ብለዋል። የአፍሪካ ምጣኔ ሃብት የሚያስፈልገውን ያህል የፋይናንስ አቅርቦትና ድጋፍ እያገኘ ባለመሆኑ የፋይናንስ ድጋፍና አማራጭን ማጠናከር እንደሚገባ አሳስበዋል።
* ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ
“በተመድ የጸጥታው ምክር ቤት አፍሪካ ቋሚ መቀመጫ ይገባታል”፤ እንዲሁም “ለአፍሪካ ትክክለኛና ሚዛናዊ መረጃ የሚያቀርብላት የአፍሪካ ህብረት አሕጉራዊ ሚዲያ ያስፈልጋል ብለዋል።
ባለፉት ዓመታት ኢትዮጵያ በገጠማት ችግር ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች የተሳሳተ መረጃ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ሲያደርሱ ቆይተዋል፤ ይህን አይነቱን ችግር ለዘለቄታው ለመቋቋም ለአፍሪካ ትክክለኛና ሚዛናዊ መረጃ የሚያቀርብላት የአፍሪካ ሕብረት አሕጉራዊ ሚዲያ መቋቋም እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል።
“አፍሪካዊ ችግሮችን አፍሪካዊ መፍትሔ” በሚል መርህ ከሁለት ዓመት በፊት በኢትዮጵያ ሰሜኑ ክፍል የተከሰተውን ጦርነት ለማቆም ኢትዮጵያ አፍሪካዊ መፍትሄን አግኝታለች፤ በዚህም አፍሪካ ችግሮችን በሰላማዊ መንገድ እየፈታች ለመሆኑ ማሳያ ነው”ብለዋል። የሰሜኑ ጦርነት እንዲቆም የአፍሪካ ሕብረት ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል” ሲሉ ምስጋና አቅርበዋል። አፍሪካ ብዙ ችግሮች አሉባት፣ ያለ ውጭ ጣልቃ ገብነት እነዚህን መፍታት የሚቻለው በውይይት በትብብር መስራት ሲቻል እንደሆነም ጠቁመዋል።
“ኢትዮጵያ ባለፉት አራት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራና በበጋ መስኖ በምግብ ራሷን ለመቻል ውጤታማ ስራ ሰርታለች”፤ ከ25 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል የአየር ንብረትን ለመቋቋም የሚያስችል አቅም ገንብታለች። በምግብ ራሷን ለመቻል ባደረገችው ጥረት የበጋ የስንዴ መስኖ በመዝራት ከራሷ አልፋ ወደ ውጭ መላክ ጀምራለች” ብለዋል።
* የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋቂ መሃመት
የአፍሪካ ሕብረት ሁሉንም አባል ሀገራት ማዕከል ያደረገና የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ እንዲሆን እየሰራን እንገኛለን። በዓለም የሚታየውን የተዛባ አመለካከትና የመንግስታት አስተዳደር ለማስተካከል አሁንም ድምጻችንን ማሰማት መቀጠል ይገባል ፤ አፍሪካን ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት ማግለል ኢፍትሃዊ ውሳኔ ነው ብለዋል።
በአሕጉሪቱ የሚታዩ የፖለቲካና የደህንነት ችግሮች አሁንም ፈተና ሆነው መቀጠላቸውን በመጥቀስ ህገ መንግስታዊ ስርዓት በጣሰ መልኩ የሚደረጉ የመንግስታት ለውጦች ሀገራትን የመበታተን አደጋ እንደደቀነባቸውም አመልክተዋል።
ሽብርተኝነትና ከምርጫ ውጭ ስልጣን ለመያዝ የሚደረግ ጥረትና የአየር ጸባይ ለውጥ አሁንም የአጉሪቱ ችግሮች ሆነው መቀጠላቸውን፤ በአሕጉሪቱ ህገ መንግስትን በጣሰ መልኩ ስልጣን የሚወጡ ኃይሎች ላይ የሚጣሉ ማዕቀቦች ውጤት ከማስገኘት ይልቅ ህዝብን ለችግር መዳረጋቸውን አስታውሰዋል። በመሆኑም ማዕቀቡ የሀገራትን ኢኮኖሚ የሚያንኮታኩትና ከፍተኛ ተጽዕኖ የሚያሳድር መሆኑን በመገንዘብ አማራጭ የመፍትሄ እርምጃ ማስቀመጥ እንደሚገባ አሳስበዋል።
“አፍሪካን በ2030 የጥይት ድምጽ የማይሰማባት አሕጉር” ለማድረግ የተጀመሩ ጥረቶች ግባቸውን እንዲመቱ ሕብረቱ ከፍተኛ ገንዘብ በመመደብ እየተንቀሳቀሰ ነው፤ “የተደቀኑ ችግሮችንና ይዘዋቸው ሊመጡ የሚችሉ ፈተናዎችን ቀድመን በመገንዘብ በጋራ ልናልፋቸው ይገባል” ብለዋል።
የአፍሪካ ሀገራት የኢኮኖሚ ዕድገት ባለፉት ሶስት ዓመታት በገጠሙት ዘርፈ ብዙ ችግሮች በነበረበት መቀጠል አልቻለም ያሉት ሙሳ ፋኪ፣ “የዋጋ ግሽበቱ ከሚጠበቀው በላይ ማሻቀብ፣ የነዳጅ ዋጋ መጨመርና ግጭት የአሕጉሪቱ ሳንካዎች ሆነው ቀጥለዋል፤ ይህ ደግሞ የሀገራትን ኢኮኖሚ የሚያንኮታኩትና አሉታዊ ተፅዕኖ የሚያሳድር መሆኑን በመገንዘብ አማራጭ የመፍትሄ እርምጃ ማስቀመጥ እንደሚገባ አመልክተዋል።
* የተመድ ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ
“አፍሪካ አፍሪካ እምቅ የሆነ የመልማት አቅም አላት። ይህን አቅም ለማልማትና ያሉባትን ችግሮች ለመፍታት በምታደርገው ጥረት የተባበሩት መንግስታት ድጋፍ ያደርጋል፤ “ነጻ የንግድ ቀጠናን ማሳለጥ ለስራ እድል ፈጠራ ወሳኝ በመሆኑ አፍሪካ በ2060 ለያዘችው የግብ አጀንዳ ያላትን ሀብት በአግባቡ በመጠቀም ህዝቡ ያለበትን ችግር በመፍታት የተሻለ እድገት ማስመዝገብ ተገቢ ነው” ብለዋል። “ለዚህ ግብ ስኬት ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት እገዛ ማድረግ እንዳለባቸው አመልክተዋል።
የዓለም የፋይናንስ ስርዓት ፍትሃዊ በሆነ መልኩ ለአፍሪካና አጠቃላይ በማደግ ላይ ላሉ ሀገሮች በሚጠቅም መልኩ መቃኘት ይኖርበታል፤ ዓለምን እየፈተነ ላለው የአየር ንብረት ለውጥ ችግርም ዕልባት ለማበጀት የጋራ ጥረት ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል። ለዚህ ደግሞ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካን የልማት እቅዶች በመደገፍ በአሕጉሪቱ ዘላቂ ሰላምና ቀጣይነት ያለው ዕድገት ዕውን እንዲሆን ድጋፉን እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
* አዛሊ አሱማኒ/የኮሞሮሱ ፕሬዚዳንት የወቅቱ የአፍሪካ ሕብረት ሊቀመንበር /
“የአፍሪካ አገራትን የብድር ጫና ለማቃለል አበዳሪ አገራትና ዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማት የጋራ የብድር ማቅለያ ማዕቀፍ በማበጀት ሊሰሩ ይገባል” ብለዋል።
ባለፈው የፈረንጆች ዓመት የኮቪድ 19 ወረርሺኝ እና የዩክሬንና የራሽያ ጦርነት በዓለም አቀፍ ደረጃም ሆነ በአፍሪካ ከባድ ተጽዕኖ ማሳደሩን፤ ይህንንም ተከትሎ የአፍሪካ አጠቃላይ እድገት ከሦስት በመቶ እንዳይልቅ ማድረጉን በመጥቀስ በአንጻሩ የአህጉሪቱ የውልደት መጠን ከፍተኛ መሆኑ አሉታዊ ጫና አሳድሯል ብለዋል።
በተለይም የአህጉሪቱን የማኅበራዊና መሰረተ-ልማት በተፈለገው ደረጃ እንዳያድግ በማድረግ 22 የሕብረቱ ሀገራት የብድር ጫና ውስጥ ስለመሆናቸው የዓለም ባንክን መረጃ የጠቀሱት አዲሱ የሕብረቱ መሪ፣ እነዚህ አገራት ዕዳቸውን ለመክፈል ስለሚያዳግታቸው የብድር ጫናውን ለማቃለል አበዳሪ ሀገራትና ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት የጋራ የብድር ማቅለያ ማዕቀፍ ሊያዘጋጁላቸው እንደሚገባ ጠቁመዋል። “ምዕራባውያን ከወራት በፊት ለአፍሪካ የኢኮኖሚ ማገገሚያ የሚውል 150 ቢሊየን ዩሮ ለመስጠት የገቡትን ቃል በመጠበቅ ገንዘቡን በፍጥነት መልቀቅ እንዳለባቸው አሳስበዋል።
“የዩክሬንና የሩስያ ጦርነት አፍሪካ ራሷን መቻል እንዳለባት አሳይቶናል” ያሉት አዛሊ፤ በተለይም የግብርና ዘርፉን ማጠናከር ወሳኝ መሆኑን አስታውቀዋል። በአሕጉሪቱ የምጣኔ ሃብትና ጠንካራ የፖለቲካ ሥርዓት ግንባታ ውስጥ የሴቶችን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ማሳደግ በእሳቸው የአመራር ዘመን ቅድሚያ የሚሰጠው ሥራ እንደሚሆንም ገልጸዋል። በአፍሪካ ሀገራትና አጋር አካላት እንዲሁም ከሌሎች አቻ ተቋማት ጋር ያለውን ትብብር በማጠናከር አህጉሪቱን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ለማሻገር በሊቀ-መንበርነት ጊዜያቸው የሚሰሩ መሆኑንም አረጋግጠዋል።
ግርማ መንግስቴ
አዲስ ዘመን የካቲት 17 ቀን 2015 ዓ.ም