
-የሕግ ማስከበሩ እርምጃ ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስቧል
አዲስ አበባ፡- የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፤ ሰሞኑን በምዕራብ ወለጋ እና በሌሎች አካባቢዎች በአሸባሪው ሸኔ እና ሌሎች መሰል ተላላኪ ጽንፈኛ ኃይሎች አማካኝነት፣ በንጹሐን ዜጐች ላይ የደረሰውን ጭፍጨፋ በጽኑ አወገዘ። መንግሥት የጀመረውን ሕግ የማስከበር እርምጃ አጠናክሮ እንዲቀጥልም አሳስቧል።
የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጭፍጨፋውን ያወገዘው እና ሕግ የማስከበሩ ተግባር እንዲጠናከር ያሳሰበው፤ በሀገራዊ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የሀገሪቱን ፀጥታ ከሚመሩ እና ከምክር ቤቱ ከፍተኛ አመራሮች ጋር በስፋት በተወያየበት ወቅት ነው።
የምክር ቤቱ አባላትም በምጣኔ-ሀብታዊ፣ ፖለቲካዊ እንዲሁም በሰላም እና ፀጥታ ጉዳዮች ላይ በጥልቀት መክረዋል።
ምክር ቤቱ ውይይቱን አስመልክቱ እንደገለጸው፤ በቅርቡ በተለያዩ የሀገራችን ስፍራዎች ማለትም በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በጋምቤላ፣ በደቡብ፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ እና በሌሎችም አካባቢዎች፤ ዜጎች ጭካኔ በተሞላበት መንገድ ሕይወታቸውን አጥተዋል። ከሞት የተረፉትም ተፈናቅለዋል፤ ለአካል እና ሥነ-ልቦናዊ ጉዳት ተዳርገዋል። ሀብት ንብረትም ወድሟል። ይህንንም ዕኩይ ተግባር ምክር ቤቱ በጽኑ ያወግዛል።
ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታትም፤ የምክር ቤቱ አባላት የየራሳቸውን ድርሻ እንደሚወጡ በምክክር መድረኩ ላይ አረጋግጠዋል።
አባላቱ በቀጣይ ትኩረት በሚፈልጉ አንገብጋቢ ጉዳዮች ላይም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሆነው ችግሩን ለመፍታት እንደሚሠሩም ያስታወቁ ሲሆን፤ በአሁኑ ጊዜ እያጋጠሙ ያሉ ችግሮችንም በአንድነት ቆመን መሻገር አለብን ብለዋል።
ለሕዝባችን ሕልውና ቀን እና ማታ ከሚለፉ የፀጥታ አካላት ጋር በመሆን የሚሠሩ ተግባራትንም በተመለከተ፤ ሁሉም የምክር ቤቱ አባላት ከሌሎች የመንግሥት አካላት ጋር በመሆን በቁርጠኝነት ለመንቀሳቀስ ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል።
ከውስጥ እና ከውጭ ኃይሎች የተጋረጠብንን የሕልውና ጥያቄ ለመመለስ፤ በመንግሥስት በኩል የተያዘውን የለውጥ መንገድ ማገዝ ይገባል ያሉት የምክር ቤት አባላቱ፤ ለተግባራዊነቱም በትጋት እንደሚረባረቡ የጋራ አቅጣጫ አስቀምጠዋል።
ስለሆነም በቀጣይ፡- የዜጎችን የሰላም ችግር በዘላቂነት መፍታት፤ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን እና ብልሹ አሠራሮችን በትጋት መታገል የሕብረተሰቡን የኑሮ ውድነት ችግር ለመፍታት ምርት እና ምርታማነትን ለማረጋገጥ መረባረብ እና ከባለድርሻ አካላት ጋር መሥራት እንዲሁም የክረምት ሥራዎችን በትኩረት ማከናወን የሚሉት ዐበይት አቅጣጫዎች ሆነው ተነድፈዋል።
በተጨማሪም፤ “የተጋረጠብንን የውስጥ እና የውጭ ጥቃት እና ሴራ ለማክሸፍ እና ለማለፍ፣ ከመቼውም ጊዜ በላይ በአንድነት ቆመናል” ሲሉ የምክር ቤቱ አባላት በአቋም ገልጸዋል።
የምክር ቤት አባላቱ እንደገለጹት፤ ሀገራችን ኢትዮጵያ ከራሷ አልፎ ለጐረቤቶቿ ብሎም ለመላው አፍሪካ የሚተርፍ ብዙ የታሪክ እና የባሕል ብሎም የመልካምነት ትውፊት ባለቤት ናት። ለጎረቤት ሀገራትም የፖለቲካዊ፣ ማሕበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ትብብር ተምሳሌት ሆና ቆይታለች። ይህም የሆነው፤ ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊውያን በወንድማማችነት፣ በአብሮነት እና በአንድነት በጽኑ ስለሚያምኑ ነው።

ኢትዮጵያ እንደ ሀገር በለውጥ እንቅስቃሴ ውስጥ እንደምትገኝ የገለጹት የምክር ቤቱ አባላት፤ ባለፉት አራት ዓመታት ውስጥ ለውጡን መቀልበስ የሚፈልጉ የውስጥ እና የውጭ ኃይሎች ግንባር ፈጥረው የተለያዩ ተግዳሮቶችን ሲፈጥሩ መቆየታቸውንም አንስተዋል።
ሀገራችን በእነዚህ ጊዜያት በርካታ ፈተናዎች ቢገጥሟትም፤ መንግሥት በወሰዳቸው ጠንካራ እርምጃዎች የተነሳ፤ ዓለም-አቀፋዊ እና የሀገር ውስጥ ጫናዎች ያልበገሩት አዎንታዊ ዕድገት በሁሉም መስክ መመዝገቡን አባላቱ በመልካም ጎኑ ገምግመዋል።
ኢኮኖሚው በብዙ ጫናዎች ውስጥ ሆኖም አዎንታዊ ዕድገት ማስመዝገቡን የገለጹት የፓርላማው አባላት ገቢ የመሰብሰብ አቅማችን መጨመሩ፣ ከወጪ ምርት የምናገኘው የውጭ ምንዛሪ ማደጉ፣ በበጋ ስንዴ ምርት አበረታች ውጤት መመዝገቡ እና የመሳሰሉት መልካም ውጤቶች ቀጣይነት ኖሯቸው እንዲጠናከሩም አበክረው አሳስበዋል።
የሕብረተሰቡን የኑሮ ውድነት ችግር ለመፍታት ምርት እና ምርታማነትን ለማረጋገጥ መረባረብ እና ከባለድርሻ አካላት ጋር መሥራት እንዲሁም የክረምት ሥራዎችን በትኩረት ማከናወን የሚሉት ዐበይት አቅጣጫዎች ሆነው ተነድፈዋል።
እንደ ሀገር አሁን እያጋጠሙ ያሉ ፈተናዎችን በድል ለመሻገር በተባበረ እና በኢትዮጵያዊ አንድነት መንፈስ መቆም ብቸኛው እና የተሻለው አማራጭ መሆኑን የምክር ቤቱ አባላት አጽንኦት ሰጥተው መወያየታቸውን ከምክር ቤት የተገኘው መረጃ አመልክቷል።
በጋዜጣው ሪፖርተር
አዲስ ዘመን ሰኔ 25 ቀን 2014 ዓ.ም