እ.ኤ.አ በ1950 በዓለም አቀፍ ደረጃ የሰዎች አማካይ የመኖር ዕድሜ ከ46 ዓመት የዘለለ እንዳልነበረ መረጃዎች ያመለክታሉ። ሆኖም እ.ኤ.አ ከ2015 ወዲህ አማካይ የሰዎች የመኖር ዕደሜ ወደ 71 ከፍ ማለቱን ቢቢሲ ‹our world in dat. org› የተሰኘው ድርጅት ተመራማሪ የሃናን ሪቼን ጥናት በመጥቀስ ከሰሞኑ በጤና ገፁ ይፋ አድርጓል። በአንዳንድ ሀገራት በተከሰቱ በሽታዎችና ያልተጠበቁ ወርረሽኞች ምክንያት የሰዎች አማካይ የመኖር ዕድሜ ለማሻሻል የተደረገው ጥረት አልጋ በአልጋ እንዳልነበርም መረጃው አያይዞ ጠቅሷል።
ዜሮ ነጥብ አምስት በመቶ ለሚሆነው የሰዎች ሞት ሽብርተኘነት፣ ጦርነትና ልዩ ልዩ የተፈጠሮ አደጋዎች በምክንያትነት የሚጠቀሱ ቢሆንም በቀላሉ መከላከል በሚቻሉ በሽታዎች ምክንያት አሁንም በዓለም ዙሪያ በርካቶች ያለዕድሚያቸው እንደሚቀጠፉ መረጃው ያትታል። ሰዎች የሞቱበት ዘመን ታሪክ፣ እንዴት እንደሞቱና ይህ በጊዜ ሂደት እንዴት እንደተቀየረ የሚያሳይ ታሪክ ነው ሲልም ይገልጻል። መረጃው በዓለም አቀፍ ደረጃ የሰዎችን አማካይ የመኖር ዕድሜ በቀጣና ከፋፍሎ ያስቀመጠ ሲሆን፤ በ79 ነጥብ 5 ዓመት የሰሜን አሜሪካ ሀገራት ከፍተኛ አማካይ የመኖር ዕድሜ ባለቤት በመሆን ቀዳሚ ሆነዋል።
አውሮፓ በ77 ነጥብ 7፣ ደቡብ አሜሪካ በ75 ነጥብ 1 እና የእስያ ሀገራት በ72 ነጥብ 4 ይከተላሉ። ከአፍሪካ አህጉር የሰሜን አፍሪካ ሀገራት በ71 ነጥበ 7 ዓመት ሲመሩ ከሳሀራ በታች ያሉ የአፍሪካ ሀገራት ደግሞ በ59 ነጥብ 3 የመጨረሻውን አማካይ የመኖር ዕድሜ ደረጃ ይዘዋል። በጥቅሉ ዓለም አቀፍ የሰዎች አማካይ የመኖር ዕድሜ 71 ነጥብ 4 መድረሱንም መረጃው አረጋግጧል። መረጃው እንዳመከተለው፤ እ.ኤ.አ በ2017 ብቻ 56 ሚሊዮን የዓለም ህዝብ በተለያዩ ምክንያቶች ሞቷል። ምንም እንኳን የዓለም ህዝብ ቁጥር እየጨመረና የሰዎች አማካይ የመኖር ዕድሜም በእጅጉ እየተሻሻለ ቢመጣም እ.ኤ.አ በ1999 ከነበረው የሞት መጠን ጋር ሲነፃፀር የሞት መጠን አሃዝ የ10 ሚሊዮን ብልጫ አሳይቷል።
ከ70 በመቶ በላይ የሚሆኑት የዓለም ህዝቦች ደግሞ ተላላፊ ባልሆኑና ዕድሜ ዘለቅ በሽታዎች ምክንያት ህይወታቸውን አጥተዋል። ከእነዚህ ተላላፊ ካልሆኑ በሽታዎች ውስጥ ልብንና የደም ስሮችን የሚያጠቃው የልብና የደም ስር በሽታ እያንዳንዳቸው ከሚከሰቱ ሦስት ሞቶች ውስጥ ትልቁን ድርሻ ወስዷል። ይህም ለሰዎች ሞት ሁለተኛው ምክንያት ከሆነውና ከሚከሰቱ ስድስት ሞቶች ውስጥ አንዱ ከሆነው የካንሰር ህመም በሁለት እጥፍ የሚበልጥ ነው። ስኳር፣የመተንፈሻ አካላት በሽታዎች፣ የአዕምሮ ህመሞችና ሌሎች ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችም በዓለም ዙሪያ ለሚከሰት ሞት ተጨማሪ መንስኤ ሆነዋል።
መረጃው በዓለም ዙሪያ ለሰዎች ሞት ዋነኛ መንስኤ ናቸው ያላቸውን መረጃው ጠቁሟል። የልብና የደም ስር በሽታዎች 32 ነጥብ 3 በመቶ የሚሆነውን በመሸፈን ቀዳሚ ናቸው። 16 ነጥብ 3 በመቶውን ካንሰር፣ 6 ነጥብ 5 በመቶውን የመተንፈሻ አካላት በሽታዎች፣ እንዲሁም 5 ነጥብ 8 በመቶ የሚሆነውን የስኳር በሽታ በመያዝ ተከታዮቹን ደረጃዎች ይዘዋል። ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ከሚሞቱ የዓለም ህዝቦች ቁጥር ባልተናነሰ መልኩ በቀላሉ መዳን በሚችሉ በሽታዎች ምክንያት የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር በአስደንጋጭ ሁኔታ እያሻቀበ መምጣቱንም መረጃው አክሎ አመላክቷል። እ.ኤ.አ በ2017 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን የሚሆኑ ሰዎች ዋነኛ ገዳይ ተብለው ከተፈረጁ አስር በሽታዎች መካከል በተቅማጥ በሽታ ህይወታቸው ተነጥቀዋል።
በአንዳንድ ሀገራትም በሽታው ዋነኛ የሰው ህይወት መጥፊያ ሆኗል። በተመሳሳይም በመጀመሪያዎቹ 28 ቀናት በሚፈጠሩ የጤና እክሎች ምክንያት 1 ነጥብ 8 ሚሊን የሚጠጉ ጨቅላ ሕፃናት በዚሁ ዓመት ሞተዋል። በዚህ ምክንያት የሚከሰተው ሞት ከሀገር ሀገር የሚለያይ መሆኑንም መረጃው የጠቆመ ሲሆን፤ በጃፓን በዚህ ምክንያት የሚከሰተው የጨቅላ ሕፃናት ሞት ከአንድ ሺ ሕፃናት መካከል ከአንድ በታች እንዲሁም በዕድገት ወደኋላ በቀሩ ሀገራት ከአንድ ሺ ሕፃናት መካከል ሃያ መሆኑን በንፅፅር አስቀምጧል። ሌሎች መከላከል የሚቻሉ በሽታዎችም በዓለም ዙሪያ የሚከሰተውን የሞት መጠን ከፍ እንደሚያደርጉም መረጃው አያይዞ ጠቅሷል።
ባደጉና ባላደጉ ሀገራት ውስጥ የሚከሰቱ የመንገድ ላይ የትራፊክ አደጋዎች ለሞቱ ማሻቀብ የድርሻቸውን እንደተወጡም መረጃው አክሎ ጠቅሷል። በዚህም እ.ኤ.አ በ2017 ብቻ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን የሚሆኑ የዓለም ህዝቦች በመንገድ ላይ የትራፊክ አደጋ ህይወታቸውን አጥተዋል። ከቅርብ አስርት ዓመታት ወዲህ ኢኮኖሚያቸው ከፍተኛ ደረጃ የደረሰ ሀገራት በመንገድ ላይ የትራፊክ አደጋዎች ምክንያት የሚከሰተውን የሞት መጠን በመቀነስ ረገድ ከፍተኛ እምርታ ያሳዩ ቢሆንም፤ በዚሁ ምክንያት በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚከሰተው የሞት መጠን ግን አሁንም ሊቀንስ አልቻለም።
ራስን በማጥፋትና አንዱ ሌላኛውን በመግደል የሚከሰተው ሞትም ለሰዎች ሞት ማሻቀብ የራሱን አስተዋጽኦ አበርክቷል። በእንግሊዝ ብቻ ራስን ማጥፋት ዕድሜያቸው ከ20 አስከ 40 ለሚሆኑ ወንዶች ሞት ዋነኛ መንስኤ እየሆነ እንደመጣም መረጃው ጠቅሷል። ሀገራት ባደጉ ቁጥር ሰዎች የሚሞቱባቸውምክንያቶች በጊዜ ሂደት እንደሚለወጡ የጠቀሰው ይኸው መረጃ፤ ባለፉት ዓመታት ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች በአሁኑ ወቅት እያደረሱ ካሉት ጉዳት በበለጠ ለዓለም ህዝቦች ሞት መጨመር ትልቁን ሚና መጫወታቸውን ጠቁሟል። እ.ኤ.አ በ1999 እንኳ ከሦስት ሞቶች መካከል አንዱ የተከሰተው በእነዚሁ ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ምክንያት ሲሆን እ.ኤ.አ በ2017 ግን ይህ አሃዝ ከአምስት ሞቶች ወደ አንድ ዝቅ ብሏል። ሕፃናት ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎች የበለጠ ተጋላጭ መሆናቸውንም መረጃው አመልክቷል።
በ19ኛው ክፍለ ዘመን እንኳ በርካታ የዓለም ሕፃናት አምስት ዓመታቸውን ሳያከብሩ ይሞቱ እንደነበር መረጃው አስታውሶ፣ የክትባት እንደ ልብ መገኘት፣ የግልና የአካባቢ ንፅህና፣ ስርዓተ ምግብ፣ የጤና እንክብካቤና የንፁህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት መሻሻል ለሕፃናት ሞት መጠን በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ የራሱን አስተዋፅኦ አበርክቷል። የሕፃናት ሞት ባደጉት ሀገራት በአሁኑ ወቅት ያልተለመደና ምንአልባትም ምንም የለም በሚያስብል ደረጃ ላይ የሚገኝ ቢሆንም በዕድገት ወደኋላ በቀሩት ሀገራት የሚከሰተው የሕፃናት ሞት መጠን ግን በእንግሊዝና በሳዑዲ አረቢያ በ20ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ ሲከሰት ከነበረው የሞት መጠን ጋር ተመሳሳይነት ያለውና አሁንም ቁጥሩ ያሻቀበ መሆኑን ያሳያል። አምስት ዓመታቸውን ሳያከብሩ የሚሞቱ ሕፃናት መጠንን በሀገራት በንፅፅር መረጃው አመልክቷል። እ.ኤ.አ ከ2000 አስከ 2015 ባለው ጊዜ በሴራሊዮንና በናይጄሪያ ከ10 በመቶ በላይ የሚሆኑ ሕፃናት አምስት ዓመታቸውን ሳያከብሩ ሞተዋል።
በኮንጎ ብራዛቪልም ከ6 አስከ 7 በመቶ የሚሆኑ ሕፃናት አምስት ዓመታቸውን ሳያከብሩ ይህችን ዓለም ተሰናብተዋል። ይሁንና በእንግሊዝና በሳዑዲ አረቢያ አምስት ዓመታቸውን ሳያከብሩ የሞቱ ሕፃናት አልነበሩም ሲል መረጃው ገልጿዋል። ‹‹በዓለም አቀፍ ደረጃ የሕፃናት ሞት በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ የዘመናዊው ህክምና ዓለም ትልቁ ስኬት ተደርጎ ይቆጠራል›› ሲል መረጃው ያትታል። ‹‹በቅርብ አስርት ዓመታት ውስጥ ተላላፊ በሽታዎችን መዋጋት በመቻሉ በየዓመቱ የሚሞቱ ሕፃናትን ቁጥር በግማሽ መቀነስ ተችሏል›› ሲልም ይገልፃል። ‹‹ይህም ተላላፊ በሆኑ በሽታዎች ምክንያት በሕፃናት ላይ የሚከሰተው የሞት መጠን ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ምክንያት በአዋቂዎች ላይ ወደሚከሰት ሞት መሸጋገሩን ይጠቁማል።››
በማለት አመልክቷል። ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች በዓለም ህዝብ ላይ እያደረሱ ያሉት ጫና ከፍተኛ መሆኑንና ዕድሜ ዘለቅ በሽታ ከመሆናቸው አኳያ ረጅም የህክምና ሂደቶችን የሚጠይቁ በመሆናቸው በርካታ ሀገራትን እያሳሰቡ እንደሚገኙም መረጃው ጨምሮ ገልጿል። እ.ኤ.አ ከ1990 አስከ 2017 ባሉት ዓመታት ውስጥ አምስት ዓመት ሳይሞላቸው የሚሞቱ ሕፃናት መጠን በቀጣና ሲታይም የሰሜን አሜሪካ፣ አውሮፓ፣ መካከለኛው ምሥራቅ፣ ላቲን አሜሪካ እና የእስያ ፓስፊክ ሀገራት በቅደም ተከተላቸው አነስተኛ ከአምስት ዓመት በታች የሕፃናት ሞት የሚከሰትባቸው ነበሩ። የደቡብ እስያና ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ ሀገራት ከፍተኛ ከአምስት ዓመት በታች ሕፃናት ሞት የሚታይባቸው ናቸው። በዓለም አቀፍ ደረጃ የሰዎች አማካይ የመኖር ዕድሜ በከፍተኛ ደረጃ መሻሻሎችን ያሳየ ቢሆንም በተለያዩ ምክንያቶች በተለይም ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ምክንያት እየደረሰ ያለው የሞት መጠን አሁንም አሳሳቢ መሆኑን መረጃው ያመለክታል። ይሁን እንጂ ይህን ክስተት ሊቀይሩ የሚችሉ ዕድሎች አሁንም እንዳሉ ይጠቁማል።
ለዚህም እ.ኤ.አ 1980 በዓለም አቀፍ ዙሪያ ኤች.አይ.ቪ ኤድስ ያደረሰውን ቀውስ በአብነት ያነሳል። ወረርሽኙ በሁሉም የዓለም ክፍሎች የተከሰተ ቢሆንም በሰዎች አማካኝ የመኖር ዕድሜ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ ያሳደረው ከሰሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪካ ሀገራት ላይ መሆኑን መረጃው ያስታውሳል። ይሁንና ከአስርት ዓመታት ብርቱ ሥራ በኋላ ቫይረሱን በመከላከል ረገድ መሻሻሎች በመምጣታቸው በቀጣናው የሚገኙ ህዝቦች አማካይ የመኖር ዕድሜ ከፍ ማለቱንም ይጠቅሳል። በተለይም የፀረ ኤች.አይ.ቪ መድሃኒቶች በስፋት ጥቅም ላይ መዋል፣ የህክምና ክትትል ባህል እያደገ መምጣትና በቫይረሱ መከላከያ መንገዶቸ ላይ ትምህርት ከመስጠት ጋር ተዳምሮ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከኤች.አይ.ቪ ኤድስ ጋር በተያያዘ በየዓመቱ የሚሞቱ ሁለት ሚሊዮን ሰዎች ቁጥር ወደ አንድ ሚሊዮን ማሽቆልቆል ችሏል።
የሰዎች አማካይ የመኖር አድሜ በብዙ ሀገራት እየተሻሻለ የመጣ ቢሆንም በአሁኑ ወቅት ሰዎች የሚሞቱባቸው መንገዶች እየበዙ ከመምጣታቸው አኳያና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች እያደረሱ ካለው ጫና አንፃር የሰዎች አማካይ የመኖር ዕድሜ ወደነበረበት ሁኔታ እንዳይመለስ ስጋት እንዳለም መረጃው ያብራራል። ‹‹ባደጉት ሀገራትም ይህ የሰዎች አማካይ የመኖር ዕድሜ መሻሻል ወጥነትና ቀጣይነት ያለው አይመስልም›› ሲል ይገልፃል። በአሜሪካ አማካይ የመኖር ዕድሜ ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ በመድሃኒቶች ያልተገባ አጠቃቀም ምክንያት እየወረደ መምጣቱንም ለአብነት ጠቅሷል። የአዲስ ወላድ እናቶች አማካይ የመኖር ዕድሜም ወጥ በሆነ መንገድ እየጨመረ እንዳልሆነና አሜሪካንን ጨምሮ በሌሎች አስር ሀገራት አሁንም እናቶች በወሊድ ወቅትና ከወሊድ በኋላ እንደሚሞቱ መረጃው አያይዞ ገልጿል። መረጃው እንዳመለከተው፤ በአሁኑ ወቅት አጠቃላይ የዓለም ምስል ሰዎች ረጅም ዕድሜ እየኖሩ እንደሆነ የሚያሳይ ቢሆንም፣ የዚያኑ ያህል ጥቂት የማይባሉ ሰዎች በተለይም ሕፃናት በቀላሉ መከላከል በሚቻሉ በሽታዎች እየሞቱ ይገኛሉ።
ይህም ቀሪ የቤት ሥራዎች እንዳሉ ያስገነዝባል። በተለይም በአካባቢና የግል ንፅህና፣ በስርዓተ ምግብ፣ በክትባትና በመሰረታዊ የጤና አገልግሎት ማስፋፊያ ዙሪያ አሁንም ተጨማሪ ሥራዎች መሠራት እንዳለባቸው ያሳያል። እየተሻሻለ የመጣውን የሰዎች አማካይ የመኖር ዕድሜ በነበረበት ለማስቀጠል ከተፈለገም ሰዎች የሚሞቱባቸውን ምክንያቶች መገንዘብ የግድ ይላል።
አዲስ ዘመን መጋቢት 3/2011
በአስናቀ ፀጋዬ