የኢትዮጵያ ስነ ጽሁፍ ውስጥ ወፍራም ስም ካላቸው ደራሲያን ተርታ ይሰለፋል። አድናቂዎቹ እንደውም እሱ የኢትዮጵያ ስነ ጽሁፍ ንጉሠ ነገሥት ነው ይሉታል። ድርሰቶቹ ከባድ እንደሆኑ የሚናገሩ ብዙ ናቸው። የእሱን ድርሰት አንብቤያለሁ ማለትም እንደ አንድ ዘመናይነት መታየት ጀምሯል። ሰውየው ብዙም ለሕዝብ ዓይን ቅርብ ያልሆነው፤ ነገር ግን አንድን የስነ ጽሁፍ ዘመን በሥራዎቹ የዋጀው አዳም ረታ ነው።
የተወለደው ሐምሌ 8 ቀን 1950 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ነው። የትውልድ ስሙ አዳሙ ነበር። የደራሲነት ጸጋው መታየት የጀመረው ገና በልጅነቱ ነው። በአንድ ወቅት በአዲስ ነገር ጋዜጣ ላይ ስለዚህ የተናገረውን እንመልከት። ‹‹5ኛ ክፍል እያለሁ ዓርብ ዓርብ ከሰዓት በኋላ ሪፖርት እናቀርባለን። ደንቡ ከጋዜጣ ያነበብነውን ወይም ከሬዲዮ የሰማነውን ነገር በራሳችን አማርኛ አሳጥረን ጽፈን ክፍል ውስጥ ማቅረብ ነው። ሁልጊዜ ርዕስ የሚሆኑት የጃንሆይ ጉብኝት ፤ የአዲስ አበባ አንደኛ ዲቪዚዮን እግር ኳስ ውድድር ውጤት እና የመካከለኛው ምስራቅ ግጭት ነው። ነገር ግን ይህን መጻፍ ሰለቸኝ።
አንድ ቀን በመንገድ ላይ ስሄድ የዶሮ ነጋዴዎች ኃይለኛ አውሎ ነፋስ መጥቶ ሲያተራምሳቸው እና ዶሮዎቹ ከቅርጫት እየበረሩ ሲያመልጡ ነጋዴዎቹም እነሱን ለመያዝ የሚያደርጉትን መውደቅና መነሳት አየሁ እና ገረመኝ። ያን ለመጻፍ ወሰንኩ። ጽፌም ክፍል ውስጥ አቀረብኩና ተማሪዎቹን ትንሽ አስደሰትኳቸው። ከዚያ መምህሩ ከየት አመጣኸው ሲሉን ከጋዜጣ አንብቤ ነው አልኩ። ጋዜጣ ላይ እንዲህ አይነት ነገር አይጻፍም ብለው ጢሜን አበረሩኝ። ከዚያ ግን ለተማሪዎች አዳሙ ደራሲ ነው የሚሆነው ብለው ተናገሩ። ደራሲ መሆን ማለት ምን ማለት እንደሆነ ያኔ አልገባኝም።››
አዳም ያኔም መጻፍ ይወድ ነበር። ከመጻፍ በተጨማሪ ጎበዝ አንባቢም ነበር። ከዘነበ ወርቅ ተነስቶ መወዘክር ድረስ እየመጣ መጻሕፍትን ያነብብ ነበር። ከማንበብ ባለፈም ይጽፋል። ነገር ግን የሚጽፈው በክረምት ወራት ብቻ ነው። በበጋ መጻፍ አይፈቀድለትም። አባቱ ከትምህርት ውጭ ያለ ጉዳይ ላይ ጊዜውን እንዲያባክን አይፈልጉም። ክረምት ላይ ባለው ሶስት ወር ግን ለመጻፍ እድል ሲያገኝ በሰፊው ይጽፋል። የ13 አመት ልጅ እያለ የታደሰ ሊበንን ጅብ ነች የተሰኘ አጭር ልቦለድ አነበበ። የታሪኩ አጨራረስ አስገረመኝ ይላል። ከዚያ ደግሞ ሌላው መንገድ የተሰኘ የድርሰት ርዕስ ሲያይ ሌላ አግራሞት ተፈጠረበት። እንዲህ እንዲህ እያለ በአፍላ አእምሮው ላይ የስነጽሑፍ ዘርን እየዘራ መጣ።
በኢትዮጵያ ስነ ጽሁፍ ተከታታዮችና አንባቢዎች ልብ ውስጥ የመሠረት ድንጋይ ያስቀመጠበት አባ ደፋር እና ሌሎች አጫጭር ታሪኮች በኩራዝ አሳታሚ የታተመው በ1977 ነው። በዚህ መድብል ውስጥ አራት ሥራዎችን አዋጥቷል። ድብድብ ፤ እብዱ ሺበሺ ፤ ሺሮኮ እና ሲፊኒክስ። ሜጋ አሳታሚ በ1990 ዓ.ም ባሳተመው ጭጋግና ጠል የአጭር ታሪኮች ስብስብ ዘላን የተባለው ልቦለዱ ታትሟል። እነዚህ ሁለቱ ከሌሎች ደራሲዎች ጋር የታተሙለት ስለሆነ እንደ ወጥ ድርሰት አልተቆጠሩለትም። ስለዚህም የአዳም የመጀመሪያ ወጥ ሥራ ተብሎ የሚነገርለት ማሀሌት የተሰኘው የአጭር ልቦለዶች ስብስብ ነው። ወቅቱም 1981 ነው። በሻማ ቡክስ በ1997 የታተመው ግራጫ ቃጭሎች ደግሞ አዳምን ከታላላቆቹ እና ዝነኞቹ ተርታ ያሰለፈ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም።
በ2001 ሁለት ልዩ ሥራዎችን ይዞ የቀረበው አዳም የአጫጭር ልብወለዶች ስብስብ የሆነው አለንጋና ምስር እና እርስ በርሳቸው በቀጭን የታሪክ ክር የሚገናኙ ልብወለዶችን ያካተተው እቴሜቴ የሎሚ ሽታን ለአንባቢያን አበርክቷል። ይህ የአጻጻፍ ስልቱ ሕጽናዊነት የሚባል ሲሆን በሌሎች መጻሕፍት ውስጥም ተጠቅሞበታል። አዳም በቀጠሉት ሶስት ዓመታት
በየዓመቱ አንዳንድ መጻሕፍትን ለአንባቢ አድርሷል። በ2002 ከሰማይ የወረደ ፍርፍር ፤ በ2003 ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ ፤ በ2004 ደግሞ ህማማትና በገና የተሰኙ መጻሕፍትን ጽፎ ለአንባቢን አድርሷል።
ከሰማይ የወረደ ፍርፍር በተሰኘ መጽሐፉ ድንቅ የፋንታሲ (ፈንጠዝያ) ሥራዎች የተካተቱ ሲሆን በይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ ደግሞ ለመጀመሪያ ጊዜ መቼቱን ከአገር ውጭ በማድረግ የውጭውን ሕይወት በስሱ ዳስሷል። ከሌሎቹ ሥራዎቹ በተለየ መልኩ ስለ አገራችን ፖለቲካ ወጣ ገባ በታዛቢ አይን ትውስታውን አስፍሯል። ህማማትና በገና የአጫጭር ልቦለዶች ስብስብ ሲሆን ለየት ያለ ቅርጽ ያላቸው አንዳንድ ልቦለዶች ተካተውበታል።
በ2007 ዓ.ም መረቅ የተሰኘ መጽሐፍ ያሳተመ ሲሆን ከዚያም በ2008 ዓ.ም በኢትዮጵያ የስነጽሁፍ ታሪክ ባለብዙ ገጹ ነው የሚባለውን የስንብት ቀለማት የተሰኘ መጽሐፍ አሳትሟል። ከሱ በኋላ ደግሞ በ2010 አፍ የተሰኘ መጽሐፍን አሳትሟል።
አዳም ነዋሪነቱ በውጭ አገር ይሁን እንጂ አገሩን በተመለከተ የምናብ ችግር የለበትም። እንዲያውም ከሌሎች ደራሲያን በተለየ የኢትዮጵያውያንን ሁለንተናዊ ገጽታ በድርሰቱ ውስጥ እስከ ጥቃቅኗ ቅንጣት ድረስ ወርዶ በዝርዝር ይተነትናል። በአንድ ወቅት ሀልዮ ከተባለ መጽሔት ጋር በነበረው ቆይታ ይህን ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል። ‹‹ከአገርህ ስትወጣ ራስህን ባዶ አድርገህ አይደለም የምትወጣው ፤ሁሉን ነገር ትውስታህ ውስጥ ትይዛለህ››
በስነጽሑፍ ሥራዎቹ ውስጥ ኅብረተሰቡን የማስተማር ዓላማ ይዞ ይጽፍ እንደሆነ ተጠይቆ በሰጠው መልስም ‹‹ብዙ ጊዜ ከማየው ተነስቼ ነው የምጽፈው። ግን ለመጻፍ ስነሳ ተዋረድ ይዤ አልነሳም ፤ ለጥ ያለ ሜዳ ይዤ ነው የምነሳው። ሁሉም ነገር እኩል ነው ከሚለው እነሳለሁ።እቃም ይሁን ሰው ፤ ሹምም ይሁን ባሪያ ፤ ምንም ይሁን ምን። ከዚያ ለጥ ካለ ሜዳ ላይ አንድ ገጽ ባህርይ እወስዳለሁ ፤ እንደ ነቁጥ አይነት። ቀጥሎ ያ ራሱ የሚጠራልህ ነገር አለ ፤ አንድ ግለሰብ አንድ ሰው ብቻ አይደለም ፤ ከግለሰቡ የሚወጡ ብዙ ተወንጫፊ መስመሮች (ቬክተሮች) አሉ። ለምሳሌ አንድ ሕጻን መረጥክ። ሕጻኑ ያለቅሳል።
ለምን ያለቅሳል ; ከረሜላ ፈልጎ.. እና እኔ ማደርገው ምንድን ነው ፤ ከአማራጮቹ መሐከል የምፈልገው ገጸ ባህሪ መምረጥ ፤ ከገጸ ባህሪው የሚወጡ መስመሮችን መከተል ፤ የሚያልቅበትን ቦታ መወሰን ነው። የትረካ ቅርጹን ነው እኔ የምፈጥረው። እንጂ በውስጡ ሊነሱ የሚችሉ ግብረገባዊ እና ሌሎች ነገሮችን እኔ የምፈጥራቸው አይደሉም ፤ ዓለም የሚሰጠኝ ነው። እኔ ኅብረተሰቡ ውስጥ የምገኝ ቢሆንም በምጽፍ ጊዜ ግን ራሴን ነጥዬ ገለል ብዬ ለመመልከት እሞክራለሁ። እንዲህ ብቻ ከሆንኩ ግን ከመግለጽ በላይ ላልሄድ እችላለሁ ፤ ምክንያቱም ላይኛው ገጽታን ብቻ በማየት ልወሰን ነው።
ስለዚህ ወደ ሁለተኛው ደረጃ እሸጋገራለሁ። ይህም ምንድን ነው ፤ ገለልተኛ ታዛቢነቴን በመጣረስ ወደ ገጸ ባህርዩ ውስጥ ለመዝለቅ እሞክራለሁ። ተዋንያን ሜተድ አክቲንግ እንደሚሉት። ብዙ ጊዜ በአንደኛ መደብ (እኔ እያለ በሚተርክ ገጸ ባህርይ) ምተርከው በዚህ ምክንያት ነው። ውስጡ ገብቼ ያ ገጸ ባህርይ ምን ሊሆን እንደሚችል ለመገመት እሞክራለሁ። መገመት ማለት ምናብ ሊሆን ይችላል። መገመት ማለት በወሰድኩት ገጸ ባህርይ አማካኝነት የማያቸውን ነገሮች ማስቀመጥ ሊሆን ይችላል። ስለዚህ ሁለት ነገሮች ነው የማደርገው። በአንድ በኩል እውነታውን ከውጭ ሆኜ መመልከት ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ወደ ገጸ ባህሪው ዘልቄ የሱን ሰሜት መዘርገፍ።››
የመጀመሪያ ዲግሪውን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በጂኦግራፊ ፤ ሁለተኛ ዲግሪውን ደግሞ ከኔዘርላንድ ኢንስቲቲዩት ኦፍ አርዝ ሳይንስ ያገኘው አዳም ነዋሪነቱ በካናዳዋ ኦታዋ ከተማ ነው። አብዛኛውን የሥራ ቀኑን በማንበብ በመጻፍ እና በመተኛት የሚሳልፈው አዳም በአንድ ጊዜ ሁለት ወይም ሦሥት መጻሕፍትን እንደሚጽፍም ይናገራል።
አቤል ገብረኪዳን
አዲስ ዘመን ጥር 1 / 2014