የተዋጣለት ተዋናይ ነው፡፡ በኮሜዲ ፊልም ዘውግ ተወዳጅ ከሆኑ ተዋንያን ከፊተኞቹ ይሰለፋል፡፡ ገና በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ሲል በአስቂኝ ምግባርና ንግግሩ ብዙዎች በፈገግታ ይቀበሉታል፡፡ በትወናው ገፀባህሪውን መስሎ በብቃት የሚተውነውን ያህል በእውኑ ዓለም ከሰዎች ጋር በቀላሉ መግባባት የሚችልና በስብዕናውም ተሞጋሽ የሆነ አመለ ሸጋ ነው፡፡
ሲተውን ተግባርና ንግግሩ በትኩረት እንዲ መለከቱት ይጋብዛል፡፡ የተሰጠውን ገፀ ባህሪ መስሎ ሳይሆን ሆኖ ስለሚጫወት የፊልም አፍቃሪያን በስራው ያደንቁታል፡፡ በበዙ ስራዎቹ ወጥ የሆነ አቋም በማሳየቱና በማይዋዥቅ ክህሎቱ እንዲሁም ድንቅ በሆነው የትወና ችሎታው ያየው ሁሉ ይደመማል፡፡ ራሱን ካወቀ ጀምሮ ኪነጥበብ መኖሪያዬ በሆነ ትወናን ስራዬ ባደረኩት ብሎ ተመኘ፡፡
ልጅ ሆኖ የተመኘው ላይ ለመድረስ ሳይታክት ለፍቷል፤ ዕድለኛ ሆነናም ተሳካለት፡፡ በእርግጥ ጥቂት እድለኞች ልጅ ሆነው መሆን የተመኙት እንደ ዕድል ይሳካላቸዋል፡፡ ጥቂቶች ደግሞ በጥረትና በልፋት ለመሆን የሚፈልጉት የልጅነት ምኞትና መሻታቸው ላይ ለመድረስ እልህ አስጨራሽ ትግል ያደርጋሉ፡፡ እርሱም ልጅ ሆኖ አርቲስት ሆኖ መገኘት እጅጉን ይፈልግ ነበርና ያለመታከት በብዙ ጥረትና ልፋት ዛሬ ላይ አሳክቶት በፊልም አፍቃሪያን ዘንድ ታዋቂና ዝነኛ መሆን ችሏል፡፡
ገና የ32 ዓመት ወጣት ነው፡፡ ከ40 በላይ ፌልሞችን በብቃት ተውኗል፡፡ ቁጥራቸው በበዙ ተከታታይ ድራማዎች ላይ ተውኗል፡፡ ከፊልም ትወና በተጨማሪም ከ5 በላይ የሆኑ የራሱ ፊልሞች ፅሁፍና ዝግጅት ላይም የእሱን አሻራ አሳርፏል፡፡ አሁንም አገራዊ ታሪክ ላይ ያተኮሩ የፊልም ስራዎች እያዘጋጀ ነው፡፡ በስምንተኛው የኢትዮጵያ ፊልም ፌስቲቫል ላይ በዓመቱ ምርጥ ረዳት ተዋናይ ዘርፍ አሸናፊና ተሸላሚም ነበር፤ ተዋናይ ቴዎድሮስ ክፍሌ(ጭንቅሎ)፡፡
አዲስ አበባ አውቶቡስ ተራ አካባቢ ተወልዶ ያደገበት ሰፈር ነው፡፡ ከልጅነቱ ጀምሮ ቤተእምነት አካባቢ አይጠፋም ነበርና አካባቢው በሚገኘው ቅዱስ ራጉኤል ቤተክርሲቲያን የሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ በመዘምራንነት አገልግሏል፡፡በዚያ ቆይታው በሰንበት ትምህርት ቤቱ ውስጥ በትያትርና በመዝሙር ከፍ ያለ ተሳትፎም ነበረው፡፡ እዚያ ነው የትወና ሀሁን የጀመረው፡፡ በእርግጥም እዚያ መንፈሳዊ ስራዎች ላይ በማተኮር ነበር የተለያዩ ስራዎችን ይሰራ የነበረው፡፡
የትወና ሀሁ
እንደ ብዙዎች ሁሉ ለአርቲስት ቴዎድሮስም የትወና ስራ መነሻና ራስን መፈተሻ ቦታው ትምህርት ቤት ነበር። በእርግጥ ከትምህርት ቤትም በተጨማሪ በዕምነት ቦታዎች ላይ ማዘውተሩ እዚያም ተሳታፊ በመሆኑ ሌላ ራሱን መፈለጊያ ምቹ መስክ ሆነለት፡፡
አበበች ጎበና ህፃናት ማሳደጊያ ትምህርት ቤት፣ሜይደይና ወይዘሮ ቀለም ወርቅና መድኃኒዓለም ትምህርት ቤቶች የቀለም ትምህርት የተከታተለባቸው ትምህርት ቤቶቹ፣ የትወና ሀሁ የተማረባቸው እንዲሁም ወደ ኪነ ጥበቡ መቃረቢያ ይሆኑት ዘንድ በትያትርና ድራማ ክበባት በመሳተፍ ችሎታውን ያሳደገባቸው ናቸው፡፡ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ ሰባትና በተማረባቸው ትምህርት ቤቶች ውስጥ በቴአትር ክበባት ውስጥ ጎልቶ የሚታይ እንቅስቀሴ ነበረው፡፡
በትምህርት ቤቱ በሚቀርቡ ልዩ ልዩ የመድረክና የክፍል ውስጥ ትዕይንቶች በሚያሳየው የትወና ብቃት በተማሪዎችና በክፍል ጓደኞቹ ጉብዝናው ተደጋግሞ ይነገረው ነበር፡፡ በዚህም ተበራትቶ ወደ ስራው በጥልቀት ገብቶ የልጅነት ህልሙን እውን ለማድረግ ጥረት ማድረግ ጀመረ፡፡ ከሌሎች ጓደኞቹ ጋር በመሆን ያለመታከት በመሳተፍ የትወና ችሎታውን ለማሳደግ አዳዲስ ነገሮችን ለመሞከር ሁሌም ጥረት ያደርግ ነበር። የቤተሰቡ አባል ወንድሙ አለማየሁ ክፍሌ ከሱ ቀድሞ ወደ ኪነጥበቡ የተቃረበ ነው፤ በተለያዩ መድረኮች ላይ ይመለከተውም ነበርና አለማየሁ ለትወና ፍላጎት ያጫረበት የመጀመሪያ ሰው መሆኑን ይናገራል። አለማየሁ በወቅቱ በማዘጋጃ ቤትና በተለያዩ ቦታዎች በሚቀርቡ ትያትሮች ላይ በመሳተፍ ድንቅ ችሎታው ተመስክሮለታል፤ እሱም የወንድሙን አርዓያ በመከተል እሱን እያየ ልምምድ ያደርግ እንደነበር ይናገራል፡፡
ከሕዝብ ጋር ትውውቅ እውቅናና ሽልማት
በእርግጥ በአካባቢውና በትምህርት ቤቶች አካባቢ በትወና ችሎታው ብዙዎች ቢያደንቁትም፣ ወደ መላው ህዝብ መቅረብ የቻለበት የመጀመሪያው ፊልሙ “ወይ አዲስ አበባ” የተሰኘው ፊልም ነው፤ በዚህ ፊልም ላይ በፅሁፍና ትወና ተሳትፏል፡፡ በዚህ ስራው ባሳየው የትወና ብቃት እጅግ ተወዳጅነትንና አውቅናን አተረፈ፡፡ የፊልሙን ፅሁፍ ያዘጋጀው ራሱ ስለነበር በድርሰትም የተዋጣለት መሆኑን አስመሰከረ፡፡
እስካሁን ከአርባ በሚበልጡ ወጥ ፊልሞችና ቁጥራቸው በበዛ ተከታታይ ድራማዎች እና ሲትኮም ላይ ተውኗል፡፡ ከስራዎቹ መካከልም፡- ሌባና ፖሊስ፣ አይገባንም፣ ሚሽኑ፣ ሄሎ ኢትዮጵያ፣ ምን አለበት፣ ቀበሮ፣አጣምራለች፣ ተወዳጅ፣ የባለስልጣን ልጅ፣ የተቀበረው፣ ባንድ ቀን እና የመሳሰሉት ሲሆኑ ከተከታታይ ድራማዎቹ መካከል፡- አለሜ፣ወላፈንና የተቀበረው ተጠቃሾቹና አርቲስት ቴዎድሮስ ድንቅ የትወና ብቃቱን ያሳየባቸው ስራዎቹ ናቸው፡፡
በስራዎቹ ከተለያዩ አካላት ከልጅነቱ ጀምሮ እውቅናን ሲቸሩት በዝናውም ጎሽ ሲሉት የቆየው ቴዎድሮስ “አጣምራለች” በተሰኘ ፊልም ላይ ባሳየው ድንቅ ብቃት የኢትዮጵያ የአመቱ ምርጥ ረዳት ተዋናይ በሚለው ዘርፍ በስምንተኛው የኢትዮጵያ ፊልም ፌስቲቫል ላይ አሸናፊ በመሆንም ሽልማት ተበርክቶለታል፡፡ በወቅቱ ከሚወደውና እጅጉን ከሚያደንቀው የፊልምና ቲያትር ባለሙያውና ተዋናይ አለማየሁ ታደሰ ሽልማት መቀበሉ ደግሞ ልዩ ስሜት እንደፈጠረበትም ይናገራል፡፡
የመጀመሪያው ክፍያ
የመጀመሪያ ስራውን ፈፅሞ አይረሳውም፤ እጅግ በጣም ጥቂት የቃላት ልውውጥ ያለበትና አንድ ‹‹ሲን›› ወይም ከፊልሙ ትዕይንት አንድ ክፍል ላይ አንዴ ብቻ ብቅ ብሎ ወዲያው የጠፋበት ነው፡፡ ለዚህ ትወናው 50 ብር ብቻ ተከፍሎት እንደነበረም ያስታውሳል፡፡ አሁን ላይ የተለያዩ በፊልም ስራዎች ላይ በስፋት እየተሳተፈ ያለው አርቲስት ቴዎድሮስ፣ በኤሌክትሪሲቲ የተመረቀ ሲሆን፣ ድንቅ ሙያተኛም ነው፡፡
የዕረፍት ጊዜ
የኪነጥበብ ስራዎች በሚቀርቡባቸው ቦታዎች መገኘት እጅጉን ይወዳል፡፡ በተለይ ቴአትር ቤት ተገኝቶ መድረክ ላይ የሚታየውን ትዕይንት መመልከት ያስደስተዋል፡፡ ማህበራዊ ህይወት እና አብሮ መኖርና መጋራት እጅጉን በሰፈነበትና ክፉ ጊዜን ተጋግዞ ማለፍ ልማድ በሆነበት አውቶቡስ ተራ አካባቢ የተወለደው አርቲስት ቴዎድሮስ፣ በእረፍት ጊዜው ከሚዋዳቸው ጓደኞቹ ጋር መጨዋወት መወያየትና የተሻለ ጊዜ ማሳለፍ እጅጉን ደስታ ያላብሰዋል፡፡
በማህበራዊ ጉዳዮች ላይ በንቃት ይሳተፋል፡፡ ከሰዎች ጋር መልካም የሆነ ግንኙነት መፍጠርና ደስተኛ ለማድረግ መሞከር ጥሩ የሆነ ጊዜን አብሮ ማሳለፍንም ይመርጣል፡፡ በተለይ አገራዊ ታሪክ የተላበሱና ልቦለድ ታሪክ ያላቸው መፅሐፍት ማንበብ በእረፍት ጊዜው የሚያዘወትረው ተግባሩ ነው፡፡ ፊልሞችን ማየት እጅጉን ይወዳል፡፡ በትወናው የሚያዘወትራቸው የኮሜዲ ዘውግ ያላቸው ፊልሞችን ሳይሆን፣ ትራጄዲና ድራማ ይዘት ያላቸው የፊልም አይነቶች ማየት ያስደስተዋል፡፡
አገራዊ ታሪክን የሚያስተዋውቁ የማህበረሰቡ ወግና ባህል የሚያንጸባርቁ ስራዎችን በማዘጋጀት ላይ የሚገኘው አርቲስት ቴዎድሮስ በቅርቡ የሚወጡ ስራዎች እንዳሉትም ይገልፃል፡፡ ወደፊት በፊልሙ ዘርፍ የራሱን አዎንታዊ ሚና ለመወጣት እንደሚጥርና ከሙያ አጋሮቹ ጋር በመስራት ላይ እንደሆነም ያስረዳል፡፡
የኢትዮጵያ ፊልም በአርቲስት ቴዎድሮስ አይን
ከተሰራበትና ትኩረት ከተሰጠው ለአገርም ለኪነጥበቡም ዕድገት ምቹ ሁኔታና ዕድል መኖሩን የሚናገረው አርቲስት ቴዎድሮስ፤አሁን ላይ የፊልም ዘር እጅጉን መቀዛቀዙን ያስረዳል፡፡ በእርግጥ ከኮሮና በፊት አንዳንድ የመዳከም ምልክቶች ያሳይ የነበረው የፊልም ኢንዱስትሪው ዘርፍ በኮሮና ምክንያት እጅጉን ተጎድቷል ይላል፡፡
ተመልካቹም ቀስ በቀስ ከሲኒማ እየራቀ ነው የሚለው ቴዎድሮስ፣ ዘርፉ እንዲነቃቃ እና በተፈለገ መልኩ የተሻለ እድገት ማስመዝገብ እንዲቻል ባለሙያዎች ጠንካራ ስራዎች ሊሰሩ እንደሚገባም ይመክራል፡፡ ተመሳሳይ ታሪኮች መበራከት፣ ለዘርፉ ተገቢው ድጋፍ አለመደረግ፣ በዘርፉ የሰለጠነና ብቁ የሆነ ሙያተኛ አለመኖር ዋና ዋና የሲኒማው ኢንዱስትሪ መቀዛቀዝ ምክንያት ብሎ የጠቀሳቸው ናቸው፡፡
ለሙያው ዕድገት የዓላማ ፅናትና ተደጋጋሚ ሙከራ ማድረግ ወሳኝ መሆኑንም ያስረዳል፡፡ የፊልም ባለሙያዎችና ደራሲያን በፊልምነት የሚያቀርቡ ታሪኮች ተመሳሳይነት እንዳይኖራቸው መጠንቀቅ ይገባቸዋል፡፡ ኢትዮጵያን በምታህል ትልቅ ታሪክና ባህል ባላት አገር ላይ ታሪኮችን መግለፅና ማሳየት ሊቀጥል ይገባል፡፡ ታሪካችንን በመፃፍና በማስተዋወቅ አዳዲስ ነገር ማሳየት ከፊልም ባለሙያዎች ይጠበቃል ሲል ያመለክታል፡፡
ለኢትዮጵያውያን መልዕክት
ወጣቱ ተዋናይ ደራሲ ቴዎድሮስ ክፍሌ ለኢትዮጵያዊያን መልዕክት ካለው ያስተላልፍ ዘንድ ጋበዝነው፡፡ “እኔ የማውቃት ኢትዮጵያ ብሄር፣ ዘርና ሃይማኖት ሳይለይ በአንድነት የሚኖርባት ናት፡፡ አሁን ላይ አንድነት የሚያለዝቡ አብሮነትን የሚፃረሩ ሃሳቦችና ሰዎች በድፍረት እየቀረቡ ናቸው፡፡ ይህ ፈፅሞ እኛን የማይገልፅና ሁላችንም ልናወግዘው የሚገባ ነው፡፡ እኛ ከጥንት ጀምሮ በፍቅር የኖርንበት አንድነት ነው የሚያምርብን ብሏል፡፡
ከአባቶቻችን የተቀበልናት አንዲት ኢትዮጵያ አንድነቷም ተቀብለን እኛም ለሚቀጥለው ትውልድ የማስተላለፍ አደራ አለብን፡፡ በዘርና በሃይማኖት ያልተለያየች በአንድነቷ የፀናች አገር እንድትኖረን እንትጋ፡፡ ለአገራችን ሰላም ሁላችን የበኩላችን እንወጣ። አገር ስትኖር ነው ሁሉንም ነገር ማድረግም መሆንም የሚያስደስተው፡፡ የአገራችንን አንድነት ለማስጠበቅና አብሮነታችንን ለማጠንከር እንትጋ፡፡ በአንድነት ጥላ ፍቅር የምንኖርባትና ሰላሟ የተጠበቀ ኢትዮጵያ ማየት እናፍቃለሁ ብሏል፡፡
ተገኝ ብሩ
አዲስ ዘመን ጥቅምት 21 ቀን 2014 ዓ.ም