ጠላትን እንዳመጣጡ ስለመመለስ ኢትዮጵያውያን አሳምረው ያውቃሉ። ይህ ብቻም አይደለም፤ አመጣጡን አይተው መወሰን ላይም ችግር የለባቸውም። ይህ ባይሆን ኖሮ ታሪክ መዝግቦ ያስቀመጣቸው በርካታ የጦር ሜዳ ድሎች ባለቤት ባልሆኑ ነበር።
ይህን የኢትዮጵያውያንን እና የኢትዮጵያዊነትን ልክ አሁንም ለጠላቶቻችን ማሳወቅ ይገባል። ይታወቃል ተብሎ የሚተው ነገር ሊኖርም አይገባም። ከማሳወቅ ለአፍታም ቢሆን መቦዘን አይገባም። ይህን አለማድረግ ብዙ ዋጋ ያስከፍላል። ቀለል ተደርጎ የሚታይ ነገር ጨርሶ ሊኖር አይገባም። ይህን ሁሉ ተገንዝቦ አለመስራት ትልቅ ስህተት ነው፤ብዙ ዋጋም ያስከፍላል።
ከምንም ከምንም በላይ ደግሞ በተመሳሳይ መንገድ ስለመጠቃት መስማት በእጅጉ ያማል። በተቀየረ መንገድ መታለል ሊያጋጥም ይችላል። የትኛውም አይነት ተለዋዋጭ ሁኔታ ቢያጋጥም እየተለዋወጡ ነገርን እንዳመጣጡ መመለስ እንጂ በተመሳሳይ ዱላ ሁሌም መመታት የዋህነት ነው። ኢትዮጵያውያን በአንድ ቡድን ተመሳሳይ ዱላ እየተመቱ ናቸው።
ይሄን ሳነሳ ስለአሸባሪው ህወሓት ላወራ መሆኑን ትረዱኛላችሁ፤ አዎን ቡድኑ ኢትዮጵያውያንን በተመሳሳይ ዱላ እየመታ ነው። ይህ ዱላ ከህግ ማስከበር በፊት ሰሜን እዝን አላላውስ ብሎት ነበር። ሀጢያታቸው አላስተኛ አላስቀምጥ ያላቸው የአሸባሪው ህወሓት መሪዎች ሰሜን እዝ በተንቀሳቀሰ ቁጥር ሊይዘን ነው የሚል ስጋት ነበረባቸው። በዚህ የተነሳም ሰራዊቱ እንቅስቃሴ ሲያደርግ ህጻናትን ሴቶችን፣ አዛውንቶችንና ሌሎች ንጹሃን ዜጎችን ጎዳና ላይ እያስተኛ እንቅስቃሴውን ያስተጓጉል ነበር። የሚያስበውን እስከሚያሳካ ድረስ ትታችሁን አትውጡ አለእናንተ ማን አለን ይሉ ነበር።
ይሄ ህዝብን እንደ መሳሪያ መጠቀም የተጀመረውም ያኔ ይመስለኛል፤በኛ ሀገር። አዎን ይህ መንገድ ለአሸባሪው ቡድን እንደ ከባድ መሳሪያ (እንደ ሚሳዬል ብንለውስ) አገልግሎታል። ቡድኑ ሰራዊቱ ለህዝብ ያለውን እምነት ለወንጀል ድርጊቱ ተጠቅሞበታል። ሰራዊቱ እንቅስቃሴውን ባስተጓገለው ኃይል ላይ ተመጣጣኝ እርምጃ ሊወስድ ሲችል ህዝብ ይጎዳል በሚል እምነት እንደ ፈቃዳቸው አድሯል።
በዚህ ሰራዊቱን ሲፈታተን የቆየው ቡድኑ፣ በኋላም ሰራዊቱ ላይ ክህደት ፈጽሞ ታሪክ ይቅር የማይለው ድርጊት ልክ የዛሬ ዓመት አካባቢ በሰሜን እዝ ላይ ፈጽሟል። አይጥ ሞቷን ስትሻ የድመት አፍንጫ ታሸታለች እንደሚባለው ይህ ድርጊቱ ያስቆጣው የሀገር መከላከያ ሰራዊት በሶስት ሳምንት ውስጥ ያደረገውን ያጣውን አሸባሪ ቡድን ከተኮፈሰበት ስልጣን ወርዶ ዋሻ ውስጥ እፍ ብሎ እንዲቀመጥ አርጎታል።
መከላከያን እንደማይችለው እየተገነዘበ የመጣው ቡድኑ፣ ሌላ መሳሪያ ማፈላለግ ውስጥ ገባ። ይህ መሳሪያውም ህዝቡን ከፊት ለፊት አርጎ ከኋላ መከተል ሆነ። በእዚህም አያሌ ታዳጊ ህጻናትን፣ ነፍሰ ጡሮችን፣ ቄሶችን ፣ አካል ጉዳተኞችን፣ ወዘተ ጦር ግንባር ላይ ለእዚያውም ከፊት ለፊት አሰለፋቸው። ይህን አይነቱን የጦርነት አሰላለፍ ነጮቹ “ሂዩማን ዌቭ” (ህዝባዊ ማዕበል እንደማለት ነው) ይሉታል።
እንደዚያ እያረገ መከላከያን በእጅጉ ተፈታተነ። መከላከያስ እነዚህን ንጹሃን እንዴት ብሎ ይምታ? ሊከተል የሚችለውን ችግር በማሰብ ራሱን መስዋእት እስከ ማድረግ ደረሰ። መንግሥት ሁኔታው አሳሳቢ መሆኑን በመገንዘብ የትግራይ ህዝብም የማሰቢያ ጊዜ አንዲያገኝ እና ሰብዓዊነትን በማስቀደም የተናጠል የተኩስ አቁም በማድረግ ትግራይን ለቆ ወጣ።
ቡድኑ ይህን የውጊያ ዘይቤውን በአማራና አፋር ክልሎች ላይ በፈጸመው ወረራ ላይም ተጠቅሞበታል፤ እየተጠቀመበትም ነው። ህጻናትን ፣ሴቶችን አዛውንቶችን፣ አካል ጉዳተኞችን ጭምር በጦርነቱ በከፍተኛ መጠን እያሰለፈ ነው። እጅግ በርካታ ህዝብ በከባድ መኪኖች እያመጣ ግንባር ላይ በመዘርገፍ ጦርነቱን ተያይዞታል።
ሰው የሚንቅ ‹‹ሰው ጤፉ›› ነው የሚባለው ፤ የገዛ ህዝቡን ናቅ ያረገው አሸባሪው ህወሓት ግን ህዝብ ጤፉ ቢባል ነው የሚሻለው። ህዝብ ባይንቅ ህጻናትን ነፍሰ ጡሮችን አዛውንቶችን አካል ጉዳተኞችን አንዴት በጦር ሜዳ ከዚያውም ከፊት ለፊት ያሰልፋል? የህዝቡ ማለቅ ለእሱ ጉዳዩ አይደለም ፤የቡድኑ መሪዎች ቆሞ መሄድ ነው ጉዳዩ፤ ኢትዮጵያን ለማንበርከክ እንዲያመቻቸው ውክልና ከሰጡት ምእራባውያን የበላው ቀብድና ምእራባውያኑ ናቸው ጉዳዮቹ።
በእዚህ አይነት መንገድ አያሌ ንጹኃን ኢትዮጵያውያንን ጨፍጭፏል፤ ሀብት ንብረታቸውን ዘርፎ ወደ ትግራይ አግዟል፤ የሀገር ሉአላዊነትን ደፍሯል፤ አስደፍሯል። ከአንድ ሚሊዮን በላይ የአማራና የአፋር ክልል ህዝብን አፈናቅሏል። ይህን ተከትሎ እንደ ሀገር እየተፈጠረ ያለው ቀውስም ሊጠቀስ ይገባል።
ተቆጣጥሯቸው በነበሩ የአማራና አፋር ክልሎች አያሌ ሰዎችን ቢጨፈጭፍም፣ ሀብት ንብረታቸውን ቢዘርፈና ቢያወድምም ህዝቡ ቡድኑን ከመሸሽ ይልቅ፤ ከመከላከያና ሌሎች ደህንነት ኃይሎች ጋር በመሆን ቡድኑን በመጋፈጥ ተበቅሎታል። የተሰውት ንጹሃንም ደማቸው ደመ ከልብ ሆኖ አልቀረም ፤ ከሰሜን ወሎ በስተቀር በአፋር ክልልና ሰሜን ጎንደር የነበረው የቡድኑ ኃይል እንዳይወጣ ተደርጎ ተቀጥቅጧል።
ቡድኑን በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን ላይ አሁንም ከፍተኛ ጭፍጨፋ እና ግፍ እየፈጸመ ይገኛል፤ ይባስ ብሎም ወረራውን ወደ ደቡብ ወሎ ዞን ለማስፋት እየሞከረ ነው። ይህንንም ዞን ለመቆጣጠር እንዳለፉት ጊዜያት ሁሉ ቁጥር ስፍር የሌላቸውን ሲቪሎች ይዞ መምጣቱን መረጃዎች ያመለክታሉ።
የደሴ ህዝብ ከመከላከያና ሌሎች የጸጥታ ኃይሎች ጋር በመሆን ቡድኑን ለመፋለም ወደ ግንባር ሄዷል። ፊትም ሰርጎ ገቦችን በመቆጣጠር ላይ ተጠምዶ የቆየው ህዝቡ ፣ አሁን ደግሞ ከፍተኛ ተጋድሎ በሚጠይቀው የጦር ሜዳ ውሎ ላይ ተሰማርቷል። እሾህን በእሾህ እንዲሉ እንደ ህዝብ ግር ብሎ እየመጣ ያለውን ቡድን የደሴ ነዋሪ ለመፋለም ወስኖ ግንባር መገኘቱ ትክክል ነው።
የሀገር መከላከያ ሰራዊትም ህዝባዊ ወገንተኝነቱ እንዳለ ሆኖ በእንዲህ አይነት መልኩ የሚመጣን ህዝባዊነት መርምሮ አስቸኳይ እርምጃ መውሰድ ይኖርበታል። ህዝብና ሀገር ሊያጠፋ የመጣ የትኛውም አሰላለፍ በምንም አይነት መልኩ ይቅርታ ሊደረግለት አይገባም። ቡድኑ በገፍ እያጋዘ የሚያራግፋቸውን ሰዎች ወታደሮቼ ብሎ ነው ያሰለፋቸው። በእዚህ አይነት አሰላለፍ እየደረሰ ያለው ጥፋት ከፍተኛ መሆኑ ታውቋል። እሱ ፊት ለፊት ያሰለፈውን ህዝብ ከጥይት መታደግ ያለበት ራሱ እንጂ የመከላከያ ሰራዊት አይመስለኝም።
መልኩ ምንም አይነት ይሁን ምንም ሊወጋ የመጣን ጠላት መዋጋት ወቅቱ የሚጠይቀው አብይ ተግባር ነው። ህዝብ ትጥቄ ነው ያለውን ጠላት ይህን ትጥቁን ማስፋታት ከተቻለ ማስፋታት፣ ካልተቻለ ሀገርን ከጥቃቱ መታደግ ጥያቄ ውስጥ አይገባም። ቆም ተብሎ የሚታሰብ ጉዳይም አይመስለኝም። ቡድኑ ባሰለፋቸው ሲቪሎችና ታጣቂዎቹ ህዝብ እያለቀ፣ እየተፈናቀለ፣ እየተሰቃየ ነው። የህዝብና የመንግሥት ንብረት እየወደመ እየተዘረፈ ነው።
አሸባሪው ህብረተሰቡን ለወረራ እያሰለፈ መሆኑም ኢትዮጵያን በተደጋጋሚ ዋጋ አስከፍሏታል፤ እያስከፈላት ነው። ሞኝ አውሬ ነው አሉ በአንድ ጉድጓድ ውስጥ ሁለቴ የሚወጋው። ይህ ቡድን ሞኝ አውሬ እያረገን ነው። ንጹሃን ዜጎች በጦርነት እያሰለፈ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያንን በተደጋጋሚ ክፉኛ ጎድቷል። ይህ ጭፍጨፋና ግፍ ፣ ንብረት ዘረፋና ማውደም በጭራሽ መደገም የለበትም። ሀገር አለመረጋጋት ውስጥ መቆየት አይኖርባትም።
እኔ እንደሚገባኝ ቡድኑ ሰራዊቱ ህዝብ አይመታም የሚል ድምዳሜ ላይ ከደረሰ ቆይቷል። በጦርነቱ የሚያሰልፈውን የህዝብ ማእበል የተመለከተ በየአካባቢው የሚገኝ ህዝብም አይዋጋንም፤ እንዲያውም ይሸሻል የሚል ግንዛቤም ይዟል። በዚህ የህወሓት ስትራቴጂ መበለጣችን ሊያበቃ ይገባል። አንዴ ሁለቴ በዚህ ተጠቅተናል፤ አሁንም መጠቃት አይኖርብንም፤ ግን እየተጠቃን ነው። ጠላትን እንዳመጣጡ መመለስ ላይ የሚቀረን ያለ ይመስለኛል። ሞኝ አውሬ ተደርገናላ፤ ይህ ሁኔታ ሊያበቃ ይገባል።
ዘካርያስ ዶቢ
አዲስ ዘመን ጥቅምት 13/2014