ለምለም መንግሥቱ
ወይዘሮ ማርታ በቀለና ሁለት ልጆቻቸው ለገና በዓል ከሚያዘጋጁት ምግብና መጠጥ በተጨማሪ ቤታቸውን ሥለሚያስውበትና ሥለሚገዙት ነገር ይመካከራሉ። ከሚገዙት የዕቃ ዝርዝር ውስጥ ለበዓሉ ማድመቂያ የገና ዛፍ(ክሪስመስ ትሪ)መቅረቱን ልጆቹ ያስታውሳሉ።
እናት ደግሞ ኢየሱስ ክርስቶስ በከብቶች ማደሪያ በረት ውስጥ መወለዱን ተምሳሌት የሆነውን ከእንጨት ውጤት ተዘጋጅቶ በገበያ ላይ በመሸጥ ላይ ያለው ቢሆንና ለለውጥም እሱን ቢገዛ እንደሚሻል ሀሳብ ያቀርባሉ።ወደ አንድ ሀሳብ ለመምጣት ገና በምክክር ላይ እያሉ በመካከላቸው ጣልቃ ገብቼ ይሄን ያህል ያስጨነቃቸው ነገር ኢትዮጵያዊ ባህል እንዳልሆነ ላስታውሳቸው ሞከርኩ። እናትና ልጆች በአንድ ቃል ‹‹ምን ችግር አለው ቤት ያደምቃል››አሉኝ።ሀሳቤ ተቀባይነት አለማግኘቱ ብዙም አልገረመኝም።
እንደ እናትና ልጆቹ ሁሉ በአዲስ አበባ ከተማ በልደት በዓል በመብራትና በኳስ ጌጣጌጥ ያሸበረቀ አርትፊሻል የገና ዛፍ በብዙ ሰዎች ቤት የተለመደ ነው።ሆቴል ቤቶች፣የተለያዩ ንግድ ቤቶች በተመሳሳይ ከበዓሉ መዳረሻ ጀምሮ ለቀናት በየበራፎቻቸው ደጃፍ ላይ ያደርጋሉ።በዓሉን ያደምቃል ከማለት ውጭ ለምን እንደሚጠቀሙ በትክክል የሚያስረዳ ሰው አያገኙም።
ትላልቅ ሆቴል ቤቶች እንኳን የውጭ ሀገር ዜጎችን ሥለሚያስተናግዱ የአካባቢያቸው ትውስታ እንዲኖራቸው ለማድረግ ነው ብለን ልንቀበል እንችላለን። ሌላው ማህበረሰብ ባህሉ ያልሆነውን ነገር እንደራሱ አድርጎ ያን ያህል ትኩረት መሥጠቱ የገና በዓል በመጣ ቁጥር እያነጋገረን ይገኛል።ግንዛቤው ዳብሮ ወደማንነታቸው እስኪመለሱ እኛም በየአመቱ ስለጉዳዩ ማንሳታችን አይቀርም።
በዚህ ወቅት ለገና ተብሎ ጥቅም ላይ ከሚውሉት ዛፎች አግባብ ባልሆነ መንገድ በመቁረጥ ጥድ ለከፍተኛ ጉዳት ይጋልጣል። ዛፉ ለገና እየተባለ በአደባባይ ለገበያ ሲቀርብ እንደነበርም የቅርብ ጊዜ ትውስታችን ነው።አሁን አሁን እንደቀድሞ የተፈጥሮ ጽድ በገበያ ላይ ባይስተዋልም ፍላጎቱ እስካለና የመጠቀሙ ልማድ እስካልቀረ ድረስ ችግሩ ተቀርፏል ወይንም የማይጠቀም ሰው አይኖርም ብሎ ለመገመት ያዳግታል።
በቅርብ በገበያ ላይ እየቀረበ ያለው የእየሱስ ክርሥቶስን በከብቶች ማደሪያ በረት ውስጥ መወለድ ተምሳሌት የሆነውም የተክል አይነት ለሌላ የእንጨት ውጤት አስፈላጊ ከሆነና አካባቢን በመጠበቅም ጠቀሜታ ካለው እንደ ጥድ ዛፍ ሁሉ ከወዲሁ ጉዳት እንዳይደርስበት ትኩረት ሊሰጠው ይገባል።
በደን መመናመን ሳቢያ የአየር ንብረት ለውጥ ሥጋት በሆነበት በዚህ ወቅት ባለው የደን ልማት ላይ መጨመር እንጂ መቀነስ አይመከረም።ኢትዮጵያ የደን ሽፋኗን ለማሳደግ በተለይም ባለፉት ሁለት አመታት በሁለት ዙር በሚሊየን የሚቆጠር የተለያዩ ዝርያ ያላቸው ችግኞች በመትከል ከሌሎች ሀገሮች ሁሉ ሳይቀር በችግኝ ተከላ መርሃግብሩ የተሻለ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ እንደሆነች ተነግሮላታል።ለሶስተኛው መርሃግብርም ጎረቤት ሀገሮችዋን ያካተተ ችግኝ ተከላ ለማካሄድ መዘጋጀቷንም ይፋ አድርጋለች። እንዲህ ያሉ ጥረቶች እያሉ የለማውን ማውደም ተገቢ እንዳልሆነ ብዙዎች እንደሚስማሙ ይታመናል።
ከአካባቢ ጥበቃ ጋር አያይዘው ለማድመቂያ ተብሎ በሚዘጋጀው የገና ዛፍ ዙሪያ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነህይወት መምህርና ተመራማሪ ፕሮፌሰር ሰብስቤ ደምሰው የሚናገሩት ፤እርሳቸው ከልጅነት እስከ እውቀት የሚያሥታውሱት በኢትዮጵያም በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በዓሉ ሲከበር የተለመደው የገና ጨዋታ መሆኑን ነው። አጨዋወቱ፣ ለመጫወቻ የሚውለው በጫፉ ላይ የተቆለመመው አጭር የእንጨት ዱላና የምትከባለለው ሩር የተባለችው ኳስ ልዩ ውበት የሚሰጥ ሲሆን፣ኳሷን በተዘጋጀው ጉድጓድ በዱላው ለመክተት በቡድን ሆነው የሚጫወቱትን ማየት የበለጠ አጓጊ ያደርገዋል። ደግሞም ያስደስታል። ይሄ ጨዋታ ማህበራዊ ትስስር በመፍጠርም ጠንካራ ጎን አለው። ሁሉም ሀገር የራሱ የሆነ የባህል እሴት ቢሆንም የኢትዮጵያ የገና ጨዋታ
ግን ለየት ያለ እንደሆነ ያምናሉ።በቤት ውስጥ የገና ዛፍ ማስቀመጥ የባህሉ ባለቤቶች እንደሆኑት አውሮፓውያኑ ለኢትዮጵያውያን ትርጉም ይሰጣል ብለው አይገምቱም። ደግሞም አንድን ነገር ሲጠቀሙ ለምን እንደሚያደርጉት ምክንያቱን መግለጽ ካልቻሉ ስሜት አይሰጥም። ሥለገና ጨዋታ ግን ታሪካዊ አመጣጡን መናገር ይቻላል ሲሉ ያስረዳሉ።
‹‹የገና ዛፍን የሚጠቀሙት አውሮፓውያኑ ከጨለማ ወደ ብርሃን ወይም ከአሮጌው ወደ አዲሱ ዘመን የሚሸጋገሩበት ጊዜ በመሆኑ አዲስ ቀን መጣልን የፀሐይ ጊዜ ረዘመልን የሚሉበት ጊዜ ስለሆነ ዛፍን በተምሳሌትነት የጠቀማሉ ። በዚህ ወቅት የሚጠቀሙት የዛፍ አይነትም የተለየ ነው›› ሲሉ ይጠቅሳሉ።
ጨዋታው ባህላዊ ይዘቱን እንደጠበቀ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲሸጋገር ባለመደረጉ ህብረተሰቡ በሌላ መጤ ባህል እንዲጠለፍ መንገድ ከፍቷል የሚሉት ፕሮፌሰር ሰብስቤ፤ለጨዋታው ትኩረት የተነፈገው መሆኑ አንዱ ማሳያ ለገና መጫወቻ ተብሎ የተለየ ሜዳ ወይንም ቦታ አለመኖሩ ነው ይላሉ ። የገናን ጨዋታ በዓሉን ጠብቆ ብቻ ከማከናወን ባህሉን እያበለፀጉ መሄድ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል። እንደ ፕሮፌሰር ሰብስቤ ማብራሪያ የገና ዛፍን በበዓል ወቅት መጠቀም ኢትዮጵያዊ ባህል እንዳልሆነ ህብረተሰቡ ይገነዘባል።
ነገር ግን ሊያቆመው አልቻለም።በተለይ አዲስ አበባ ከተማ የተለያዩ ዓለምአቀፍ ድርጅቶች የሚገኙባት ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የባህል መወራረሱ ሊገታ አይችልም። ህብረተሰቡ ሀገር በቀል እጽዋት እንዳይጠቀም ትምህርት እየሰጡ ግን አማራጮችን አብሮ በማስቀመጥ ዛፉ እንዲጠበቅ ማድረግ ያዋጣል።
‹‹በሌላው ዓለም የገናን ዛፍ የሚጠቀሙት አካባቢን በሚያራቁት ደን በመጨፍጨፍ አይደለም። ይልቁንም ዘርፉን ትልቅ ኢንዱስትሪ በማድረግ ዜጎችም በገቢው እንዲጠቀሙ ለገና በዓል ብቻ ታሰቦ የሚጸድቅ ጥድ በመትከልና ለገበያ በማመቻቸት ነው›› የሚሉት ፕሮፌሰር ሰብስቤ ፤አካባቢ ሳይጎዳ፣ ገቢም እየተገኘ፣ ማህበረሰቡም በዓሉን እያከበረ ሁሉንም ተጠቃሚ ያደረገ ሥራ ይሰራል።በኢትዮጵያም ወጣቶች አደራጅቶ፣ለችግኝ መትከያ የሚሆን ቦታ አመቻችቶና ለሥራ መነሻ የሚሆን
የገንዘብና የተለያየ አቅም ፈጥሮ በተመሳሳይ ሁኔታ መጠቀም ከተቻለ ዜጎች የሥራ እድል ያገኛሉ።አካባቢም ይጠበቃል።ዓለም አንድ መንደር ናት።ወይም የግሎባይዜሽን ዘመን በምንልበት በዚህ ወቅት በማስቆም ላይ ብቻ ትኩረት የሚደረግ ከሆነ ገንዘብ ለማግኘት ሲል ደን የሚጨፈጭፍ አጥፊ እንዲፈጠር ማድረግ ነው።በተጨማሪም ሌብነትን ማስፋፋት ነው።እንዲህ ያለው ነገር ውስጥ ከመግባት ከወዲሁ የፌዴራል መንግሥትም ሆነ የክልል አስተዳደሮች በጋራ ተባብረው ኃላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባል።
ጽድን ከመጠቀም ይልቅ የበረት ተምሳሌት ያለው ከእንጨት ውጤት ተሰርቶ እየቀረበ ወዳለው መሸጋገሩንም ፕሮፌሰር ሰብስቤ አይደግፉም።ጥቅም ላይ እየዋለ ያለው ግብዓት መፈተሽ አለበት ይላሉ። እርሳቸው እንዳስረዱት ቀርከሃና ሽመል የሚባሉ የተክል አይነቶች አግባብ ባልሆነ መንገድ ለጉዳት ተዳርገዋል።ተክሎቹ በሰዎች እንክብካቤ ሳይሆን በተፈጥሮ የሚገኙ ናቸው።
የሸምበቆ ተክል በቀላሉ ስለሚያድግ በዚህ ተክል ተዘጋጅቶ ቢቀርብ አይቃወሙም።የሽመል ተክል በቆላማ በተወሰነ አካበቢ የሚለማ በመሆኑ ይህን ጥቂት የሆነ ሀብት መጉዳት ተፈጥሮን ማዛባት ማለት ይሆናል።የቀርከሀ ተክል ደግሞ ቀስ ብሎ የሚያድግና በቀላሉም የሚተካ ባለመሆኑ ትርፉ አካባቢን ማራቆት በመሆኑ ሊታሰብበት ይገባል።
አመራጮችን ማየት በመልካም ጎን የሚወሰድ ቢሆንም ሊያስከትል የሚችለውን ጉዳት አብሮ ማየቱም ተገቢነት አለው።አሁን በገበያ ላይ በመቅረብ ላይ ያለው የበረት ተምሳሌት በሚሰራበት ወቅት ተረፈምርቱ በየአካቢው ተዝረክርኮ ለአካባቢ ጽዳት መጓደል መንሥኤ እየሆነ ይገኛል።የጥራት ደረጃቸውና ለግብአትነት የዋለው ተክልም ለጤና ጉዳት እንደማያስከትል የጤና ማረጋገጫ የለውም።
የተፈጥሮ ጽድን ለመተካት ሲባል በአርቲፊሻል ፕላስቲክ እየተዘጋጀ ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባው የፕላስቲክ ዛፍ ምርትም ጥቅም ላይ ውሎ ሲጣል የሚያስከትለው አደጋ ከፍተኛ እንደሆነ ግንዛቤ ሊያዝ ይገባል።ከዚህ ቀደም ተደጋግሞ በባለሙያዎች እንደተገለጸው ፕላስቲክ ቶሎ ስለማይበሰብስና በመሬት ውስጥ ረጅም አመት ስለሚቆይ የአፈር ለምነትን በማሳጣት ጉዳት ያስከትላል።
በአጠቃላይ የገና ዛፍን መጠቀም በመንፈሳዊም በአካባቢ ላይም በሚያሳድረው ተጽዕኖ ሰዎች ደስታን ይፈጥራል ከሚሉት በላይ ጉዳት አለው።በኢትዮጰያ ኦርቶዶክስት ተዋህዶ ቤተክርስቲያንም በክርስትና አስተምሮ የገና ዛፍ ከልደት በዓል ጋር ተያያዥነት እንደሌለው የእምነቱ ተከታዮች ይገልጻሉ።አብያተክርስቲያናት ከሌላው በበለጠ ለችግኝ ትልቅ ትኩረት እንደሚሰጡ በየቤተእምነቱ ግቢ ውስጥ የሚታዩ ሀገርበቀል ዛፎች ማሳያ ናቸው።
በአንድ ወቅት በተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን ተዘግበው ለህዝብ ጆሮ የደረሱት መረጃዎች እንዳመለከቱት በአሜሪካን ሀገር 98 በመቶ የሚሆነው የገና ዛፍ ተክል የሚለማው በእርሻ ማሳ ላይ ሲሆን፣ከአንድ ሚሊየን ሄክታር መሬትም ለዚሁ ተክል ይውላል።21ሺ የሚሆኑ አርሶአደሮች ጽድ በማብቀል ሥራ ላይ ተሰማርተዋል።አርሶአደሮቹ በአመት ከ34 እስከ 36 ሚሊዮን ለገና ዛፍ የሚውል ጽድ ያመርታሉ።
የምርት ሽያጩም ከሀገር ውስጥ ገበያ ከፍተኛውን ድርሻ የሚይዘው ወደ ውጭ የሚላከው በመሆኑ በገቢም ከፍተኛ የሆነ ትርፍ ይገኛል።አገልግሎት አሰጣጡም አብሮ የታሰበበት በመሆኑ ጽዶቹ ሳይጠወልጉ ተጠቃሚው ጋር እንዲደርሱ በሂሊኮፕተር ማጓጓዣ ይጠቀማሉ።
በአሜሪካ ‹‹ብሄራዊ የገና ዛፍ››የሚል ማህበር ተቋቁሞ በሥራ ላይ ይገኛል።ማህበሩ በየአመቱ ከምርቱ ለሀገሪቱ ፕሬዚዳንት በሥጦታ ያበረክታል።በኢትዮጵያም መጠቀሙ የግድ ከሆነ እንዲህ ያለውን ተሞክሮ ማዳበሩ ይመረጣል።ደንን ከመጨፍጨፍ መታደግ የዛፎቹን ዝርያ ለይቶ፣በዘርፉ ላይ የሰው ኃይል አሰማርቶና መሬት አዘጋጅቶ ተጠቃሚነቱ ላይ ትኩረት ማድረጉ ተገቢነት ያለው ተግባር እንደሆነ መጠቆም እንወዳለን።
ሌላው ማሳሰብ እምንፈልገው መጠቀም ብቻ ሳይሆን ስለአወጋገዱም ማሰብ አስፈላጊ መሆኑን ነው።የጽድ ዛፍ በመጠቀም በዓሉን የሚያከብሩ ሀገሮች የአካባቢ ብክለትንም የሚከላከሉበትን ዘዴ ግምት ውስጥ አስገብተው እንደሆነ መዘንጋት የለበትም።ግንዛቤው እያደገ ሲሄድ በኢትዮጵያ የገና በዓል ያለዛፍ የሚከበርበት ጊዜ እንሚመጣ ተስፋ እናደርጋለን።
አዲስ ዘመን ታህሳስ 29/2013