መርድ ክፍሉ
ሰውን ለመርዳት ሀብታም ወይም የሚሰጥ ነገር መኖር የለበትም፡፡ ሰው ሰውን ለመርዳት ቅንነትና ፍላጎት በቂ ናቸው፡፡ የሚረዳቸው ሰው ያጡ አረጋውያን፣ ህፃናትና አካል ጉዳተኞች በየቦታው ወድቀው ይታያሉ። ለዚህ ደግሞ በኢትዮጵያ ውስጥ በተግባር የመረዳዳቱ ሁኔታ አነስተኛ በመሆኑ ነው፡፡
ነገር ግን የመረዳዳትም ሆነ በልክ የመኖር ባህሎች ዛሬም እንዳሉ የሚያሳዩ ተግባራት እንዳልጠፉ በርካታ ማሳያዎችን ማንሳት ይቻላል። በተለይ በቅርቡ የኮቪድ 19 ወረርሽኝ መከሰትን ተከትሎ በርካታ ዜጎች ለከፍተኛ የኑሮ ጫና መዳረጋቸው ይታወሳል። ይህንን ክፉ ጊዜ ለማለፍ ደግሞ የደጋግና ቅን ልቦች መኖር ትልቅ አስተዋፅኦ ማድረጉን ስንመለከት የመረዳዳት ባህላችን ዛሬም ጠንካራ መሆኑን እንገነዘባለን።
በጎ ፍቃድ አገልግሎት ማለት በፍቃደኝነት ላይ የተመሰረተ ተሳትፎ በማድረግ ዉስጣቸዉ ከሚሰማቸው ሰብአዊ አመለካከት ተነስተው ለሚኖሩበት ማህበረሰብ ሰፊ የልማት አውታሮችን በመዘርጋት የዜግነት ኃላፊነትን የሚገነዘቡ ሃገራዊና ብሄራዊ ግዴታዎችን የሚያውቁበት በማህበራዊ ሚናዊች ስር ግንባር ቀደም የሚሆኑና የሃገርና የወገን ፍቅርን የሚያዳብሩበት ትልቅ ሚና ያለው ተግባር ነዉ፡፡
እነዚህ ወጣቶችም ባላቸዉ የእረፍት ጊዜያቸውን መስዋዕት አድርገው ልማትን ለማምጣትና ለአካባቢ ደህንነት ነጻ ጊዜያቸውን፣ ገንዘባቸውን፣ ጉልበታቸውን እና እውቀታቸውን በተጨማሪም በጎ አመለካከትን የሚያዉሉበት ስራ ሲሆን ሌሎችን ከመርዳት አኳያም በጎ ምኞትን ተላብሰው ከማህበረሰባቸው ጎን ሁነው የሚያውቁትን የሚያስተምሩበትና ከሌሎች አካላትም የህይወት ክህሎት የሚቀስሙበት ዋነኛ መንገድ ነው፡፡
በአገሪቱ በተለያዩ ክልሎች የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ከተከሰተ በኋላ ረጂና ጧሪ ቀባሪ የሌላቸውን ወገኞች በዘመቻ መልክ ድጋፍ ሲደረግላቸው ቆይቷል፡፡ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች በሚገኙ ከተሞች ወጣቶች በበጎ ፈቃደኝነት በመሰባሰብ አካባቢያቸው የሚገኙ ሰዎችን እየደገፉ ይገኛሉ፡፡ ወጣት በጎ አድራጊዎቹ አረጋውያንን፣ ህፃናትን፣ አካል ጉዳተኞችንና የጎዳና ተዳዳሪዎችን እየረዱና እየደገፉ ይገኛሉ፡፡ ከነዚህ መካከል ኢትዮጵያዊነት የበጎ አድራጎት ማህበር አንዱ ነው፡፡
የኢትዮጵያውነት የበጎ አድራጎት ማህበር ሊቀመንበር ወጣት ነብዩ ፈቃዱ እንደሚናገረው፤ የኢትዮጵያውነት የበጎ አድራጎት ማህበር በጌድዮ ዞን ዲላ ከተማ በሚገኙ ወጣቶች የተመሰረተ ነው፡፡ ማህበሩ የተመሰረተው ወጣት ነብዩ ከጓደኛው ጋር በመሆን ከሶስት ዓመት በፊት የተመሰረተ ቢሆንም ህጋዊ ሰውነት አግኝቶ መንቀሳቀስ ከጀመረ ግን አንድ ዓመት አስቆጥሯል፡፡
ማህበሩ ያከናወናቸው ተግባራት
ማህበሩ የሚሰራው አረጋውያን፣ አካል ጉዳተኞችና ህፃናት ላይ ሲሆን በብዛት ግን አረጋውያን ላይ አተኩሮ እየሰራ እንደሚገኝ ወጣት ነብዩ ይናገራል፡፡ የአረጋውን ቤቶችን ማደስ፣ ቤት ለሌላቸው ቤት መስራት፣ በየወሩ ለ150 አረጋውያን በቋሚነት የእህል ድጋፍ፣ ህክምና የሚያስፈልጋቸው አረጋውያንን ማሳከምና የአልባሳት እርዳታ እንደሚደረግ ይገልፃል፡፡
በከተማው የሚገኙ የተወሰኑ ጎዳና ተዳዳሪዎችን በየሰዉ ቤት ተጠግተው እንዲኖሩ የማድረግ ስራ መከናወኑን የሚጠቅሰው ወጣት ነብዩ፤ ሁለት መቶ የሚሆኑ ጎዳና ላይ የሚገኙ ህፃናትን ወደ ቤተሰቦቻቸው እንዲመለሱ መደረጉን ይጠቁማል፡፡ የህክምና አገልግሎት የሚያስፈልጋቸውን የጎዳና ተዳዳሪዎች በየቀኑ ህክምና እንዲያገኙ ይደረጋል፡፡ በየበዓላቱ አልባሳት ተገዝቶ እንደሚሰጣቸውም ያመለክታል፡፡
አካል ጉዳተኛ የሆኑና ደጋፊ የሌላቸውን ሰዎች ዊልቸርና ክራንች በመግዛት የሚሰጣቸው ሲሆን ለዚህ በከተማው የሚገኙ ባለሀብቶች ድጋፍ እንደሚያደርጉ ወጣት ነብዩ ይገልፃል፡፡ የማህበሩ አባላት ከሚያዋጡት ወርሃዊ መዋጮ ውጪ ባለሀብቱንና በጎ ፈቃደኞችን በማስተባበር ድጋፍ እንደሚገኝም ይናገራል፡፡
የኮሮና ወረርሽኝ በተከሰተበት ወቅት ከቤት መውጣት የማይችሉ አረጋውያንና አካል ጉዳተኞችን ቤት ለቤት በመሄድ ሳይንታይዘርና ሳሙና ተሰጥቷቸዋል። በወቅቱ በትምህርት ቤቱ የግንዛቤ ስራዎች ተሰርተዋል። ከመንግስት ጋር በመነጋገር ለህብረተሰቡ አስፈላጊ የሚባሉ ግንዛቤዎችን በመስጠት ሰፊ ስራዎች መከናወናቸውን ወጣት ነብዩ ይናገራል፡፡
ሌላው የማህበሩ አባል የሆነው ወጣት ቢንያም ሽፈራው እንደሚናገረው ከሆነ ማህበሩ ከተመሰረተ ጀምሮ የአረጋውያንን ቤት እያደሰ ይገኛል፡፡ ያለፈው ክረምት ወቅት የነበረው የአየር ሁኔታ አስቸጋሪ የነበረ ሲሆን አረጋውያኑ ከምግብና ከሌሎች ድጋፎች ይልቅ የመጠለያ ሁኔታዎች እንዲመቻቹላቸው ጠይቀዋል፡፡ በዚህም የአረጋውያን ቤቶች ታድሰዋል፤ ተሰርተዋል፡፡
በጎዳና ተዳዳሪነት የሚኖሩ ህፃናት ዙሪያም ማህበሩ በርካታ ስራዎች ማከናወኑን የሚናገረው ወጣት ቢንያም፤ ቤተሰብ ያላቸው የጎዳና ተዳዳሪ ህፃናት ወደ ቤታቸው እንዲመለሱ ከዲላ ከተማ ፖሊስ ፅህፈት ቤትና ከሴቶችና ህፃናት ፅህፈት ቤት ጋር በመተባበር ሁለት መቶ ህፃናት ወደ ቤተሰቦቻቸው እንዲመለሱ መደረጉን ይናገራል፡፡
የማህበሩን አባላት በማስተባበር ወርሃዊ አስቤዛ በማዘጋጀት ደጋፊ የሌላቸው አረጋውያን ይደግፋሉ፡፡ በሌላም በኩል ለአንድ ሰው አንድ አረጋዊ በመስጠት ከ300 እስከ 500 ብር በመመደብ የወር አስቤዛ እንዲገዙ በማድረግ ለተረጂዎቹ ይሰጣል፡፡ በተጨማሪም ምግብ ማብሰልና ልብስ በማጠብም አረጋውያኑ እንደሚታገዙ ወጣት ቢንያም ይጠቁማል፡፡
የህብረተሰቡ ተሳትፎ
የከተማው ህብረተሰብ ማህበሩ ከተመሰረተ ጊዜ ጀምሮ ከፍተኛ ድጋፍ ሲያደርግ የነበረ ነው፡፡ በማህበራዊ ሚድያ በኩል የማህበሩ ስራዎች ስለሚወጡ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ከፍተኛ ትብብር እያደረጉ መሆናቸውን ወጣት ነብዩ ይጠቁማል፡፡ በዚህም ማህበሩ ለሚፈልጋቸው ማንኛውም የድጋፍ እንቅስቃሴ ህብረተሰቡ ከጎኑ መሆኑን በተለያዩ ጊዜት ማሳየቱን ያመለክታል፡፡
ማህበሩ ከተመሰረተ በኋላ በተደረጉ እንቅስቃሴዎች የከተማው ህዝብ ለጋስ መሆኑ የታየበት መሆኑን ወጣት ቢንያም ይናገራል፡፡ በ2011 ዓ.ም በጌድዮና በምዕራብ ጉጂ አካባቢ በነበረው ችግር ለተፈናቀሉ ሰዎች ማህበሩ ድጋፍ ማድረጉን ይጠቅሳል፡፡ በዚህም የህብረተሰቡ ድጋፍና ለጋስነት የታየበት መሆኑን ይገልፃል፡፡ ህብረተሰቡ ድጋፍ ለማድረግ ወሰን፣ ሀይማኖትና ሌሎች ነገሮች የሚበግሩት አለመሆኑን ይናገራል፡፡
የተሰበሰበው ድጋፍ ለሚገባው ሰው የሚሰጥ ከሆነ ማህበረሰቡ ያለውን ከመስጠት እንደማይቆጠብ ወጣት ቢንያም ያስረዳል፡፡ በአካባቢ ያለን የተቸገረ መርዳት ኢትዮጵያዊ ባህል በመሆኑ ህብረተሰቡ የሚያስተባብረው ካገኘ ውጤታማ ስራ መስራት እንደሚቻልም ያመለክታል።
አሳዛኝ ከስተት
ከአንድ ዓመት በፊት ማህበሩ ድጋፍ ለማድረግ ቤት ለቤት አሰሳ በሚያደርግበት ወቅት ነበር ባልና ሚስት የሆኑ አረጋውያንን ያገኘው፡፡ አረጋውያኑ ቀደም ብሎ የነበረው ህይወታቸው የተደላደለና የሞቀም ነበር፡፡ በህመም አጋጣሚ ሁለቱም አረጋውያን ያላቸውን ሁሉ አጡ። አረጋውያኑ ምንም ልጅና የሚረዳቸው የሌለ በመሆኑ ለከፍተኛ ችግር ተጋልጠውም ነበር፡፡
ማህበሩ ወደ አረጋውያኑ ቤት ሲሄድ አረጋውያኑ የሚበሉት ምግብ እንኳን አልነበራቸውም ነበር፡፡ የአካባቢው ነዋሪም እንብዛም ትኩረት አድርጎባቸው ስለማያውቅ ያለማንም ደጋፊ ህይወታቸውን ሲገፉ ቆይተዋል፡፡ ማህበሩ ችግራቸውን ቀርቦ በመረዳት ምግብ በመደገፍና ቤታቸውን በመታደሱ አረጋውያኑ በጥሩ ሁኔታ ላይ ይገኛሉ፡፡ የማህበሩ አባላትም በየአስራ አምስት ቀኑ አረጋውያኑን ይጎበኛሉ፡፡ ህክምና አገልግሎትም በየጊዜው እያገኙም ነው፡፡
ማህበሩ ያጋጠሙት ችግሮች
ማህበሩ አብዛኛውን ጊዜ የገንዘብ ችግር የሚያጋጥመው ሲሆን አብዛኛው የማህበሩ አባላት የራሳቸው ስራ እንደሌላቸው ወጣት ነብዩ ይጠቁማል። ማህበሩ አንድ ቦታ ተቀምጦ የሚሰራበት ቦታ የሌለው ሲሆን በቅርቡ ቢሮ ማግኘታቸውን ይጠቁማል። ለአረጋውያን ቤት በሚሰራበት ወቅት አረጋውያኑን ቤት በመከራየት የሚያስቀምጧቸው ሲሆን በቀጣይ መንግስት ቋሚ የሆነ መሬት እንዲሰጣቸው በመነጋገር ላይ መሆናቸውን ያመለክታል፡፡ መንግስት መሬት ከሰጣቸው አረጋውያኑን በአንድ ቦታ አስቀምጦ ለመደገፍ እንደሚያስችል ይጠቅሳል፡፡ ከዚህ ውጪ ምንም አይነት ችግር እንዳላጋጠማቸውና ህብረተሰቡም የከተማ አስተዳደሩም አስፈላጊ የሚባሉ ድጋፎችን እያደረጉ መሆናቸውን ያብራራል፡፡
የማህበሩ አባላት መስራት በሚገባው ልክ እየሰራ አለመሆኑን የሚናገረው ወጣት ቢንያም፤ ዋነኛ ችግር የነበሩት የግብዓት ችግሮች ናቸው፡፡ ማንኛውም ድጋፍ ከህብረተሰቡ በመሰብሰብ ተመልሶ ለተቸገሩ ህብረተሰብ ክፍል የሚሰጥ ሲሆን አሁን ያለው የህዝቡ ግንዛቤ በተፈለገው ደረጃ የነቃ አለመሆኑ ችግር መፍጠሩን ወጣት ቢንያም ያመለክታል፡፡ በመንግስትም ይሁን በግለሰብ ደረጃ ስራውን ተረድተው ድጋፍ እያደረጉ ናቸው፡፡ ማህበሩ የራሱ የሆነ ቦታ ያስፈልገዋል፡፡ በሌላ በኩልም ሁሌም ከግለሰቦች ገንዘብ ከመሰብሰብ ማህበሩ የራሱ የሆነ ገቢ እንደሚያስፈልገውም ይናገራል፡፡
ከማህበረሰቡ ገንዘብ በማሰባሰብ የማህበረሰቡን ችግር መፍታት ካልተቻለ መንግስት ሁሉንም ችግር ሊፈታው እንደማይችል ወጣት ቢንያም ይገልፃል። መንግስት መሬትና ሌሎች አስፈላጊ ነገሮችን ድጋፍ ማድረግ ከቻለ ማህበሩ ተጠናክሮ የህብረተሰቡን ችግር ለመፍታት እንደሚሰራ ያመለክታል፡፡ በዲላ ከተማ የሚገኙ አረጋውያን ብዙ ሲሆኑ ማህበሩ እስካሁን 150 አረጋውያንን ብቻ እየደገፈ እንደሚገኝ ይጠቁማል፡፡
የከተማ አስተዳደሩን በተደጋጋሚ የመሬት ጥያቄ እንደሚመለስ ጥያቄ የቀረበ ቢሆንም የአመራር መቀያየር በመኖሩ ጥያቄው እስካሁን አለመመለሱን ወጣት ቢንያም ይናገራል፡፡ ነገር ግን ማህበሩ ገቢ ለማሰባሰብ በሚቀርፃቸው ገቢ ማሰባሰቢያዎች የከተማ አስተዳደሩ ትብብር እንደሚያደርግ ይናገራል፡፡ አሁን ካለው የከተማው አስተዳደር ጋር እንደ አዲስ ስራዎች እየተጀመሩ መሆናቸውን ይጠቁማል፡፡
የማህበሩ ቀጣይ እቅድ
ማህበሩ በቀጣይ ከከተማው በመውጣት ሌሎች ቦታዎች ላይ የመንቀሳቀስ እቅድ አለው፡፡ በአጎራባች ከተማዎች ሲዳማና ኦሮሚያ ክልል የበጎ አድራጎት ስራ ለማከናወን እቅድ እንዳለ ወጣት ነብዩ ይጠቅሳል፡፡ ዘላቂ መፍትሄ ለሚሹ አረጋውያን ቤት ከመስራት በዘለለ በቋሚነት የምግብ እርዳታዎችን በየወሩ እንዲሁም ምንም ደጋፊ ለሌላቸው ደግሞ በየሳምንቱ የምግብ ድጋፍ የማድረግ ሀሳብ ያለ ሲሆን በተበታተነ መንገድ የሚደረገው ድጋፍ ወደ አንድ መዓከል አረጋውያኑን ለማምጣት ታስቧል፡፡
በከተማው የሚገኙ የጎዳና ተዳዳሪዎችን በመሰብሰብ የግንዛቤ ስራ በመስራት ስራ እንዲጀምሩ ተደርጓል። ትምህርት መማር የሚችሉትን ለማስተማር፣ ስራ መስራት የሚችሉትን ደግሞ ወደ ስራ ማሰማራትና ቤተሰብ ያላቸውን ወደ ቤተሰቦቻቸው የመመለስ ስራ እንደሚከናወን ወጣት ነብዩ ያመለክታል፡፡ ማንም ሰው ጎዳና ላይ እንዳይኖር በሚል መርህ እየተሰራም መሆኑን ይናገራል፡፡
አቅማቸው ለስራ ያልደከሙ አረጋውያንን ከበጎ አድራጊዎች ጋር በመነጋገር ከመንግስት ቦታ በመጠየቅ የማደራጀት ስራ በመስራትና ወደ ስራ ከገቡም በኋላ የገበያ ትስስር ለመፍጠር እቅድ ተይዟል፡፡ አካል ጉዳተኞች ባሉበት ቦታ በመሰብሰብ የተወሰነ የስራ እድሎችን ለማመቻቸት መታሰቡን ወጣት ነብዩ ይጠቁማል፡፡ ይህም ስራ ከሁለት ወራት በኋላ ወደ ተግባር የሚገባ እንደሚሆን ይናገራል፡፡
ለማንኛውም የሀይማኖት በአላት ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት የበጎ ስራ እንደሚከናወን የጠቀሰው ወጣት ነብዩ፣ ለአረጋውያኑ እንደ ሀይማኖታቸው በበዓላት ወቅት ከፍተኛ ስራ እንደሚከናወን ይጠቅሳል፡፡ በበዓላት ወቅት ቤት ለቤት በመሄድ ከአረጋውያኑ ጋር በዓል የሚከበር ሲሆን በየሳምንቱ በቡድን በመከፋፈል ጉብኝት እንደሚደረግም ይናገራል፡፡ በጉብኝቱ ወቅት ቤት ማፅዳት፣ ምግብ ማብሰልና የአረጋውያኑን ገላ ማጠብ እንደሚከናወን ይጠቅሳል፡፡
ወጣት ቢንያም እንደሚናገረው፤ ማህበሩ የራሱን ገቢዎች ለመፍጠር ፕሮጀክቶች ቀርፆ እየተንቀሳቀሰ ነው። የዶሮ እርባታ ለመጀመር ታስቧል፡፡ ማህበሩ ሲመሰረት በዋነኝነት አረጋውያንና ህፃናትን ለመርዳት ታስቦ እንደመሆኑ የጎዳና ተዳዳሪዎችን ለማንሳት እቅድ አለ፡፡
በጎዳና ላይ የሚገኙ ህፃናት መማር ቢችሉና ስነልቦናቸውን ማስተካከል ከተቻለ ለውጥ ማምጣት እንደሚቻል ወጣት ቢንያም ይጠቁማል፡፡ የጎዳና ተዳዳሪ ህፃናትን ካሉበት ህይወት ለማውጣት ፕሮጀክት ተቀርፆ ወደ ተግባር እንደሚገባ ይናገራል፡፡
ማህበሩ በአሁን ወቅት በእጁ ላይ የሚገኙትን ተረጂዎች ለመደገፍ የሚያስችል ግብዓት ማነስ እንጂ መረዳት ያለባቸው አረጋውያን እየተደገፉ አለመሆናቸውን ወጣት ቢንያም ይገልፃል፡፡ እነዚህን አረጋውያን መደገፍ በሚያስችል ሁኔታ ስራዎች ለመጀመር ታስቧል፡፡ አረጋውያኑን በኢኮኖሚ ብቻ መደገፍ ለውጥ ስለማያመጣ አረጋውያኑን አንድ ማዕከል አስገብቶ መርዳት የማህበሩ እቅድ መሆኑን ያስረዳል፡፡
ሌላው ማህበሩ መስራት የሚፈልገው ከወጣቶች ጋር በተያያዘ ሲሆን ወጣቱ ከስራ ውጪ የሚያሳልፍባቸውን ቦታዎች ማዘጋጀት ላይ ነው፡፡ ወጣቱ ሱስ ውስጥ እንዳይገባ የማድረግ ስራ በረጅም ጊዜ እቅድ ውስጥ አስገብቶ እየሰራ መሆኑን ወጣት ቢንያም ያስረዳል፡፡
አዲስ ዘመን ታህሳስ 23/2013