
የአእምሮን እንደ አዲስ የማስተካከል ጉዳይ በጣም ወሳኝ ነው። ፈረንጆቹ ጋር ደግሞ ይህ በጣም የተለመደ ሀሳብ ነው። እንደውም /reprogram your mind/ or/reprogram your sub conscious mind/ እያሉ የተለያዩ ሀሳቦችን ያነሳሉ። ለመፍትሄዎችም የተለያዩ መጽሐፎችን ይፅፋሉ። ሴሚናሮችን ያዘጋጃሉ። ቪዲዮዎችን ይሰራሉ። በዚህም ሰዎች አእምሯቸውን እንደ አዲስ ይቀይራሉ።
ለምን መሰላችሁ? ኑሮ ያደክመናል። ሕይወት ተደጋጋሚና አሰልቺ ትሆናለች። አእምሯችን ብዙ መጥፎ ነገሮችን ይሸከማል። ቁጭት፣ ጭንቀት፣ ፍርሃት አለብን። በቃ! መጥፎ ስሜቶች በውስጣችን አሉ። ታዲያ እነዚህ ስሜቶች ከአእምሯችን ውስጥ መራገፍ አለባቸው። እንደ ልጅ ጥርት ያለ ሃሳብ ማሰብ አለብን። ንፁህ አእምሮ ያስፈልገናል። አእምሯችንን እንደ አዲስ ለማስተካከል ታዲያ ምን ማድረግ አለብን?
የመጀመሪያው አእምሮህ እንዴት እንደሚሰራ ማወቅ አለብህ። ለምሳሌ ስልክ ነክቶ ለማያውቅ ሰው ዘመኑ የደረሰበትን የመጨረሻውን የስልክ ምርት አይፎን ሰርቲን ፕሮ ማክስ ገዝተህ ብትሰጠው ‹‹እንዴት የሚያምር የከበረ ድንጋይ ነው? ደሞ እኮ ልስላሴው›› ብሎ ቤቱ እንደተራ እቃ ሊያስቀምጠው ይችላል። ለምን አያውቀውማ! አእምሮህ ለምን እንደሚሰራና እንዴት እንደሚሰራ ካላወክ አጠቃቀሙን አታውቅበትም።
አንዳንዴ አእምሯችን እንዴት እንደሚሰራ ስለማናውቅ ስንጨነቅ መድኃኒት እንውጣለን። ትንሽ ነገር ሲገጥመን ‹‹ምነው ፈጣሪዬ ምን አደረኩህ›› እንላለን። ትንሽ ነገር ሲፈጠርና መጥፎ ስሜት ሲሰማን ፈጣሪን እናማርራለን። በቃኝ እንላለን። ተስፋ እንቆርጣለን። እኔ እኮ አበቃልኝ እንላለን። ሕይወትን ትርጉም እናጣበታለን። ለምን? የአእምሯችን አሰራር አልገባንም። አእምሯችን ነው የተጎዳው። እኛ ግን በአካል ሁሉ ነገራችን ይጎዳል።
አያችሁ የአእምሯችን አሰራር በጣም ወሳኝ ነው። ስለዚህ አንተ ሕይወትህን እየጠላሃት ያለኸው ምን አልባት አእምሮህ እንዴት እንደሚሰራ ስላላወክ ነው። ከዚህ በኋላ ግን መጨነቅ ማቆም አለብህ። መፍራት ታቆማለህ። መጥፎ ስሜቶችና ሃሳቦች አእምሮህን አይቆጣጠሩትም። አዕምሮህ እንዴት እንደሚሰራ ማወቅ ብቻ ነው ካንተ የሚጠበቀው።
ሁለት አይነት የአእምሮ ክፍሎች አሉ። ንቁ /conscious/ እና ድብቅ /sub-conscious/ ይባላሉ። ንቁ /conscious የአእምሮ ክፍል በጣም ንቃት ውስጥ ሆኖ ነው የሚያገለግለው። ለምሳሌ አንድ ነገር አዲስ ከሆነ ንቁ ሆነን ነው የምንሰማው። አዲስ ነገር ስንለምድ ነቃ ብለን ነው የምናዳምጠው። ለመጀመሪያ ጊዜ ምግብ ያበሰላችሁ ጊዜ አንዳንዱን ሂደት በንቃት ነው የምንከታተለው። ኪ ቦርድ ለመጀመሪያ ጊዜ ስንተይብ (ታይፕ ስናደርግ) እያንዳንዷን ፊደል እየመረጥን ነው።
ብዙ ጊዜ ግን በቀን ውስጥ አዲስ ነገር የምንለምደው ለጥቂት ሰዓታት ነው። ብዙ ሰዓት ንቁ አይደለንም። ስለዚህ ንቁ /conscious/ የሚባለውን የአእምሮ ክፍል ብዙ ጊዜ አንጠቀምበትም። ስለዚህ በጣም ወሳኙ ሁለተኛውና ድብቅ /sub-conscious/ የሚባለው የአእምሮ ክፍል ነው። ይህ የአእምሮ ክፍል ደጋግመን የምናደርጋቸውን ነገሮች የሚቆጣጠር የአእምሮ ክፍል ነው። በሰውነታችን ውስጥ ከሚካሄዱ እያንዳንዱ ሂደቶች ጀምሮ ለምሳሌ የምግብ ልማትና መተንፈስን ጨምሮ ማንኛውንም የሰውነት ሥርዓቶችን ይቆጣጠራል።
ይህን ብቻ ሳይሆን ልማዶቻችንን፣ ደጋግምን የምናደርጋቸውን ነገሮች በሙሉ ድብቅ /sub-conscious/ ነው የሚቆጣጠረው። ለምሳሌ የኮምፒዩተር ኪቦርድ ላይ ስትፅፍ የሆነ ሰዓት ላይ መልመድ ትጀምራለህ። ስለዚህ ይህ ድብቅ /sub-conscious/ የሚባለው የአእምሮ ክፍል ማስታወሻዎችን ይመዘግባል። ስለሆነም በኪቦርዱ ላይ ኤ የቱ ጋር እንደሆነ ታውቃለህ። ወዲያው ሌሎቹንም ፊደሎች ትነካካለህ። ብዙ ነገሮች ላይ ፈጣን የምትሆነው ድብቁ የአእምሮ ክፍልህ ስለለመደው ነው። ስለዚህ ድብቁ የአእምሮ ክፍል ደጋግመን ያደረግነውን፣ ተደጋግሞ የሰማነውን፣ የተነገረንን፣ ደጋግመን ያየነውን ሕይወታችን ላይ መዝግቦ ያስቀራል። ዋናው የአእምሮ ማስታወሻ ክፍል ነው። በእሱ መንገድ እንድንጓዝ ያደርገናል።
ለዛ ነው አንዳንድ ልጅ በልጅነቱ አትችልም እየተባለ ተደጋግሞ ከተነገረው ትንሽ ከፍ ሲል አልችልም የሚል ስሜት ይሰማዋል። ስለዚህ አይሞክርም። አዲስ ነገር ላይ አይደፍርም። አንዳንድ ልጅ በልጅነቱ አንተ ጎበዝ ነህ ! ጀግና ነህ እየተባለ ያደገ ልጅ ደግሞ ደፈር ይላል። ብዙ ነገር ይሞክራል። ደጋግሞ የሰማውን በሕይወቱ ላይ ይገልጠዋል። በልጅነት ጊዜ ብቻ ሳይሆን ከፍ እያልን ስንሄድ አብረናቸው የምንውላቸው ጓደኞቻችን የሚነግሩን ነገሮች በእኛ ድብቁ የአእምሮ ክፍል ውስጥ ተመዝግበው ይቀራሉ። ድብቁ የአእምሮ ክፍል አብዛኛውን የሕይወታችን ክፍል ይወስናል።
ድብቁ /sub-conscious/ የአእምሮ ክፍል አንድ የተለየ ባህሪ አለው። ሞኝ ነው። ደጋግሞ የተነገረውን ነገር ያስቀራል። መቼም ሞኝ ታውቃላችሁ። የሆነ ነገር ካደረጋችሁት ‹‹እሱ እኮ እንዲህ አድርጎኝ›› ይላል። ቂም ነው የሚይዝባችሁ። ልክ ‹‹ሞኝና ወረቀት የያዘውን አይለቅም›› እንደሚባለው። ሞኝ ውለታ ከዋላችሁለትም የሆነ ቀን አስታውሶ ‹‹እሱ እኮ እንደዚህ አድርጎልኝ›› ይላችኋል። በቃ! ድብቁ የአእምሮ ክፍል ልክ እንደሞኝ የሰበሰበውን፣ ደጋግሞ የሰማውን መዝግቦ ያስቀራል።
እንግዲህ ላዛ ነው አንተም የምትጨነቀው። አየህ! የሚያስጨንቁ ጉዳዮችን ደጋግመህ ትሰማለህ። ስለዚህ በሕይወትህ ትጨነቃለህ። የዘራኸውን ታጭዳለህ። የምትዘራው መጥፎ ጭንቀት፣ መጥፎ ሀሳብ፣ መጥፎ ነገር ከሆነ እሱ በሕይወትህ ይገለጣል። አሁንም የምትጨነቀው ለዛ ነው። ደስ የሚለው ነገር ግን ይህ ድብቁ የአእምሮ ክፍልህን መቀየር ትችላለህ። እንዴት አድርገህ? እየደጋገምክ ለአእምሮህ ጥሩ ጥሩ ነገሮችን በመንገር። አዳዲስ ነገሮችን በአእምሮህ ውስጥ በመዝራት።
አእምሯችን እንደመሬት ነው። የሚዘራበትን መምረጥ አይችልም። መሬት አፍ አውጥቶ ስንዴ ዝሩብኝ አይልም። እኛ ሰዎች ነን መሬቱ ላይ የምንዘራው። ግን ደግሞ ስንዴ ፈልገን ስንዴ ከዘራን መሬቱ ስንዴ ያበቅላል። አእምሮህ አንተ የምትፈልገውን ነገር ነው የምትጭንበት። የምትሰማው ነገር ወሳኝ ነው። ጥሩ ነገር ከሰማህ በአእምሮህ ውስጥ ጥሩ ነገር እየዘራህ ነው።
አየህ! ከዚህ በኋላ አእምሮህን አዲስ ማድረግ አይደል ዓላማህ? ስለዚህ አእምሮህን የሚያስተካክል ነገር መስማት ትጀምራለህ። የምትሰማው ነገር መንፈሳዊ ነገር ሊሆን ይችላል። መልካም ነገር፣ ተስፋ የሚሰጥ ነገር ሊሆንም ይችላል። ከዚህ ውጭ ግን ሌላ ነገር አትሰማም። ሌላ ነገር አታደርግም። ትጠነቀቃለህ። ለምትዘራው ነገር ተጠንቀቅ። የአእምሮ በርህን ጠብቅ። አየህ! ከዚህ በኋላ መጥፎ ዜና መስማት የለብህም። ለምን? መጥፎ እንድታስብ ያደርግሃል።
በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ በትዝታ መኖር ማቆም ይኖርብሃል። ምን አልባት ስለትናንት እየደጋገምክ ታስብ ይሆናል። ትላንት ስለደረሰብህ መጥፎ ነገር፣ ስለገጠመህ ቁጭት፣ በጣም የሚያስቆጩህን አጋጣሚዎች ታስባቸዋለህ። ጭንቀትህ ስለትናንት ነው። ስለዚህ ትላንትን በዛሬ ውስጥ እየኖርክ ነው ማለት ነው። አእምሮህ ደጋግመህ የምታስበውን ነው የሚሰጥህ። ትላንትናን ካሰብክ ትላንትናን ዛሬም ትደግመዋለህ። ሕይወት ተደጋጋሚ ትሆናለች። አሰልቺ ትሆናለች። የትናንቱን ዛሬም ትኖረዋለህ።
ታዲያ ምን ይሻላል? ነገን በዛሬ ውስጥ መኖር መጀመር አለብህ። ነገን እያሰብክ ዛሬ ላይ ጠንክር። ነገ በሕይወትህ ይገለጣል። አየህ! መልካም ነገሮችን ደጋግመህ ስታስብ መልካም ነገር በአእምሮህ ውስጥ እየዘራህ ስለሆነ መልካም ነገር በሕይወትህ ትገልጣለህ። የቀንም የሌሊትም ህልመኛ መሆን አለብህ። የቀን ህልመኞች መሆን በራሱ ሕይወታችንን ይቀይረዋል። ቀን ላይ ዝም ብለን ስንቀመጥ መልካም ነገሮችን ብናስብ ‹‹እንዲህ ባደርግ፣ ይሄን ባሳካ፣ ይሄ ቢኖረኝ›› ብንል አእምሯችንን መልካም ነገር እየመገብነው ነው።
ድብቁ የአእምሮ ክፍል አንተ ተኝተህም ይለፋል። አንተ የምትፈልገውን ነገር ለመስጠት የማያደርገው፤ የማይቆፍረው ጉድጓድ የለም። አንዳንዴ ቁጭ ስትሉ ከሰው ጋር እያወራችሁ የሆነ ሃሳብ ብልጭ ብሎላችሁ አያውቅም? እርግጠኛ ነኝ ያውቃል። ምክንያቱም ድብቁ አእምሮ ደጋግሞ እያሰበ ነበር። አንተ ሌላ ነገር ውስጥም ብትሆን አእምሮህ መልሱን ሲያገኝ መስራት ይጀምራል።
አየህ! ስለነገ ህልምህና መልካም ነገር ካሰብክ የሆነ ሰዓት ላይ በሕይወትህ ድብቁ የአእምሮህ ክፍል ይገልጠዋል። ፈጣሪህም ተአምሩን የሚያሳይህ በድብቁ የአእምሮ ክፍልህ ነው። ታዲያ የቀን ህልመኛ ብቻ ሳይሆን የሌሊትም ህልመኛ መሆን አለብህ። ልትተኛ ስትል በጣም የምትፈልገውን ነገር አጥብቀህ እያሰብክ መተኛት አለብህ። እውቁ የሳይንስ ሊቅ አልበርት አንስታይን ‹‹ልተኛ ስል በጣም ልፈታው የምፈልገውን ሳይንሳዊ ችግር እያስብኩት እተኛለሁ። እኔ ግን የማስበው ፈትቼዋለሁ ብዬ ነው። ጠዋት ስነሳ ግን ያን ችግር ፈትቼው፤ መፍትሄውንም አግኝቼው እነቃለሁ›› ይላል።
ስለዚህ የትኛውንም የዚህ ዓለም ችግር እንደፈታኸው አስበህ የምትኖር ከሆነ የሆነ ሰዓት መፍትሄው በሕይወትህ ይገለጣል። ድብቁ የአእምሮ ክፍል ስራውም ይህ ነው። ለዛ ነው የቀንም የሌሊትም ህልመኛ መሆን ያለብህ።
በሶስተኛ ደረጃ ውስጥህ ነው ወሳኙ። ወዳጄ! ውጫዊ ነገሮችና ውጫዊ ሁኔታዎች ያንተን ውስጣዊ ሰላምና ደስታ ሊወስኑት አይገባም። መፍቀድ የለብህም። ምክንያቱም ለምሳሌ ሰዎች ሲያደንቁህ ደስ የሚልህ ከሆነ፣ ፊት ሲነሱህ፤ የልባቸውን አውጥተው መጥፎ ነገር ሲናገሩህ አንተ የሚከፋህ ከሆነ ያንተን ውስጥ እየተቆጣጠረው ያለው ውጫዊ ዓለም ነው። ዓለም ስትገላበጥ ውስጥህ መገላበጥ የለበትም። ከውጭ ወደ ውስጥ መኖር ማቆም አለብህ። ከውስጥ ነው ወደውጭ መኖር ያለብህ።
ውስጥህ ሰላምና ደስታ ካለ ዓለም አብራህ ትስቃለች። አብራህ ትደምቃለች። ሕይወትህን የሚወስነው ውስጣዊ ነገር ነው። አየህ! መለወጥና መቀየር የምትጀምረው ከውስጥ ወደ ውጭ መኖር ስትጀምር ነው። አለበለዚያ ይች ዓለም አትሞላም። ስለዚህ ዓለም በተቀየረች ቁጥር ውስጥህ የሚቀየር ከሆነ መቼም ደስተኛ አትሆንም። ሕይወትህ ላይ ጭንቀቶችና መጥፎ ሀሳቦች የሚቆጣጠሩህ ውጫዊ ነገሮችን እያየህ ነው።
አየህ! እንደዛ እንዲሆን መፍቀድ የለብህም። አንተ ሁልጊዜም የሰው ልጅ ነኝ ብለህ ማመን አለብህ። ‹‹እኔ ሁልጊዜም ደስተኛ ነኝ፤ በፈጣሪዬም ደስተኛ ነኝ፤ ጤና ሰጥቶኛል›› በል። ያለህን እያየህ በውስጥ እርካታ ሊኖርህ ይገባል። ያኔ ውጭህም ያምራል።
በአራተኛ ደረጃ አካባቢህን ምረጥ። አንዳንዴ አንተ በጣም አቅም አለህ። በጣም ትችላለህ። ሕይወትህ ላይ የጎደለህ ነገር የለም። ፈጣሪህ የሰጠህ ብዙ ችሎታዎች አሉህ። ብቃትህን እንዳታወጣው ያደረገህ በአካባቢህ ያሉ ሰዎች ሊሆኑ ይችላሉ። አካባቢህም ሊሆን ይችላል። ታዲያ አእምሮህን እንደ አዲስ ማስተካከል የምትፈልግ ከሆነ መቆረጥ ያለበትን ቁረጥ። መቀጠል ያለበት ነገር ካለ ደግሞ ቀጥል። ከጥሩ ሰዎች ጋር ዋል።
አካባቢህ አንተን ይወስንሃል። ለምሳሌ ማድቤትህ ውስጥ ምግብ እያበሰልክ አንድ ሰው መጥቶ ቆሻሻ ቢደፋብህ ትተናነቀዋለህ። ለምን? ምግቡ ሆድህ ውስጥ ስለሚገባ ለምትበላው ታስባለህ። አእምሮህ ውስጥ ለሚገባው ነገርም ማሰብ መጀመር አለብህ። አእምሮህ ውስጥ መጥፎ ነገር፣ ቆሻሻ ለሚበትኑ ዜናዎች፣ ሃሳቦች፣ መጥፎ ሰዎች፣ እንደማትችል ለሚነግሩህ ሰዎች ቦታ መስጠት የለብህም።
አካባቢህን በደምብ አጥናው። ላንተ የሚመጥን ከሆነ አእምሮህ እንደ አዲስ መሰራት ይጀምራል። የምትሰማው ነገር በጣም ወሳኝ ነው። ሕይወትህ ላይ የሚገለጠውም ደጋግመህ የሰማኸው፣ ያደረከው፣ የምትውለው ቦታ ነው። የዛሬ አምስት አመት ያደረካቸው ነገሮች አሁን ያለህበትን ወስነዋል። የዛሬ አምስት አመት የምትደርስበትን የሚወስኑት ደግሞ አሁን የምታደርጋቸው ነገሮች ናቸው። ስለዚህ አካባቢህን ምረጥ።
አምስተኛውና የመጨረሻው ደረጃ የመደጋገም ኃይል ሲሆን ይህም ወሳኝ ነው። ከባድ ነገሮች ቀላል የሚሆኑት ከደጋገምናቸው ብቻ ነው። አንድን ነገር ደጋግመን ስናደርገው አእምሮን ያንን ነገር ቀለል አድርጎ ለመስራት የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም። በአእምሮን እየደጋገምን አንድን ነገር ስንሰራ በቀላሉ ነገሩን እንድንከውን ጥርጊያ መንገድ ያመቻቻል።
ስለዚህ የመደጋገም ኃይል ወደሕይወታችን እንዲገባ ማዳበር አለብን። አንተ የምትደጋግመውን ነው ህይወትህ ላይ ምታገኘው። ደጋግመህ የምተሰማውና የምታየው ነገር በጣም ወሳኝ ነው። ስለዚህ በእጅ በእግርህ ብለህ አእምሮ ማሰብ ያለበትን እንዲያስብ አድርግ። እየደጋገምክ ለአእምሮህ ጥሩ ነገር ንገረው።
አስናቀ ፀጋዬ
አዲስ ዘመን ሰኔ 24/2015