የክረምት ስሜቱ ደብዛዛ ነው። ይህም ቢሆን ክረምት የሕይወትና ሕልውና ዑደት መሠረት ነው። የበጋ ወራት ፍስሐና ተድላ የክረምት ስጦታዎች መሆናቸውም የሚካድ አይደለም። በክረምት ሰማዩ ዝናብ ይለግሳል፤ መሬትም ረስርሳ ሕይወት ትሰጣለች። የሰው፣ እንስሳትና እጽዋት ቀጣይነትም በክረምት ወቅት በሚመጣው በረከት የሚወሰን ነው። የሰብል ልምላሜ፣ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድቦች አቅም ሳይቀር የሚወሰነው በዚሁ ወቅት ነው።
ክረምት ከአዎንታዊ ጎኑ ባሻገር አሉታዊ ጎንም አለው። በተለይ ከባድ ዝናብን ተከትሎ የጎርፍና ውሃ ሙላት ስጋቶች ይከስታል። ለሰው ሕይወትና ለሀገር ሀብት ጥፋት ምክንያትም ይሆናል። የጤና ቀውስ የመሆን ዕድሉም ከፍተኛ ነው። እንደ ጉንፋን፣ አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት የመሳሰሉ የጤና ችግሮች ይወልዳል።
በክረምት ወቅት በገጠርም ሆነ በከተሞች ውሃ ያቆሩ ሥፍራዎች የወባ ትንኝ ያራባሉ። የውሃ መፋሰሻ ቱቦዎች ይዘጋሉ። የክረምት ባህሪ እንደ ጉንፋን፣ የአፍንጫን ጨምሮ ሌሎች የአስም ዓይነቶች እንዲሁም በአለርጂ ሳቢያ የሚከሰቱ የመተንፈሻ አካላት የጤና ችግሮችን ይወልዳል።
የክረምት ወራት በተላላፊ በሽታዎች ብቻ አይወሰንም። የክረምት ክፋቱ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችንም እንዲስፋፉ ዕድል መፍጠሩ ነው። የካንሰር፣ የልብና ስኳር በሽታዎች በዚህ ወቅት የሚበረቱ ተላላፊ ካልሆኑ በሽታዎች መካከል በቀዳሚነት የሚጠቀሱ ናቸው።
ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ሳቢያ በየዓመቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከ36 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ለሕልፈተ-ሕይወት እንደሚዳረጉ ጥናቶች ያሳያሉ። የጤና ባለሙያዎች እንደሚሉት በተለይ በክረምት ወቅት ጤነኛ ያልሆነ አመጋገብ፣ የአኗኗር ዘይቤዎች፣ ሲጋራ ማጨስ፣ አልኮል መጠጣት፣ በቂ የአካል እንቅስቃሴ አለማድረግ ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎች ያጋልጣሉ።
ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ላይ በኢትዮጵያ ሰፊ ጥናት ባይደረግም ወደ ሕክምና ተቋማት የሚመጡ በበሽታው የተያዙ ሕሙማን ቁጥርና ሥርጭት መጠን ከጊዜ ወደጊዜ እየጨመረ ስለመምጣቱ የተለያዩ መረጃዎች ይጠቁማሉ። ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ከፍተኛ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ የሚያስከትሉ ናቸው። የደም ግፊት፣ የስኳር፣ ኮልስትሮል፣ የልብና የተለያዩ የካንሰር በሽታዎች በተለይም ክረምት ላይ የኅብረተሰቡን ብርቱ ጥንቃቄ ይሻሉ።
በክረምት ወቅት በርካታ ሰዎች ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ ሳያደርጉ በቤታቸው እንዲያሳልፉ ሊገደዱ ይችላሉ። ይህ ደግሞ ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎች የማጋለጥ ሳይንሳዊ መሠረት እንዳለው ባለሙያዎች ይገልፃሉ። አንድ ሰው በቀን ከ30 ደቂቃ ያላነሰ እንቅስቃሴ ቢያደርግ በተወሰነ መጠን ላብ እንዲወጣ በማድረግ ብቻ የሰውነቱን የቅባት መጠን መቀነስ ስለሚያስችለው በስኳር፣ ደም ግፊትና የልብ በሽታ የመጠቃት ዕድሉን ማጥበብ ያስችለዋል። አብዛኛው ሰው ግን ይህንን እንቅስቃሴ በክረምት ጊዜ እንደማያደርግ ይነገራል።
በአመጋገብ ረገድ ስጋ፣ ወተት፣ እንቁላልና መሰል የእንስሳት ተዋፅኦ ምግቦችን መቀነስ እንደሚገባና ይልቁንም አትክልትና ፍራፍሬ ምግቦችን መመገብ የተሻለ የሰውነት በሽታን የመከላከል አቅምን መገንባት እንደሚያስችል በጤና ባለሞያዎች ይመከራል።
በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በክረምት ወቅት እንደሚያርፉ ይገመታል። ከእነዚህ ውስጥ ደግሞ ተማሪዎችና መምህራን በአብነት ይጠቅሳሉ። ክረምቱ ለእንቅስቃሴ ምቹ ባለመሆኑ በእረፍት ምክንያት ረዥም ጊዜ ቤት ውስጥ መቀመጥ ከእንቅስቃሴ ጉድለት ጋር ተያይዞ ለሚወለዱ ደም ግፊትና መሰል የጤና ችግሮች እንደሚያጋልጥ ማወቅም ተገቢ ነው ይላሉ የጤና ባለሞያዎች።
በክረምት ብዙ ሠራተኞች ከቅዝቃዜም ከዝናብም አንጻር ተሰባስበው የመቀመጥ ልምዱ ከፍ ቢልም በአንጻሩ ለተላላፊም ሆነ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች የመጋለጥ ዕድሉ ከፍ ይላል። እናም በክረምቱ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ላለመጋለጥ እንቅስቃሴ ማዘውተር አስፈላጊ መሆኑ አጠያያቂ አይደለም። ከወባ፣ ኮሌራና መሰል ተላላፊ በሽታዎች ለመዳን ደግሞ ለንጽህና ከፍተኛ ትኩረት መስጠት እንደሚገባ ይመከራል።
በቅዱስ ጴጥሮስ ሆስፒታል የውስጥ ደዌ ስፔሻሊስት ሐኪም ዶክተር ሰላም ስዩም እንደሚሉት፣ የክረምት ወቅት ውሃ ወለድን ጨምሮ የተለያዩ የመተንፈሻ አካላት ችግር የሚታይበት ጊዜ በመሆኑ በተለይም ከጤና ጋር በተያያዘ በጣም ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል። ከዚህ አንፃር ሰዎች በተለይም እንደ አጣዳፊ ተቅማጥና ተውከት (አተት) ያሉ በሽታዎች በክረምት ወቅት አቅማቸው የጎላ በመሆኑና የመከሰት ዕድላቸውም ሰፊ መሆኑን በመገንዘብ በተቻለ መጠን የራስንና የአካባቢን ንጽህና መጠበቅ ብሎም ያልበሰሉ ምግቦችን ከመመገብ መታቀብ ይኖርባቸዋል።
በተጨማሪም ሰዎች በተለይም ያልተጣራ (የቧንቧ) ያልሆነን ውሃ ሲጠጡ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ አለባቸው። በተቻለ መጠን ውሃን አፍልተው መጠጣትና ሌሎች ውሃን ሊያክሙና ከውሃ ወለድ በሽታዎች ሊያጣሩ የሚችሉ ኬሚካሎችን መጠቀም አለባቸው። በሌላ በኩል ደግሞ የአተት በሽታ ማንኛውንም ሰው የሚያጠቃ በመሆኑና በተለይ በሽታው ሕፃናትና አረጋውያን ላይ ሲከሰት ይዞት የሚመጣው ችግርም ከፍ ስለሚል ኅብረተሰቡ ሊወስዳቸው የሚገቡ ጥንቃቄዎች ከፍተኛ መሆን አለባቸው። ለበሽታው አጋላጭ የሆኑና በተለይ ደግሞ ያልበሰሉ ምግቦችን ከመመገብ መቆጠብ ይኖርባቸዋል።
ዶክተር ሰላም እንደሚያብራሩት እንደ ሰላጣ፣ ቲማቲምና ሌሎችም ሳይበስሉ ሊበሉ የሚችሉ የምግብ ዓይነቶች ለእነዚህ በሽታዎች ጥሩ መራቢያ በመሆናቸው ሰዎች እነዚህን ምግቦች ለመመገብ ሲያስቡ በሎሚና ሌሎች የአትክልት ማጠቢያ ኬሚካሎች ተጠቅሞ ማጠብ ያስፈልጋል። በተቻለ መጠን ደግሞ እነዚህን ያልበሰሉ ምግቦች ሕፃናት እንዳይጠቀሟቸው ማድረግ የበሽታውን የመስፋፋት መጠን በእጅጉ ይቀንሰዋል።
አጣዳፊ ተቅማጥና ተውከት (ኮሌራ) ከሌሎች ወይም ከምናውቃቸው የህመም ዓይነቶች ለየት ያለ ነው። ህመሙ የያዘው ሰውም የማያቋርጥና ወደውሃነት የተጠጋ ተቅማጥ ያስከትላል። ማስመለስ አልፎ አልፎ ትኩሳትና ራስ ምታትም የበሽታው ባህሪያት ናቸው። እንደዚህ ዓይነት ምልክቶች ሲታዩ ታዲያ በቶሎ ወደ ጤና ተቋም መምጣት ያስፈልጋል። በሽታው የያዛቸውን ሰዎችንም ለይቶ ማቆየት፣ በተመገቡባቸውና በነኳቸው ዕቃዎች ያለመጠቀም የበሽታውን የመተላለፍ መጠኑን በእጅጉ ይቀንሰዋል።
‹‹ሁሉም ተቅማጦች ኮሌራ አይደሉም›› የሚሉት ዶክተር ሰላም ነገር ግን ከላይ የተጠቀሱት ምልክቶች ሲኖሩ በትክክል የበሽታው ምልክቶች መሆኑን መገንዘብ እንደሚገባና ሰዎች ችላ ሳይሉ በቶሎ ወደ ሕክምና ቦታ መሄድ እንዳለባቸው ያስረዳሉ። ኮሌራ በባህሪው በተቅማጥና ትውከት አማካይነት በሰውነት ውስጥ ያሉ ጠቃሚ ንጥረ ነገሮችን ሁሉ የሚያሳጣ በመሆኑ በተለይ ሕፃናትና አረጋውያን ላይ ከፍ ያለ ጉዳት ያደርሳል። ከዚህ አኳያ በተቻለ መጠን አስፈላጊውን ጥንቃቄ በማድረግና የበሽታው መምጫና መተላለፊያ መንገዶችን መገንዘብ እንደሚገባም ነው ዶክተር ሰላም የሚያብራሩት።
በሽታው ሕፃናትና አረጋውያን ከያዛቸው የልብ ምታቸውን በማዛባት በሰውነታቸው ውስጥ ያሉትን ጠቃሚ ንጥረ ነገሮች አሟጦ በመጨረስ ራስን እስከመሳት ሊያደርስ ይችላል። ስለዚህ ህመሙ ሲሰማ በቶሎ በአቅራቢያ ወደሚገኝ ጤና ተቋም በማምራት አስፈላጊውን ሕክምና ማግኘትና ከሰውነት የወጡ ጠቃሚ ነጥረ ነገሮችን በቶሎ መተካት እንደሚያስፈልግም ይጠቁማሉ።
ይሁን እንጂ የበሽታው ተጠቂዎች ወደ ሕክምና ቦታ እስኪደርሱ ድረስ በቤት ውስጥ ሕይወት አድን ንጥረ ነገር /ORS/ በመመሪያው መሠረት መጠቀም አልያም ደግሞ በአንድ ሊትር ውሃ ውስጥ 6 የሻይ ማንኪያ ስኳርና 1 ማንኪያ ጨው በመቀላቀል ባስመለሳቸውና ባስቀመጣቸው ቁጥር መውስድ እንዳለባቸው፤ ይህም ሳይዳከሙ ጤና ተቋም መድረስ እንደሚያስችላቸው ዶክተር ሰላም ያብራራሉ። በተጨማሪም ከጣፋጭ ነገር ውጪ ያሉ ማንኛውንም ሰዎች የሚጠቀሟቸው ፈሳሽ ነገሮችን መውሰድ እጅግ አስፈላጊ መሆኑንም ይመክራሉ።
ዶክተር ሰላም እንደሚገልፁት፣ የኮሌራ የመተላለፍ መጠን በጣም ፈጣንና ከፍ ያለ መሆኑን ኅብረተሰቡ ሊገነዘብ ይገባል። በተቻለ መጠን ህመሙ ያለበትን ሰው ብቻውን ማድረግ፣ በተመገበበትና በጠጣበት ዕቃ ሌላ ሰው እንዳይጠቀም ማድረግ፤ ሕፃናትና አረጋውያን ብሎም ተጓዳኝ በሽታዎች ያሉባቸው ሰዎችን ከአካባቢው ማራቅ ያስፈልጋል።
ኮሌራ እስከ አሁን በአዲስ አበባ ከተማ በወረርሽኝ መልክ ባይታይም በሌሎች ክልሎች ላይ ስለመኖሩ እየተነገረ ነው። አንዳንድ ሰዎችም በኮሌራ ታመው ወደቅዱስ ጴጥሮስ ሆስፒታል እየመጡ ይገኛሉ። ስለዚህ በተቻለ መጠን ግንዛቤን በማሳደግ ኅብረተሰቡም የራሱንና የአካባቢውን ንጽህና በመጠበቅ የሚመገበውን ምግብና የሚጠጣውን ውሃ ንጹህ በማድረግ ከችግሩ መዳን ያስፈልጋል። ይህ ሳይሆን ቀርቶ በበሽታው ከተያዙ ግን ችግሩ ከፍ ያለ ጉዳት ሳያስከትል ወደጤና ተቋም መምጣት ይገባል።
ውሃ የመሰለ ተቅማጥ፣ ማስመለስ፣ ትኩሳትና የአካል መዳከም ካለ ህመሙ ኮሌራ ሊሆን ስለሚችል በአፋጣኝ ወደ ጤና ተቋም መምጣት ያስፈልጋል። ታማሚው በቤቱ በቆየ ቁጥር ከተቅማጡና ከማስመለሱ ጋር ከሰውነቱ የሚያጣቸው ጠቃሚ ሚኒራሎች (ንጥረ ነገሮች) ስለሚኖሩ ጉዳቱ ከፍ ይላል። በሌላ በኩል የክረምት ወቅት ከኮሌራ በተጨማሪ የመተንፈሻ አካላት ችግሮችን በማምጣትም ሚናው ከፍ ያለ በመሆኑ ሰዎች እንደ ጉንፋን መሰል ምልክቶች (ትክትክ ዓይነትና ተራዘመ ሳል) ሲኖር ወደጤና ተቋም መሄድ ያስፈልጋል።
በአየር መቀየር ምክንያት የሚከሰቱ በርካታ የመተንፈሻ አካላት ችግሮች ሊከሰቱ ይችላሉ። በተለይም አስም፣ የቆየ የመተንፈሻ ችግር፣ ሳይነስ ያለባቸው ሰዎች መድኃኒታቸውን በአግባቡ መጠቀም፤ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባቸዋል። ከሚያውቁት የህመም ሁኔታ የጨመረ ትንፋሽ ማጠርና መሰል ችግሮችን ያስከተለ ህመም ከተሰማቸው ግን በአስቸኳይ ወደሕክምና ተቋም መሄድ እንዳለባቸው ይመከራል።
በተለይ አሁን ላይ በብዙ ሰዎች ላይ ጉንፋን መሰል ምልክቶች እየተስተዋሉ ነው። ይህ ምናልባት መንስኤው ምንድነው የሚለውን ለማጤን ጥናት ማድረግ ሊያስፈልግ ይችላል። ነገር ግን ማንኛውም ሰው ከተለመደው የጉንፋን ህመም የተለየ ብሎም ለቀናት የዘለቀ የጉሮሮ ህመምም ይሁን ሳል ካጋጠመው ወደሆስፒታል በመሄድ ምንነቱን መለየት ብሎም ተገቢውን ሕክምና አግኝቶ ከተባባሰ ችግር ራስን ማዳን ይገባል።
የግል እና የአካባቢን ንጽህና የመጠበቅ ዝቅተኛ ልምድ ባለባቸው አካባቢዎችና ያልበሰሉ ምግቦች ጥቅም ላይ በሚውሉባቸው ቤቶች ውስጥ ሁሌም ቢሆን ኮሌራን ጨምሮ አተት ዋነኛ ምልክታቸው የሆኑ የተለያዩ በሽታዎች እንደሚከሰቱ ግልጽ በመሆኑ የግልና የአካባቢ ንጽህና በመጠበቅ ፤ በተለይም በዚህ በክረምት ወቅት ካልበሰሉ ምግቦች ራስን በማራቅ ጤናን መጠበቅ ያስፈልጋል።
እፀገነት አክሊሉ
አዲስ ዘመን ሰኔ 24/2015