ሰሞኑን እኔ ወደ ምኖርበት ኮንዶሚኒየም አንድ ጓደኛችን ቤት ሊቀይር እንደሆነ ነግሮኝ ነበር። ወደ አካባቢው በመምጣት የሚከራየውን ቤት አይቶ በዋጋ ከተስማማ በኋላ ኪራዩን ከፍሎ ቁልፍ ተቀብሎ ነገ እቃዬ ይዤ እመጣለሁ ብሎ ይሄዳል። ሆኖም ግን በዚያው ዕለት ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት አካባቢ ሲሆን ጓደኛችን እቃውን በመኪና አስጭኖ በመምጣት እንድናግዘው ስልክ ሲደውል በጣም ነበር የተደናገጥኩት።
በብርሃን ወደ ተከራየው ቤት መግባት እየቻለ እንደሌባ በሌሊት እቃውን ለማጓጓዝ መሞከሩ ቢገርመኝ ሌሊት የሚያስኬድ ምን ጉድ መጣ ስል ጠየኩ። እሱም እቃውን ከመኪና ላይ ለማውረድ የሚጠየቀው ብር ከአቅሙ በላይ በመሆኑ በጫኝና አውራጆችን የሥራ መስክ የተደራጁ ወጣቶችን ለመሸሽ ጉዞውን በሌሊት ማድረጉን አወጋኝ። ለካ እኔ አላስተዋልኩም እንጂ ማታ ማታ ከምሽት ስድስት ሰዓት ጀምሮ እስከ 12 ሰዓት ባለው ጊዜ ወደፎቅ የሚመላለስ የእግር ኮቴና የእቃ ኳኳታ መበራከት ለዚህ ኖሯል።
ቤቴ ምድር ላይ በመሆኑ አንዳንድ ቀን ከታች ወደላይ ወይም ከላይ ወደታች የሚመላለሰው የሰው ኮቴና የእቃ ኳኳታ ስሰማ የደህንነት ስጋት አሳድሮብኝ እንደነበር አልሸሸገም። ከቤቴ ባልወጣም በመስኮቴ አሻግሬ እንደተመለከትኩት ለግርግሩና ለኳኳታው ምክንያት የሆኑት ከፎቅ ወደ ምድር እቃ የሚያጓጉዙ ሰዎች (ቤት በመልቀቅ ላይ ያሉ) መሆናቸው ተመልክቼ ነበር።
በወቅቱ ግምቴ የነበረው ቤት የሚለቁ ሰዎች እቃቸውን ቀስ ብለው በጥንቃቄ በማውረድ ለመኪናው ቅርብ ወደ ሆነው /የመኪናው ማቆሚያ ቦታ/ፓርኪንግ/ በማስጠጋት በማግስቱ በጠዋት መንገድ ሳይዘጋጋ ለመጫን እንዲመቻቸው አስበው እንደሆነ ነበር። ነገሩ ”ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ” አይነት መሆኑ የገባኝ ግን አሁን ላይ ትንሽ ዘግይቶ ነው። ነገር ከሥሩ ውሃ ከጥሩ ይባል የለ በጨለማ ጉዞን ከመጣ ጉዳዩ ምን ያህል አሳሳቢ እንደሆነ ለመረዳት አያዳግትምና ስለጉዳዩ የሚያወቁ ሰዎች ለማነጋገር ወሰንኩ።
ቤት በመልቀቅ ላይ ያሉ ሰዎች እንደሚሉት ከሆነ በጨለማ ቤት ለመልቀቅ የተገደዱበት ዋንኛ ምክንያት በጫኝና አውራጅ ተደራጀተው በየሰፈሩ እኛ ካልሆንን ማንም ሰው ይህንን እቃ ከመኪና ላይ ማወረድ አይችልም የሚሉ ጉልበተኞችን ሽሽት እንደሆነ ይናገራሉ። ታዲያ ቢያወርዱስ ምን አለበት ሥራቸው አይደል እንዴ ስል ጠየኩኝ።
ማውረዱን ማን ከልክሎቸው ነገር ግን እቃውን ከመኪና ላይ ለማውረድ የሚጠሩት ዋጋ ሁሉም እቃ ቢገመት የማያወጣውን ነው ይላሉ። አንድ መኪና እቃ ለማውረድ የሚጠይቁት ብር በቀላሉ ከ5ሺ ብር በላይ እንደሆነም ጭምር ነግረውኛል።
እቃውን ከመኪና ለማውረድ እነሱ ከተመኑት ዋጋ ተከራክሮ ለማስቀነስ የማይሞከርና የማይቻል እንደሆነም ያነሳሉ። ምናልባት ልባቸው ራርቶ ቀነስን ካሉ እንኳን ቀነስን ብለው የሚጠሩት ብር ከአራት መቶ እና አምስት መቶ ብር አይበልጥም። ሰውየው የመክፈል አቅም ይኑረውም አይኑረውም እነሱ የሚጠሩትን ዋጋ እስካልከፈለ ድረስ ያንን እቃ ማውረድ ሆነ በሌላ አካል ማስወረድ አልችልም፤ ኧረ እንዲያውም አይታሰብም።
ግምታዊ ጥሪያቸውን ያልቻለ ሰው ደግሞ ለራሱ በቤተሰብ አባላት ሊያወርድ ቢሞክር እንኳን ጉድ ነው የሚፈላው። እንዴት ይህ ሆነ ብለው በሰው ንብረት ላይ ፈቃጅና ከልካይ ሆነው ለያዥ ለገናዥ አስቸግረው ለግብግብና ለዱላ የሚዳረጉበት ሁኔታዎች የተፈጠሩበት አጋጣሚዎች መኖራቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ይናገራሉ።
የኑሮ ውድነቱ ናላው የዞረው የቤት ተከራይ ደግሞ የተሻለ አማራጭ ሲያገኝ ትንሽ ብር ትርፍ አገኘሁ ብሎ ተደስቶ ቤት ለቆ ሌላ ቦታ ሲገባ ካለበት ሲለቅም ሆነ ወደሌላ ቦታ ሲገባ የጫኝና አውራጅ የሚጠየቀው ሁለት ጊዜ ነው። ከነበረበት አካባቢ ሲለቅ ሆነ ወደ አዲሱ ሠፈር ሲገባ ንብረቱ ወደ መኪና ለማስጫንም ሆነ ለማስወረድ የቤቱን የአንድ ወር ኪራይ ክፍያ የሚበልጥ ወጪ ለእቃ መጠየቁ አይቀሬ ነው።
በፊት የነበረበት የከፈለ ሰው እንኳን እዚያ ከፍዬ ነው ያስጫንኩት ቢል ሰሚ የለውም። ሰውየው መክፈል አልችልም እባካችሁ በአቅሜ መጠን ይህንን ያህል ልክፈል ብሎ ስቅስቅ ብሎ ቢያለቅስ እንባው ከማበስ ይልቅ የጉልበት ጨዋታ ይጀመራል። ባስ ሲል ደግሞ የሕግ ያለህ ብሎ ቢጮህ እንኳን ጩኸቱ ሰሚ አልባ ነው።
በአካባቢው ያሉ የጸጥታ አካላትን ቢያመለክት ጫኝና አውራጅ ሥራ ላይ የተሰማሩ አካላት በሕግ የተደራጁ ሕጋዊ ሰውነት ያላቸው መሆናቸውን አስረግጠው በመንገር ተስማሙ ከማለት በዘለለ የሚሰጡት መፍትሔ የለም።
በጫኝና አውራጅ የተደራጁ አካላት የጭነት አገልግሎት የሚሰጡ መኪናዎች ወደ ኮንደሚኒየም ውስጥ የሚያስገባው መንገድ ሲጎዙ ካዩ ከየት መጡ ሳይባል መኪናውን በቁጥጥር ሥር ያውሉታል ። “በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” እንዲሉ ከኑሮ ውድነት የተነሳ ሰው የእለት ጎሮሮውን እንኳን ለመሸፈን እየተናነቀው ባለበት በዚህ ጊዜ ደግሞ በሰበብ አስባብ ኪሳቸውን ለማዳበር የሚፈልጉ ሊያውም በመንግሥት አካላት በሕግ የተደራጁ አካላት እየፈጸሙት ያለው ተግባር አስነዋሪ ነው።
ምክንያቱም እነሱን ሽሽት ሰዎች ከሚያደርጉት የጨለማ ጉዞ ጋር ተያይዞ ሌላ ተደራራቢ ችግር ሊያመጣ ይችላልና በደንቡ መታየት የሚገባ ጉዳይ ነው። እነዚህ አካላት ከሰው ተፈጥሮ ምንም ሰብዓዊነት ሳይሰማቸው ሰው ላይ የሚጭኑት የዋጋ ክምር ግን በእጅጉ የሰውን ሞራል የሚጎዳ ነው።
ይህ በሕጋዊነት ያደራጃቸው አካላት በጫኝና አውራጅ በሚል ወጣቶችን አደራጅተው የሥራ እድል ከመፍጠር በዘለለ ሥራቸውን በምን አግባብ እያከናወኑ እንደሆነ ክትትልና ቁጥጥር እንደማይደረግ አመላካች ነው። የመንግሥት አካላትም የህብረተሱን እሮሮ ሳያውቁት ቀርተው ሳይሆን እየሰሙ እንዳልሰሙ በመምሰል በግዴለሽነት እያለፉት ይመስለኛል።
ትንሽ ቀዳዳን ተጠቅሞ በዚያ ውስጥ በመሹለክ ለማስፋት የሚሞክሩትን አካላት አደብ ማስያዝ በሁለቱም በኩል የሚመለከታቸው አካላት ጉዳዩን በጥሞና ተመልክተው ሊያስተካክሉት በሕግ አግባብ የሚመሩበት ሁኔታ ሊፈጥር የግድ ይላል። በሕጋዊነት ቢደራጁም በምን ሁኔታ መሥራት እንዳለባቸው ግልጽ የሆነ አሰራር ተዘርግቶ ህብረተሰቡም ይህንን የሚያወቅበት ሁኔታ ከተፈጠረ በተበጀው ሕጋዊ መስመር መሠረት ችግሮች ሊፈቱ የሚችልበት ሁኔታ ይፈጠራል።
ሕብረተሰቡ በጨለማ አዩኝ አላዩኝ በሚል ፍራቻ የወለደው ድብብቆሽ ወጥቶ በነጻነት መብቱን አክብሮና አስከብሮ የሚሄድበት ሁኔታ ሊኖር ይገባል። ሕብረተሰቡ ደግሞ ዋጋቸው ተመጣጣኝ ከሆነ በሌሊት ጨለማ ከመደነባበር በፀሐይ ብርሃን ወደ ፈለገው ቦታ ለመጓጓዝ ይችላል። ይህ ዛሬ እንደቀላል እያየን የምናልፈው ችግር ነገ መልኩን ቀይሮ ሌላ ትልቅ ችግር ሊፈጥር ይችላልና ባይ ነኝ። የነገ ሰው ይበለን፤፤ ቸር እንሰንብት።
ትንሳኤ አበራ
አዲስ ዘመን የካቲት 18 ቀን 2015 ዓ.ም