ትምህርት ሚኒስቴር ከሰሞኑ በተማሪዎች የአፈታተን ሂደት ላይ አዲስ አቅጣጫ አስቀምጧል። የፈተና አሰጣጡ በተለየ መልኩ በዩኒቨርሲቲዎችና በዩኒቨርሲቲ መምህራን የሚሰጥበትን ሁኔታ አመቻችቶ ተማሪዎችም በዛ ሁኔታ ፈተናቸውን ወስደዋል። ይሄ መሆኑ ከመማር ማስተማር ስርአቱ ባሻገር በትምህርት ጥራት ላይ የሚፈጥረው የራሱ የሆነ አዎንታዊ በረከት አለው ።
ቀደም ባለው ጊዜ የነበረው የፈተና አሰጣጥ ሁኔታ ምን እንደሚመስል ሁላችንም የምናውቀው ነው። ተማሪዎች ዩኒቨርሲቲ መጥተው በአንድ ቦታ ላይ ሲፈተኑ የሚኖረው ጠቀሜታ ሰፊ እንደሆነ ብዙዎች ይስማማሉ ። እንዲህም በሆኖ አንዳንድ ተማሪዎችና የተማሪ ወላጆች በአዲሱ የትምህርት ሚኒስቴር አቅጣጫ ላይ ቅሬታዎችን ቢያሰሙም ብዙሀኑ ተማሪና የተማሪ ወላጆች ግን አዲሱን የአፈታተን ስርአት በይሁንታ ተቀብለውታል።
ሀገር ከምትበለጽግባቸውና ዘመናዊነትን ከምትላበስባቸው መንገዶች ውስጥ አንዱና ዋነኛው ትምህርት ነው። ትምህርት ስንል ሰፊ ሀሳብ ነው። ከዚህ እንደባህር ከሰፋ ሀሳብ ውስጥ ተማሪና የትምህርት ጥራትን ብናነሳ እንኳን ብዙ ሀሳቦችን ማንሸራሸር እንችላለን። ትምህርት ሀገር፣ ትውልድ፣ ስልጣኔ ከሚፈጠርባቸው መንገዶች ውስጥ ዋነኛው ነው ካልን የፈተና አሰጣጣችንና የአፈታተን መንገዳችን ምን ይመስላል? የሚለውን ጥያቄ መመለስ ይኖርብናል።
ያለፉትን ጥቂት አመታት መለስ ብለን ብናይ በትምህርቱ ዙሪያ በርካታ ቅሬታዎች እንደነበሩ እንደርስበታለን። ከፈተና በፊትና ከፈተና በኋላ የሚነሱ አንዳንድ አሉባልታዎች የተማሪዎችን ስነ ልቦና ከመጉዳት ባለፈ በትምህርት ጥራት ላይ የሚፈጥረው የራሱ የሆነ ተጽእኖ ነበረው። አንዳንድ ኃላፊነት በማይገባቸው ሰዎች መሪነት በትምህርቱ ሴክተር ላይ ይሄ ነው የማይባል የአሉባልታ ጦርነት ተከፍቶበታል። መንግስት ይሄን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ከወሰዳቸው ርምጃዎች ውስጥ አንዱ ደግሞ ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲ ውስጥ እንዲፈተኑ ማድረግ ነው።
ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲ ውስጥ መፈተናቸው የትምህርት ጥራትን ከመጠበቅና የሚነሱ አንዳንድ ቅሬታዎችን ከማስቀረት ባለፈ የራሱ የሆነ ጥቅም አለው። ተማሪዎች በውጤታቸው አማካኝነት ወደ ተመደቡበት ዩኒቨርሲቲ ከመግባታቸው በፊት ዩኒቨርሲቲ ምን እንደሚመስል ያያሉ። ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ለሚገጥማቸው ማናቸውም ነገሮች ቀድመው እንዲዘጋጁ እድል ይሰጣቸዋል።
ከተለያዩ ቦታ ከመጡ ተማሪዎች ጋር ለልምድ ልውውጥ እድል ይከፍትላቸዋል። ይሄ ትንሹ በረከቱ ነው። በዋናነት ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲ እንዲፈተኑ የተደረገበት ምክንያት የኩረጃና የአንዳንድ ግለሰቦችን ወገንተኝነት ለማስቀረት ነው። ኮርጆ ያለፈ ተማሪ አይደለም ለሀገር አይደለም ለወገኑ ለራሱ መሆን አይቻለውም። እንደ ወንፊት እያነፈሰ ስንዴውን ከእንክርዳዱ የሚለይ የትምህርት ስርአት ያስፈልገናል። ኩረጃን የሚጸየፍ ተማሪና ማህበረሰብ መፍጠር የትምህርት ሚኒስቴር ተቀዳሚ ስራው ነው። ለዚህም በመማር ማስተማሩ ላይ አስተማማኝ ህግና ደንቦችን ማስቀመጥ ያስፈልጋል።
በአጉል የትምህርት ስርአት ሀገር ነው የሚፈርሰው…ትውልድ ነው የሚመክነው። ሁልጊዜም ለሀገራችን የተሳለውን ነገር ማሰብ ይኖርብናል። ሀገር የምትገነባው ጥራት ባለው ትምህርትና ጥራት ባላቸው ተማሪዎች ነው። ዛሬ ላይ በየህክምና ተቋሙ፣ በየሆስፒታሉ፣ በየጤና ጣቢያው በህክምና ስህተት የምንሰማቸው ሞቶችና የአካል መጉደሎች እኮ ጥራት በሌለው ትምህርትና ጥራት በሌላቸው ተማሪዎች የተፈጠረ ነው።
ዛሬ ላይ በምህንድስናው ዘርፍ እየታዩ ያሉ ክፍተቶች ኩረጃ የፈጠራቸው እንከኖች ናቸው። ችግሮቻችንን ለማሸነፍ በትምህርት ዘርፉ ላይ ይሄ ነው የሚባል ለውጥ ማምጣት ይኖርብናል። የትምህርት ዘርፉን አስተማማኝ ሳናደርግ የምንሄድበት መንገድ ሩቅ አያደርሰንም። ለጋራ ጥቅም በጋራ ስናብር ሀገር እየሰራን እንደሆነ ማሰብ አለብን። ሁሉም ነገር እውቀትን መሰረት አድርጎ የቆመ ነው። እውቀትን መሰረት ያደረገ ተማሪና ማህበረሰብ ካልፈጠርን ሀገራችንን ለውድቀት እየዳረግናት እንደሆነ ልብ ልንል ይገባል።
ሀገራችን በሁሉም መስክ ጥራት ያላት እንድትሆን ጥራት ያለው ትምህርትና፤ ጥራት ያላቸው ተማሪዎችና መምህራኖች ያስፈልጓታል። የአንድ ሀገር ኢኮኖሚ መነሻውና መድረሻው የተማረ የሰው ሀይል ነው። የተማረ የሰው ሀይል ደግሞ ሊገነባ የሚችለው ጥራት ባለው ትምህርት ነው። በአንድ ሀገር ሁሉንም መሆን የሚችሉ ነገሮች ጥቂቶች ናቸው። ትምህርትን ብንወስድ ሁሉም ቦታ ላይ ሁሉንም ነገር ሆኖ ልናገኘው እንችላለን። ካለ ትምህርት የተገነባ ኢኮኖሚ፣ የተመሰረተ ፖለቲካ፣ የቆመ ማህበራዊ መስተጋብር የለም።
ካለእውቀት የሚፈጠር ትውልድ፣ የሚመጣ ለውጥ የለም። ጠንካራ የትምህርት ስርአት ሁሉንም መሆን የሚችል ነው። በዚህ በአንድ ሀገር ላይ ሁሉንም ለሆነ ትምህርት ምን እያደረግን ነው የሚለው ጥያቄ መንግስትም እንደመንግስት እኔና እናተም እንደ ዜጋ ልንመልሰው የሚገባ ጥያቄ ነው። ለአንድ ጊዜ አለምን መለስ ብለን ብንቃኛት በትምህርት የቆነጀች ሆነን እናገኛታለን። ለአፍታ ስልጡን ሀገራትን ብናስባቸው የጥንካሬአቸው ምንጭ ጥራት ያለው የትምህርት ስርአት እንደሆነ እንደርስበታለን።
እኛ ሀገር ሲሆን ግን ሌላ ነው። ትምህርት ለእድገት ዋነኛ ነገር እንደሆነ እናውቃለን ጥራት ያለው ትምህርት ለማምጣት ስንጥር ግን አይታይም። በራሱ የሚተማመን እውቀትን መሰረት ያደረገ ተማሪ ገና አልፈጠርንም። ብዙ ክፍተቶቻችን ለትምህርት ከሰጠነው አናሳ ግምት የተነሱ እንደሆኑ ለማወቅ ጠቢብ መሆን አይጠበቅብንም። በየአመቱ ከትምህርት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ ከተማሪና ከወላጅ ቅሬታ እንደተነሳ ነው። ከመንግስትም ማብራሪያ ሲሰጥ ማየት አዲስ ነገር አይደለም።
በትምህርት ዘርፉ ላይ ጥያቄ የማይፈጥሩ አስተማማኝ ስራዎች ይጠበቁብናል። አሁን ላይ የታየው አዲስ አካሄድ የምንናፍቀውን ለውጥና አዲስነት ይሰጠናል ብለን እናምናለን። እስከዛሬ ለስህተት በተጋለጡ የመፈተኛ ቦታዎች ተማሪዎቻችንን ስንፈትን ነበር። በሚያስተምሩበት ትምህርት ቤት ላይ ፈታኝ ሆነው የተመደቡ መምህራኖች ነበሩ። እኚህና የመሳሰሉት አካሄዶች ለውጥ ሳያመጡልን በትምህርት ጥራቱ ላይ ጥያቄን ፈጥረው ሰንብተዋል።
ጥራት ያለው ትምህርት ጥራት ያለው ማህበረሰብን ይፈጥራል። ጥራት ያለው ማህበረሰብ ደግሞ ጥራት ያላትን ሀገርና ትውልድ መገንባት ይችላል። እናም የትምህርት ሚኒስቴር ለትምህርት ጥራት ቅድሚያ ሰጥቶ መስራቱ ሊያስገርመን አይገባም። ሀገራችን በሁሉም ዘርፍ የእኛን ተሳትፎ የምትፈልግበት ጊዜ ላይ ነን። በትምህርቱ ላይ አስተማማኝ ለውጥ ካመጣን በሌሎች ጉዳዮች ላይ መግባባት አያዳግተንም።
ያልተማረ ጭንቅላት፣ እውቀትንና ምክንያታ ዊነትን ያልተላበሰ አእምሮ መግባባት ይቸግረዋል። የዛሬ ችግሮቻችን ከዚህ እውነት ውስጥ የሚመዘዙ እንደሆኑ ማሰብ እንችላለን። በሁሉም ዘርፍ ውጤታማ ለመሆን ጥራት ያለው ትምህርት ላይ ልንረባረብ ይገባል። እንደ ተማሪ፣ እንደ ዜጋ መንግስት ለሀገር ጥራት በሚወስዳቸው አንዳንድ ማሻሻያዎች ላይ የነቃ ተሳትፎ በማድረግ ጥራት ያላትን ሀገር በመፍጠር ሂደት ላይ ልንሳተፍ ይገባል።
አንዳንድ ነገሮች የተለየ አቅጣጫ ይፈልጋሉ። አለም ከፍጥነት አቅጣጫ የተሻለ ነው የሚል አባባል አላት። እንደ መንግስት፣ እንደ ዜጋ አቅጣጫዎቻችንን በመቀየር የምንቀይራቸው ብዙ ነገሮች አሉ። አሁን ላይ የሚያስፈልገን ምንም ሳይሆን የአቅጣጫ ለውጥ ብቻ ነው። በፖለቲካው፣ በኢኮኖሚው፣ በጤናው፣ በትምህርት፣ በትራንስፖርት ዘርፉ በሁሉም ነገር ላይ የአቅጣጫ ለውጥ ያስፈልገናል። የተራመድንባቸው መንገዶች አዲስ ነገርን አልሰጡንም። የአቅጣጫ እሳቤ በህይወት ውስጥ የትም ቦታ የሚሰራ ነው።
ሰው ከለመደውና ለውጥ ሊያመጠለት ካልቻለ ዘልማድ መውጣት መቻል አለበት። ለተከታታይ አመታት በአንድ አይነት የትምህርት አሰጣጥ ላይ ተሳትፈን ኩረጃን፣ አሉባልታን ማስቀረት አልቻልንም። ለተከታታይ አመታት በአንድ አይነት እሳቤ ውስጥ ቆመን የምንፈልገውን የትምህርት ጥራት አላሳካንም። ይባስ ብሎ ችግሮቻችን ከአመት አመት እየተባባሱ በመማር ማስተማር ስርአቱ ላይ እንቅፋት ሲፈጥሩ ነበር። አሁን የአቅጣጫ ለውጥ ነው ያደረግንው። ይሄ የአቅጣጫ ለውጥ የታሰበለትን አላማ እንደሚያመጣ እሙን ነው።
ከዚህ በፊት የፈተና ስርቆት ነበር። አካባቢን ለመጥቀም ሲባል በትውልድ ላይ በደል የሚፈጽሙ አንዳንድ ግለሰቦችና ቡድኖች ነበሩ። ፈተና ከአንድ ቦታ ወደ አንድ ቦታ ሲጓጓዝ የሚፈጠር ችግር ነበር። የአሁኑ የትምህርት ሚኒስቴር የአቅጣጫ ለውጥ ግን እነዚህን ሁሉ ችግሮች የሚያስቀር ነው። መንግስት የዚያን ሁሉ ተማሪ ወጪ ችሎ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ እንዲፈተኑ ያደረገው ከጉዳቱ ይልቅ ጥቅሙ እንደሚያመዝን ስለተረዳ ነው።
ለተማሪ ትራንስፖርትና ምግብ ተብሎ ከመንግስት ካዝና የወጣው ገንዘብ ብዙ ስራዎችን የሚሰራ ቢሆንም መንግስት ይሄን ውሳኔ የወሰነው ለትምህርት ጥራት ካለው ጽኑ ፍላጎት የተነሳ እንደሆነ ማሰብ አይከብድም። አንዳንድ አቅጣጫዎች እስኪለመዱ ድረስ ዋጋ ያስከፍላሉ። ከተለመዱ በኋላ ግን ዋጋቸው የላቀ ነው። በዚህ የትምህርት ሚኒስቴር የአቅጣጫ ለውጥ ተጉዘን ጥራት ባለው ትምህርት ጥራት ያላቸውን ዜጎች እንደምናፈራ አምናለው።
አዳዲስ ነገሮችን መለማመድ አለብን። በአንድ አቅጣጫ ብቻ መጓዝ አዲስ ነገር አያስገኝልንም። አሁን ላለችው ኢትዮጵያ የሀሳብ ለውጥ፣ የፍጥነት ለውጥ ባጠቃላይ የአቅጣጫ ለውጥ ነው የሚያስፈልጋት። በተመሳሳይ ፍጥነት፣ በተመሳሳይ መንገድ ላይ ተጉዘን ሩቅ መሄድ አንችልም። ያልሄድንባቸውን ሌሎች መንገዶች እንፈልግ። ባልሄድንባቸው ሌሎች መንገዶች ላይ እንራመድ።
ለችግሮቻችን መፍትሄ የምንሰጠው የአቅጣጫ ለውጥ ስናደርግ ነው። ፖለቲካዊና ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊም ተግዳሮቶቻችን እጅ የሚሰጡን ከተለመደውና ከደጋገምንው አዲስ ነገር ከሌለው አሮጌ ልማድ ስንወጣ ነው። በእኛ ሀገር ለብዙ ዘመናት ሳይቀየሩ በአንድ አይነት አቅጣጫና አስተሳሰብ ስር የሰደዱ ነገሮች ብዙ ናቸው። በአንድ አይነት ሀሳብ፣ በአንድ አይነት መንገድ ላይ ተጉዘን ለውጥ ማምጣት አንችልም። ትንሽ ዘወር ማለት አለብን።
አዲስ ነገር መነሻቸው አዲስ አስተሳሰብ ነው። አዲስ ሀገር ለመፍጠር አዲስ መንገድ ያስፈልገናል። አዲስ መንገድ ደግሞ በአዲስ አቅጣጫ የሚገኝ ነው። ትምህርት ሚኒስቴር የሀገር ዋልታና ማገር በሆነው የትምህርት ስርአት ላይ ለውጥ ለማምጣት ብዙ ለፍቷል። የትምህርት ስርአቱን ከመቀየር ጀምሮ፣ መማሪያ መጽሀፎችን በማሻሻል፣ የመምህራኖችን የትምህርት ደረጃ በማጤንና ለለውጡ ይጠቅማሉ ያላቸውን ሁሉ አድርጓል። በዚህ ሁሉ አዲስ ሂደት ውስጥ የሚመጣውን ለውጥ በጋራ የምንጠብቀው ይሆናል። ካሳለፍናቸው አንድ አይነት ሁኔታዎች የተሻለ ትምህርትና ተማሪን እንደምናገኝ ግን የታመነ ነው። በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ፈተና መስጠትን የትምህርት ጥራትን ከማምጣት አኳያ ብቻ ብናየው መልካም ነው። ከዚህ ውጪ ምንም ሊሆን አይችልም።
ልክ እንደ ትምህርት ስርአቱ ሁሉ የአቅጣጫ ለውጥ በማድረግ ልንቆጣጠራቸው እየቻልን ያልተቆጣጠርናቸው ችግሮቻችን ብዙ ናቸው። አንዳንድ ነገሮች ማሰብ ብቻ ነው የሚፈልጉት። አንዳንድ ነገሮች ከተለመደው ወጣ ብለን ስንከውናቸው ልክ ይሆናሉ። ያቃተን ትንሽ ማሰብና..ትንሽ ዞር ማለት ነበር። አሁን ዞር ብለናል.. ጣጣዎቻችን እጅ እንደሚሰጡን እናምናለን። ሀገራችን የቀድሞ ክብሯን፣ የምታገኘው በጨዋነት ነው። ጨዋነት ያምርብናል፤ ውበታችን ነው። ትንሽ በማሰብ…ትንሽ ዞር በማለት የራቀንን ጨዋነት እንመልስ። የሸሹንን ጸጋዎቻችንን እንመልስ። በመኮረጅና በማስኮረጅ የሚያድግ ሀገር የለም። ሀገር ልታድግ የምትችለው የሚገባውን ባገኘ ተማሪና ዜጋ ነው። የልፋታችንን ብቻ በማግኘት ለሀገራችን ውለታ እንዋል።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ጥቅምት 15 ቀን 2015 ዓም